የህይወት ፅጌዋ የሚፈነዳው ምንጩ የሚንፎለፎለው በወጣትነትህ ላይ ነው። አባትህን የሚያንገላታው የህይወት ማእበል ለአንተ ለወጣቱ በረጋ ሀይቅ ላይ ወደ ፀሀይ መጥለቂያ እንደሚደረግ የጀልባ ጉዞ ነው። ልብን በደስታ መንፈስ በተስፋ ይሞላል።
ወጣት ከሆንክ የቀጠፍከው የፅጌረዳ እንቡጥ እጅህ ላይ ሊፈካ ይችላል። ወጣት ከሆንክ ልትተክለው ያዘጋጀኸው የብርቱካን ችግኝ የበሰለ ፍሬ ልትበላ ትችላለህ። ወጣት ከሆንክ አለም አይገዛህም፤ አለምን ትገዛዋለህ። ህይወት አይበይንብህም አንተ ትበይነዋለህ …… እንዳለው ጋሽ ስብሀት ገብረእግዚአብሄር ወጣትነት አቅም፣ ጉልበት ሆኗት ነገን በከፍተኛ ራእይ የራሷ ለማድረግ ከምትተጋ ጠንካራ ወጣት ጋር ቆይታ አድርገናል። ይህች ወጣት ሀና ሀይሉ ትባላለች። አነቃቂ ንግግሮችን በማድረግ የምትታወቅ ወጣት ናት።
መንቃት እና ማንቃት፤ መብቃት እና ማብቃት የህይወቷ መርህ ነው። የሰው ልጅ ልክ እንደ ውቅያኖስ ነው። ስፋቱ እንጂ ጥልቀቱ አይታይም! በየቀኑ እማራለሁ የተማርኩትን ደግሞ ላካፍላችሁ ወደድኩ! የምትለው ሀና እንዲህ ስለራሷ አጫውታናለች፤ መልካም ንባብ።
በ1989 አ.ም የተወለደችው ሀና የወጣቶችን መንፈስ በሚያጠነክሩ፣ ለበጎ ስራ በሚያነቃቁ ስልጠናዎች የእድሜ እኩዮቿን ለማገዝ እየጣረች ያለች ወጣት ናት። ሀና አፍላ የወጣትነት እድሜ ላይ ብትሆንም የምትናገራቸው ንግግሮች፤ ከአፏ የሚወጡት ቃላት ብስል፤ አስተዋይ ወጣት እንደሆነች ያጠይቃሉ።
ደማቅ ፈገግታ ፊቷ ላይ የሚነበበው ወጣት ለእያንዳንዱ ጥያቄ መልስ ስትሰጥ ልበ ሙሉነቷ ፊቷ ላይ ይታያል። የዚህች ወጣት ጥንካሬና በሳል ቋንቋ ሚስጥር ምን ይሆን ብዬ ስለአሰተዳደጓ ባነሳሁት ጥያቄ ላይ ነው ሀና ከልጅነት ጭንቀቷ ለመሸሽ ስትል ለመደበቂያ የመረጠችው አመራጭ የህይወት መስመሯን እንዳመላከታት የተረዳሁት። ሰው የልጅነቱ ልጅ ነው ይሉት ነገር ወጣት ሀና ላይ ሰርቶ የልጅነት መስመሯ እስከ ወጣትነት እድሜዋ ሳይንሻፈፍ ሰምሯል።
መቼም ትዳር ሲነሳ ስኬታማ ትዳሮች እንዳሉ ሁሉ በሁለቱ ተጣማሪዎች አለመግባባት ምክንያት ለሚፈጠሩ ችግሮች ያፈሯቸው የአብራካቸው ክፋዮች የሚያሳልፉትን የስቃይ ህይወት ማሳያ የሆነችው ሀና ልጅነቷን በቤተሰቦቿ አለመግባባት የተነሳ ከአስር በላይ ትምህርት ቤቶች በአዲስ አበባ ውስጥ እየቀያየረች ትማር እንደነበር ትናገራለች፤ አንዴ ዘመድ ጋ፤ አንዴ አባቷ ቤት፤ ቀጥሎ ደግሞ እናቷ ጋር እየተፈራረቁ የኖሩት እሷና ታናሽ እህቷ በትምህርት ቤት መቀያየር የተነሳ ቋሚ ጓደኛ እንኳን እንዳልነበራቸው ትናገራለች።
ሀናም በእንደነዚህ አይነት ችግሮች መካከል የሚያድጉ አብዛኞቹ ልጆች እንደሚያደርጉት ከዚህ ጭንቀት መውጫ የሚሆን መሸሸጊያ ትፈልግ ጀመር። ያኔ ለሷ እንደመደበቂያ የሆነላት መጻሕፍትን ማንበብና በትምህርት ቤት ውስጥ በሚገኙ በተለያዩ ክበባት መሳተፍ እንደነበር ትናገራለች። ያ ለመሸሸጊያነት የተጠቀመችው አማራጭ ግን ከልጅነቷ ጀምሮ በብስለትና በጥንካሬ ነገሮችን ማለፍ እንድትችል ያደረጋት መሆኑን ነው የምትናገረው።
