በኢትዮጵያ የታሪክ መዝገብ ስማቸው ጎልቶ ከሚነበብላቸው፤ በአይረሴ ታሪካቸው በዋሉት ውለታ በኢትዮጵያዊያን ልብ ከቀሩ ባለታሪኮች ተርታ እርሱ በቀዳሚነት ይነሳል። የልጅነት ዕድሜ ሳያግደውና ፍርሀት ሳይፈጥርበት ከብርቱ የጠላት ክንድ ጋር ታግሎ ከጠላት ብርቱነት በላይ በርትቶ ጠላትን የረታ ብላቴና ነው። ዘርዓይ ደረስ። ይህ ጉምቱ ልዕለ አዕምሮ ሰኔ 7 ቀን 1930 ዓ.ም (ከ83 ዓመታት በፊት) በሮም አደባባይ የፈፀመው አስደናቂ የጀግንነትና የሀገር ፍቅር ተግባር የዛሬው የሳምንቱ በታሪክ አምዳችን ርዕሰ ጉዳይ ነው።
የኢትዮጵያ ታሪክ ኢጣሊያ በኢትዮጵያ – ከወልወል እስከ ጎንደር (ግንቦት 1927 – ኅዳር 1934) በተሰኘውና በተድላ ዘዮሐንስ ዘውዴ የተሰናዳው መጽሐፍ እንደሚዳስሰው፤ ዘርዓይ ደረስ የተወለደው በ1908 ዓ.ም ኤርትራ ውስጥ አዲ ሓይስ በተባለ ስፍራ ነው።
ከቤተ ክህነት ትምህርት በኋላ ዘርዓይ አስመራ ከተማ ውስጥ በሚገኝና በሳልሳዊ ኢማኑኤል ስም በተሰየመ ትምህርት ቤት ገብቶ ዘመናዊ ትምህርት ተምሯል። ከዚያም መምህር ሆኖ ማስተማር ጀመረ። ይሁን እንጂ ዘርዓይ ለተማሪዎቹ ስለኢትዮጵያ ደጋግሞ መናገሩና መከራከሩ ለጣሊያኖቹ ምቾት የሚሰጥ ስላልነበር ከስራው ተባረረ። እርሱ ግን ‹‹ገብረሚካዜላውያን›› የሚባል ማኅበር አቋቁሞ ኢትዮጵያ በጠላት እጅ ስለወደቀች ሁሉም ሰው በጸሎትም በመንፈስም ከኢትዮጵያውያን ጎን እንዲቆም መቀስቀስ ጀመረ። የኢትዮጵያን መወረር ተቃውሞ በጋዜጣ ላይ ገለፀ።
አማርኛ፣ ትግርኛ፣ ጣሊያንኛና አረብኛ መናገር ስለሚችል በመስከረም 1929 ዓ.ም ወደ ሮም ተላከ። በዚያም አንድ የቅኝ ግዛት አገር ዜጋ ሊያገኘው የሚገባው ከፍተኛ ደረጃ ተሰጥቶት የአስተርጓሚነት ስራውን ጀመረ።
ሰኔ 7 ቀን 1930 ዓ.ም የኢጣሊያ መንግሥት በዶጋሊ ጦርነት ለሞቱት ጣሊያናውያን የተሰናዳ የመታሰቢያ መርሐ ግብር በሮም ከተማ በአንድ የመንግሥት አደባባይ ላይ አዘጋጅቶ ነበር። በዕለቱ ዘርዓይ የኢትዮጵያን ጦርና ሌሎች ዕቃዎች ይዞ ለማላገጫነት እንዲቆም ፒያሳ ዲ ፒአሞንቲ በተባለው አደባባይ እንዲገኝ ተደረገ። ዘርዓይ ከያዛቸው እቃዎች መካከል አንዱ ራስ አሉላ ዶጋሊ ላይ ጀብዱ የሰሩበትና በፋሺስት ኢጣሊያ ወረራ ወቅት ከኢትዮጵያ ተዘርፎ የተወሰደው ጎራዴ ነበር።