አሁን ከተማሪነት ዘመኗ ጀምሮ ታደርጋቸው ከነበሩ ማህበረሰብ አቀፍ ስራዎች ያገኘቻቸውን ልምዶች፣ ከህይወት ገጠመኞቿ ጋር አቀናጅታ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍል ለመጡ ወጣቶች በተለያዩ መድረኮች እያጋራች ትገኛለች። በአቻ ስልጠናዎችም የብዙ ወጣቶች ነፍስን ከህልሟ አገናኝታለች።
ከአዋሳ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘችው የ24 አመቷ ወጣት ሁሉም ሰው ለውጥ የሚያመጣ ስራ መስራት ከፈለገ የለውጥ ሀሳብ ብቻ ነው የሚያስፈለገው ትላለች። ነገር ግን ወጣት ምንም ጥሩ ነገር ሲሰራ አይዞህ፣ በርታ፣ ጠቃሚ ነህ የሚለው አካል አለመኖሩ ሁሌም ቅሬታ የሚፈጥርባት መሆኑን ነው የምትናገረው።
̋ከፍታችን በውድቀታችን አይለካም፤ ስንችል ስለማይችሉ ነው፤ ስናሸንፍ፣ ሲሳካልን አሰርተው ነው፤ በከፍተኛ ወጤት ስናልፍ ኮርጀው ነው፤ ስናገኝ ሰርቀው ነው፤ ስንቀድም በብራቸው ነው፤ የሚሉት ሰነፎች ናቸው፤ በመሆኑም መቼም ችሎታችን አይዋጥላቸውም። እኛ ግን ሁሉን በሚችል አምላክ ሁሉን እንችላለን፤ ድንቅ ሆነን ተፈጥረናልና።” የምትለው ሀና ጠንክራ ለማጠንከር ከተለያዩ መጻሕፍቶች ያገኘቻቸውን ጥቅሶች ትጠቀማለች።
በልጅነቷ በክበባት በምትሳተፍበት ወቅት እንኳን ማን መሪ ይሁን ተብሎ ሲጠየቅ እጇን አውጥታ ራሷን የምትመርጥ ብቸኛ ልጅ ነበረች። ይህች ወጣት ራስን ማብቃት ለራስ መሆን ለሌሎች የሚተርፍ አቅም እንዳለው ነው የምትናገረው።
̋አንድ ነገር መለወጥ ብትችል የምትለውጠው ነገር ምን ይሆን ነበር? ለውጥ ከውስጥ የሚጀምር ሂደት ነው …. ማንም ብትሆን ከየትም ብትነሳ ከየትም ብትመጣ ….. መለወጥ ከፈለክ የለውጥን መንገዶች መማርና ማወቅ ብቻ ነው የሚጠበቅብህ ….” ሀገራችንም ለሚያስፈለጋት ለውጥ ጊዜ ከመስጠት ይልቅ ሁሉም የሀገር ዜጋ ጉዳዩን ጉዳዬ ብሎ የለውጥ መንገድን መጀመረ እንደሚኖርበት ነው የምትናገረው።
ገና የአስራ ሰባት አመት አፍላ ወጣት እያለች ነበር ̋አልታመምኩም፤ አለተደፈረኩም፤ ምንም ነገር አልቸገረኝም፤ ግን እርዳታችሁ ያስፈልገኛል፤ ህልሜን አድኑልኝ።” የሚል ማስታወቂያ የለጠፈችው። ይህች ወጣት ወጣቱ ተጠግቶት የሚያስተምረው ሰው ካላገኘ ማንም እየተነሳ የሚሞላበትን ሀሳብ የሚያስተናግድ ባዶ እቃ ሆኗል የሚል እምነት አላት።
ወጣትነት አቅም ነው። ራእይ የሌለው ወጣት መረን ነው። ዝም ብሎ እንደመንጋ ይነዳል ህልም ያለው ከሆነ ህልሙን በጉልህ የፃፈ ከሆነ ግን ለነገ ህልሙ ሲል የሚጠነቀቅ ራሱን ጠብቆ መኖር ይችላል ትለናለች።
”ነገዬን አትንኩብኝ፤ ነገዬ ውስጥ ልጆቼ … ስኬቴ ….. ጀግንነቴ …. ከሞት በኋላ ያለው ህይወቴ እና እጁን ዘርግቶ የሚጠብቀኝ ፈጣሪዬ ይጠብቀኛል። ነገዬን አትንኩብኝ፤ ትናንት ውስጥ የተነሳሁበት ቦታ…. ብሄር ….. ቦታ ….ሰው …. አመለካከት ….. ድክመት እና ጥንካሬዬ ሁሉም ላልጨብጠው አልፏል።” የምትለው ወጣት በመዳፏ የጨበጠችውን ዛሬን ተማምና የነገ ህልሟ ላይ የሚያደርሳትን ተግባር ታከናውናለች።
ነፍሰጡር ሴት ነገ ላይ ልጅ እንደምትወልድ አስባ ለአዲሱ እንግዳ መቀበያ የተለያዩ ዝግጅቶች ታደርጋለች። በዙሪያዋ ያሉ ሰዎችም ያን ያህል ይጠነቀቁላታል። እኔም ለህልሜ ያን ያህል ነው የምጠነቀቀው። ነገ እንደማቅፈው ለማውቀው ህልሜ መደላድል አዘጋጃለሁ የምትለው ወጣት ሀና ነገዋን በተስፋ እየጠበቀች ዛሬን ያለምንም ዋዛ ፈዘዛ የምታሳልፍ ጠንካራ ወጣት ነች።
በተለያዩ ድርጅቶች ውስጥ በተለያዩ ክህሎቶች ላይ ስልጠና የምትሰጠው ይች ወጣት ለሁሉም ሰው መድረስን ተስፋ በመሰነቅ አማርኛ፤ እንግሊዝኛ፤ ኦሮሚኛ፤ ሲዳሚኛ (በጥቂቱ)፤ ቋንቋዎችን በሚገባ በማወቅ ስራዋን ለማቅለል ትጠቅምበታለች።
”ከልጅነቴ ጀምሮ አንዳች መልካም ያልሆነ ነገ አይቼ አላውቅም! አይኔን ስጨፍን ወይም አፌን ስከፍት አሁን ያለሁበት እና ያለኝ ነገር ሁሉ ይረሳኛል! በወደቅኩበት ጊዜ ሁሉ ተስፋዬ ራዕዬ ብድግ ያደርገኛል!
በነገዬ ላይ ታላቅነትን፥ ፍሬያማነትን፥ ስኬትን ሺህ ጊዜ ተናግሬያለሁ! ተነግሮኝማል! ከምመኘው እና ከማስበው ሁሉ በላይ ነች። ነገር በአንድ ዘር ውስጥ ጫካ እንዳለ ሁሉ ልቤ ውስጥ ለፈጣሪ ካለኝ ሙሉ እና ፅኑ እምነት የተነሳ ነገዬ በፍሬ እንደ ተሞላ ጫካ ነው። ካየሁት ሁሉ ይልቅ ያየልኝ ይበልጣል …” የሚሉ አነቃቂና ተስፋ ሰጪ ቃላትን በመናገር ተስፋ የላቸውም የሚባሉ ወጣቶችን እንኳን ከህልማቸው ጋር የማገናኘት ስራን ትሰራለች።
አዲስ ነገርን፣ ለውጥን አጥብቄ እፈልጋለሁ፤ አዲስ ነገር ከመውደዴ የተነሳ አዲስ ለውጥ እንኳን ባይኖር አዲስ ነውጥ መኖሩ አይቀርም። ህይወትሽን ለምን ትወጂዋለሽ? ብትሉኝ ሁሌም ለመኖር የምጓጓበት እና ለመኖር የምጓጓለት ምክንያት ስላለኝ ነው እላችኋለሁ። በርግጥም በየቀኑ ወደ ላይ ከፍ እንጂ ወደ ታች ዝቅ ያልኩባቸውን ቀኖች ብዙ አላስታውሳቸውም። በርግጥም በእያንዳንዱ ቀን በህይወቴ አዲስ ነገር አለ፤ አልያም አዲስ ሰው ይኖራል የምትለው ሀና ተስፋና አዲስ ነገር የህይወት ጉዞዋ መቃኛ ናቸው።
ሀና ስለ ሀገራችን ኢትዮጵያ ስትናገር፤ ሀገራችን አሁን ያለችበት ሁኔታ ሁሉ የጭንቅ ጊዜ ሰዓት እና ወቅት ነው፡፡ ብዙ ውድመት እና ኪሳራ፣ ብዙ ጥላቻና ግጭት የበዛው ምናልባት የምስራች ከፊታችን ስላለ ነው ብዬ አምናለሁ። ከልጅ በፊት እንዳለ ምጥ እጅግ የጨለመው ድቅድቁን ጨለማ የሚሽር ብርሀን ከፊት ስላለ ይሆናል። በተስፋ የተሞላች እናት ከወለደች በኋላ የሚያስፈልጋትን ከመውለዷ በፊት እንደምታዘጋጅ ይሄንን ብርሃን በማሳየት ትውልዱ ማዘጋጀት አለብን። ሰው ተስፋ የሚያደርገው ነገር ከሌለው ህይወቱ በፈተናና በመከራ የታጠረ ይሆናል፡፡