ዘርዓይ ፒያሳ ዲ ፒአሞንቲ አደባባይ ሲደርስ፤ ቀደም ሲል አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ቆሞ የነበረው የይሁዳ አንበሳ ሐውልት ሮም አደባባይ ላይ እንዲቆም ተደርጎ አየው። ከሐውልቱ ላይ ሁለት ግልገሎች የምታጠባ የተኩላ ምስል ተቀምጦበታል። በአንበሳው መስቀል ላይ ደግሞ የኢጣሊያ ባንዲራ ተሰቅሏል። የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ መሬት ላይ ተጥሏል። በዙሪያው ተጽፈው ከሚታዩና የኢትዮጵያንና የሕዝቦቿን ክብር ከሚነኩ መፈክሮች መካከል አንዱ ‹‹ …የይሁዳ አንበሳን ልጆችሽ እንደፍየል ጭራውን ጠምዝዘው አምጥተው ከእግርሽ ስር ያሰግዱታል …›› የሚል ነበር። በአደባባዩ የተሰበሰበው ሕዝብም እየሳቀና እየጮኸ አንበሳው ላይ ምራቁን በመትፋት ያፌዝና ይሳለቅ ነበር።
ዘርዓይ ደረስ ሁኔታውን በመገረምና በመናደድ ስሜት ሲመለከት ማርሻል ማሪዮ ኢሶን የተባለ የዘበኞች አለቃ ወደ ዘርዓይ ቀርቦ ድርጊቱን መመልከት እንደማይችል ነግሮት ዘርዓይን ከአካባቢው ሊያባርረው ሞከረ። ዘርዓይ ‹‹እናንተ የምታዩትን እኔ የማላይበት ምን ምክንያት አለ?!›› ብሎ ጠየቀው። የዘበኞቹ አለቃም የዘርዓይን ጥያቄ እንደድፍረት በመቁጠር ‹‹ … ከእንግዲህ አንበሳ የለም! ለተኩላዋ ልትሰግድና ልታመልካት ይገባሃል!›› አለው። ዘርዓይ ግን ‹‹አይደረግም!›› አለ። ክርክሩ ከረረ። ማርሻል ኢሶን ‹‹ … ከእንግዲህ በኋላ አንበሳው የተኩላዋ አሽከር መሆኑን ልነግርህ እወዳለሁ … ያውም ንጽሕናውን ያሻሻለ እንደሆነ … ›› አለ።
ዘርዓይ በእልህ ተከራከረ። አንበሳው ጣሊያኖችን ከአንድም ሁለት ጊዜ ሰባብሮ ድራሻቸውን እንዳጠፋቸው አስረዳው። የዘበኞቹ አለቃ ‹‹ … ከአንበሳው ጀርባ ላይ ወጥታችሁ አሳዩት ቁርጡን ይወቀው!›› የሚል ትዕዛዝ ለወታደሮቹ ሰጠ። ሕዝቡ ጭምር አንበሳው ላይ ለመውጣት ተተረማመሰ።
ዘርዓይ ደረስም በያዘው ጎራዴ ጣሊያኖችን መጨፍጨፍ ጀመረ። ያፌዘበትን ማርሻል ኢሶንን ለአንበሳው እንዲሰግድ አድርጎ እጅና እግሩን ክፉኛ አቆሰለው። የሌሎችንም ሬሳ በአንበሳው ስር ጎተተው።