ገና ቀን ሳለ ሌሊት መስሎት ይተክዛል፤ ተስፋ የቆረጠ ሰው ነገን ሳይሆን ዛሬን ብቻ ያስባል። ለዚህም በኃጢአት ላይ ኃጢአት፣ በበደል ላይ በደል ሲሰራ የሚኖረው ተስፋ የቆረጠ ሰው ግዴለሽና ራሱን የሚጥል ይሆናል። በአሁኑ አስቸጋሪና አስከፊ ጊዜ የምናየውም፣ የምንሰማውም፣ የምናነበውም ወዘተ እንደዛ ሊሆን ይችላል። ነገሮች ሁሉ ተስፋ አስቀራጭ መስለው ሊታዩን ግን ይችላሉ፡፡
አብዛኞቻችን በዚህ ምክንያት ሳናቀው ተስፋ የመቁረጥ ስሜት ውስጥ እየገባን እንደምንገኝ አንዳንድ ምልክቶች ማሳየት ጀምረናል፡፡ ይህም ችግር መላ ካልተበጀለት ስለተስፋ፣ ስለነጋችን ዛሬ ቆም ብለን ካላሰብን፣ ነገ የማንወጣው ችግር ውስጥ ልንወድቅ እንደምንችል ሁሉም ሊረዳው ይገባል።
ተስፋ መራራ ጊዜ ላይ ቆሞ ጣፋጭ ነገር ማየት፣ ጨለማ ውስጥ ሆነው ብርሀንን እንደመጠበቅ ነው። ስለዚህ በነገ ውስጥ ያለን መልካም ጊዜ እያሰብን በዛሬ ሁኔታዎች ሳንሸበር የተሻለ ነገ ለሀገራችን ብነመኝላት ደስ ይለኛል።
ሰው ከሰው ጋር ቢጣላ ወይም ሰው ቢያስቀይመው በሰው ቢከፋ ከተከፋበት አከባቢ ፈቀቅ ይላል። ሀገር ግን እንደዛ አይደለችም፤ ከሰውነት በላይ ናትና ተሰፋ ሳይቆረጥባት የምትሰራ መሆን ይኖርባታል።
ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ ስንል ብሔር ስለሌለንም አይደለም፤ ማህበረሰብ ስለሌለንም አይደለም፤ ቋንቋ ስለሌለንም አይደለም፤ ታሪክ ስለሌለንም አይደለም፤ የክልል ሰንደቅ አላማ ስለሌለንም አይደለም፤ የምንደ ግፈው የፓለቲካ ፓርቲ አርማም ስለሌለን አይደለም፤ ተለይተን ስላልተበደልንም አይደለም:: ስላልተራብን፣ ስላልተጠማን፣ ስላልታሰርን፣ ስላልተገረፍን አይደለም፤ ስላልተፈናቀልንም አይደለም:: ሁሉንም ሆነናል። ነገር ግን ከሆነው እና ካለን በላይ የጋራ እናታችን ቅድስት አገር ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ስለምናስቀድም እንጂ። ኢትዮጵያዊነትን ብናስቀድም ለጋራ ህልውናችንና ለሰው ልጅ መሰረት የሚሆን ዘመኑን የሚዋጅ ትውልድ እንሆናለን ብለን በማሰብ ነው ትላለች ሀና።
በሙላት የሚናገሩ የሚኖሩ ወጣቶች መኖራቸው ሀገራችን ተረካቢ ትውልድ እንደማታጣ የነገ ተስፋዋ ብሩህ እንደሆነ ያሳየናል። የወጣቶቻችን ጉልበት የነገ ራእይን አመላካች ስለሆነ እንደ ሀና ያሉ ወጣቶች ይበርክቱልን ብለን እናበቃለን።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ግንቦት 29/2013