ሮም ተሸበረች። ‹‹ኢትዮጵያ ሰብራ ገብታ የኢጣሊያን ሕዝብ ጨፈጨፈችው … ታጥቀህ ራስህን ተከላከል …›› ተብሎ ታወጀ። ሁሉም በያለበት ተኩስ ከፈተ። ብዙ ሰው እርስ በእርሱ ተጋደለ። የኢጣሊያ መንግሥት ባለስልጣናት ድርጊቱ ውርደት ስለሆነባቸውና ነገሩን በምስጢር ስለያዙት ስንት ሰው እንደሞተ በውል አይታወቅም። ሆኖም በትርምሱ ምክንያት ብዙ ሰዎች መቁሰላቸው የታሪክ ጸሐፊዎቹን አስማምቷል።
ዘርዓይ ጣሊያኖች ላይ እርምጃ መውሰድ የጀመረው ከረፋዱ አራት ሰዓት ሲሆን፤ ሽብሩ ግን እስከ 10 ሰዓት ተኩል ድረስ ቀጥሎ ነበር።
ኋላ ግን አገሪቱ ሰላም መሆኗንና ሽብሩ የተፈጠረው አንድ የአዕምሮ በሽተኛ ህመሙ ተነስቶበት እንደሆነ የሚገልፅ አዋጅ ተነገረ። የአወጁ ቃል ይህ ብቻ አልነበረም። ‹‹ … ወደ ፒያሳ ሄዳችሁ እጁን ያዙ!›› የሚል ትዕዛዝም ነበረው። በዚህ ትዕዛዝ ምክንያት የከተማው ሕዝብ እንደገና ወደ አደባባዩ ወጣ።
ዘርዓይ ደረስ ሰውነቱ እንደነብር ተቆጣ። በተኩላዋ ሐውልት ላይ ቆሞ በመናገር ሕዝቡን ዝም አሰኘው። ‹‹ … በየቤታችሁ እየዞርኩ ብዙ ሰው አርድ ነበር። ግን እኔን አስሮ የያዘኝና እዚህ ሲያኮራምተኝ የዋለው የአንበሳው ፍቅር ነው። ደግሞም አሟሟቴ ከአንበሳው ስር እንዲሆንልኝ ፈልጌ ነው። ወንድ ይምጣና ይማርከኝ …›› ብሎ ተናገረ። ከተኩላዋ ላይ ወርዶ አንበሳውን እየዳሰሰ ቆመ።
አውቶማቲክ መሳሪያ የያዙ ወታደሮች ከሁለት አቅጣጫ በመምጣት ዘርዓይን ተኩሰው መቱት። ጎራዴውን መዘዘና እንደገና ወደ ሕዝቡ ገሰገሰ። ከተማዋ በተኩሱና በሽሽቱ ምክንያት እንደገና ተረበሸች። ዘርዓይ ቢወድቅም ሊቀርበው የደፈረ ሰው አልነበረም። ጎራዴውን ይዞ ከወደቀበት ተነሳ። መሬት ላይ ወድቆ የነበረውን የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ በማንሳት በደሙ ለውሶ አንበሳው ላይ ሰቀለው።
ተኩላዋ ላይ የነበረውን የኢጣሊያ ባንዲራ የተሰበሰበው ሕዝብ እያ የው አወረደው፤ ቀዳዶ ከመ ሬት ጣለውና ረገጠው። አንበ ሳውን እየሳመ ያነጋግረው ነበር። ዘርዓይ ይህን ሁሉ ሲያደርግ ሊያስቆመው የሞከረ ሰው አልነበረም። አሁን ግን ወታደሮቹ ደግመው ተኮሶበት … ዘርዓይም ወደቀ … ግን አልሞተም ነበር።
ዘርዓይ ይህን ሁሉ ሰርቶ፤ በስድስት ጥይት ተመትቶ መትረፉ ጣሊያኖ ችን አበሳ ጫቸው፤ አስደነገጣቸውም። በወቅቱ በሮም ከተማ ውስጥ ከነበሩት ሐኪም ቤቶች ሁሉ የተሻለ ወደሚባለው የሕክምና ተቋም (ቀዳማዊ ኡምቤርቶ ፖሊክሊኒክ) አስገቡትና ሕክ ምና ተደርጎለት አገገመ።
ሐምሌ 15 ቀን 1930 ዓ.ም ቤኒቶ ሙሶሊኒ በዘርዓይ ጥቃት የቆሰሉትን ለመጠየቅ ሐኪም ቤት ሲደርስ ማርሻል ማሪዮ ኢሶን ሞቶ እየተገነዘ ነበር። ለኢሶን ያመጣለትን ኒሻን አስቀምጦ በከፍተኛ ቁጣ ዘርዓይ ወደተኛበት ክፍል ገባ። አገግሞ ስላገኘው የበለጠ ተናደደ።
‹‹ … አንተ ነህ ሮምን የደፈርካት?›› ብሎ ጠየቀው። ሙሶሊኒም ዘርዓይ በሚገባ ታክሞ እንዲድን ለሐኪሞቹ አደራውን ሰጠ። ዘርዓይን በሞት መቅጣት የኢጣሊያን ስም በማይረባ ነገር በመላው ዓለም መበተን መሆኑን ገልፆ፤ በዳነ ጊዜ በቃልም በጽሑፍም ይቅርታ እንዲጠይቅ፣ የአዕምሮ ሕመምተኛ መሆኑን የሚገልፅ ማስረጃ እንዲዘጋጅና ዘርዓይም ሕመምተኛ መሆኑን እንዲያምን እንዲደረግ ትዕዛዝ ሰጠ።
ፕሮፈሰር ፋውስቶ ኮንስታንቲኒ የተባለው ሐኪም የሙሶሊኒን ትዕዛዝ ለማስፈፀም ላይ ታች አለ። ለብዙ ቀናት አግባብቶ አንድ ወረቀት እንዲፈርም አቀረበለት። ደብዳቤው ስለተደረገለት ሕክምና አመስግኖ ‹‹ … በ500 ወታደሮች አደባባይ ላይ በድንገት ታምሜ በሰዎች ሕይወት ላይ ስላደረስኩት በደል … ይቅርታ እጠይቃለሁ። በስድስት ጥይቶች የተመታው ሰውነቴና አንጎሌም ድኖ በቅርብ ቀን ለመውጣት ሀኪሙ ተስፋ ሰጥቶኛል …›› የሚሉ ሃሳቦችን ያካተተ ነበር።
ዘርዓይ ደብዳቤውን ከሐኪሙ ነጥቆ በመቀዳደድ ፊቱ ላይ በተነበት። ቀደም ሲል በዚሁ ስለዚሁ ጉዳይ በተደረገ ክርክር ላይ ዘርዓይ ‹‹ … በእናንተ አፍ እውነት የሚነገረው መቼ ይሆን?›› ብሎ በድፍረት የጠየቀው ፕሮፈሰር ኮንስታንቲኒ የሐፍረት ማቅ ለብሶ ወጣ፤ ድጋሚ ወደ ዘርዓይ አልተመለሰም።
ፕሮፈሰር ኮንስታንቲኒ በድጋሚ እርሱ በአካል ወደ ዘርዓይ ባይመለስም ጥረቱን ግን አላቋረጠም ነበር። ሁለት ኢትዮጵያውያንን (አንድ ስማቸው ያልተጠቀሰ ደጃዝማችና አንድ መነኩሴ) ላከበት። ሁለቱ ሰዎች የዘርዓይን አቋም ለማስለወጥ ብዙ ደከሙ። የኢጣሊያን መንግሥት ኃያልነትና የእርሱን ወጣትነት እያገናዘቡ ብዙ አባበሉት። እርሱ ግን ሀሳቡን መለወጥ አልፈለገም። ሞግቶ አባረራቸው። አቋሙ እንደማይቀይር ስለታወቀም በድጋሚ እንዲህ ዓይነት ጥያቄ አልቀረበለትም።
ስለሆነም ጉዳዩ ወደ መደበኛ ፍርድ ቤት ቀረበ። መደበኛው ፍርድ ቤት ወደ ጦር ፍርድ ቤት መራው። የጦር ፍርድ ቤቱ ዳኞች በጭካኔያቸው የታወቁ ሦስት ኮሎኔሎች ነበሩ። ሕዝቡ ተሰብስቦ የፍርድ ሂደቱ ተጀመረ።
ዓቃቤ ሕጉ ዘርዓይ 11 ወንጀሎችን እንደፈጸመ በመጥቀስ በቤንዚን ተቃጥሎ እንዲሞት ወይም እጁ ታስሮ በሰረገላ እየተጎተተ በከተማው እየዞረ ለከተማው ሕዝብ እንዲታይ ለቅኝ ግዛት አገራት ዜጎች የተደነገጉ ሕጎችን በመጥቀስ አመለከተ። ሌላ ሕግ ስለሌለ እንጂ እነዚህ ሕግጋትም ለዘርዓይ ወንጀል በቂ ናቸው ብሎ እንደማያምንም ዓቃቤ ሕጉ ገለጸ።
ሰብሳቢ ዳኛው ሌሎቹን ዳኞች ሳያማክር የራሱን ሃሳብ ሰነዘረ። ‹‹ … ኢጣሊያ አንዳች ጉዳት አልደረሰባትም … ›› ብሎ ሲናገር ሕዝቡ ተንጫጫ። ዳኛው ግን ጫጫታውንና ፉጨቱን ከምንም ሳይቆጥር ‹‹ … አንድን እብድ የምንቀጣበት አንቀፅ በዚያው በአእምሮ ሕመምተኞች ቦታ ተቀላቅሎ እንዲኖር ብቻ ነው›› በማለት ፍርዱን ደመደመ።
ሌሎቹ ዳኞች ግን ሳይስማሙ ቀሩ። ‹‹እኛ እብድ መሆኑን አናምንም፤በተጠቀሰው አንቀፅ ይፈረድበትና አሟሟቱን እንመልከት›› አሉ። ዓቃቤ ሕጉ በሁለቱ ዳኞች ሃሳብ ተበረታትቶ ‹‹እርሱን ‹እብድ ነው› የሚል ሰው ራሱ ያበደ ነው›› አለ። የሕዝቡ ጭብጨባ አስተጋባ።
ዳኞቹ መጀመሪያ ማድረግ የሚገባቸውን ስራ ማከናወን ጀመሩ። ዘርዓይ ቃሉን እንዲሰጥ ተፈቀደለት። ጣሊያንኛ በሚገባ ማወቁ ጉዳዩን አንደልቡ ለማስረዳት ጠቀመው። ‹‹ … ምን እንድል ነው የምትሹት? እብድ ነኝ እንድል ነው ወይንስ ጤነኛ?›› ብሎ ዳኞቹን ጠየቃቸው። መልስ የለም።
ወደ ዓቃቤ ሕጉ ዞሮ ‹‹አንተ እንደምትለውና እንደምታወራው መሆኑን ላረጋግጥልህ እወዳለሁ። በእውነቱ የእኔ ዶክተር አንተ ብቻ ነህ›› አለው። ዘርዓይ ሐኪሙ ከሙሶሊኒ ተሻርኮ አብድ ነው ማለቱን፤ሰብሳቢ ዳኛውም ይህንኑ ማስተጋባቱን አጋለጠ። ሙሶሊኒ ሮምን ጥቁር ታሪክ አልብሷት እንደሚሄድም ተነበየ።
የተሰበሰበው ሕዝብ ‹‹ … ይገደል! ይሰቀል! ይቃጠል!›› እያለ ጮኸ። እርሱ ግን በድፍረት ንግሩን ቀጠለ። ብዙ ከወቀሳቸው በኋላ ‹‹ … እኔ ሙሉ ጤነኛ ነኝ!›› አላቸው። ከእነርሱ በቀር ምንም በሽታ እንደሌለው ነገራቸው። ‹‹ … ያገርን መውደድ ቋንቋ ካወቃችሁ አገራችንን እንድንጠላ፣ እርስ በእርሳችን እንድንጣላ ለምን ታስገድዱናላችሁ?›› ብሎ ጠየቃቸው። አሁንም መልስ የለም። በእርሱ ላይ ለመፍረድ ብዙ ሺ ሕዝብ መሰብሰቡን አሳይቶ ፋሺስቶች ግን በአገሩ ሚሊዮኖችን ሲጨፈጭፉ ዳኛ እንደሌለባቸው ገለጸ።
‹‹ግን የኢትዮጵያውያን አጥንትና ደም ዋጋ ሲኖረው የእናንተ ስም እየገማ ትኖራላችሁ!›› አላቸው። በመጨረሻም ‹‹የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በክብር ትኑር! ንጉሥ ተፈሪ በድል አድራጊነት ይኑር! የይሁዳ አንበሳ ምንጊዜም ድል ከሱ ይሁን!›› ብሎ ንግግሩን አበቃ።
ሕዝቡ እጅግ በጣም ጮኸ፤ችሎቱ ተተረማመሰ፤ ዳኞቹ የሚሰማቸው በማጣታቸው ተበሳጩ። ዓቃቤ ሕጉ ‹‹ሮማ ማልቀስና ማዘን የሚገባት ዛሬ ነው!›› አለ። ሰብሳቢ ዳኛው ተሸነፈ፤ በቤንዚን ተቃጥሎ እንዲሞት ሁሉም ዳኞች ተስማሙ።
ችሎቱ በዚህ ሁኔታ ላይ ሳለ ሁለት የፖሊስ መኮንኖች ወደ ችሎቱ ዘለቁ። አንዱ ፖሊስ ወታደራዊ ሰላምታ ከሰጠ በኋላ አንዲት ፖስታ ለሰብሳቢ ዳኛው ሰጠ። ሰብሳቢ ዳኛው ደብዳቤው ላይ የሙሶሊኒን ፊርማ ሲመለከት ደነገጠ።
ሙሶሊኒ በደብዳቤው ለአንድ ‹‹እብድ›› ዋጋ በመስጠት ሲጨቃጨቁ እንደዋሉ መስማቱን ገልፆ ‹‹ … በአርባ ሚሊዮን ደንቆሮ መካከል ተፈጥሬ እናንተን ጠዋት ማታ ማስተማሩ ሰለቸኝ …›› የሚል ከባድ ወቀሳ በማቅረብ ‹‹ … ለእብድ የተደነገገ ሕግ ስለሌለኝ ወደ አዕምሮ በሽተኞች ሐኪም ቤት ሄዶ እንዲቀመጥ ይሁን … በእብደቱ እንጂ ሮምንና ሕዝቧን እንዳልደፈረ እንዲታወቅ›› የሚል ትዕዛዝ አስቀምጦ ነበር። በተጨማሪም ደብዳቤው ማንኛውም ሰው ዘርዓይ ደረስ ስለፈጸመው ነገር ቢያነሳ በገመዱ እንደሚገባ ያስጠነቅቅ ነበር። ፋሺስቶችን በራሳቸው ምድር ላይ ያሸማቀቃቸው ዘርዓይ ደረስም ወደ እስራት ኑሮው ተሸጋገረ።
የፋሺስት አስተዳደር ከተወገደ በኋላ ዘርዓይን ወደ ኢትዮጵያ ለማምጣት የተደረገው ጥረት ሳይሰምር እስራት ላይ እያለ በ1937 ዓ.ም አርፏል። አስክሬኑ ወደ ኤርትራ መጥቶ በሐዘጋ ማርያም ቤተ ክርስቲያን እንዲያርፍ ተደርጓል።
አዲሱ ገረመው
አዲስ ዘመን ሰኔ 13/2013