አቶ አዱኛ ሂርጳ ይባላሉ። በአስተሳሰብና ማህበራዊ ለውጥ ላይ በስፋት የሚሠሩ ናቸው። አሁን ደግሞ ሰዎች በራሳቸው፣ በቤተሰባቸው፣ በተቋማቸውም ይሁን በአገራቸው ጉዳይ ለምን ብለው እንዲጠይቁ እና መልካም ለውጥ እንዲያመጡ ማበረታታት የሚያስችል ‹‹ለምን ኢትዮጵያ›› በሚል ድርጅት መስርተው በሠሩባቸው ዓለምአቀፍ ግብረሰናይ ድርጅቶች ያዩዋቸውን ተሞክሮዎች ወደ አገራቸው ለማምጣት እየሠሩ ይገኛሉ። በተለይም የሕዝቡን የኑሮ ሁኔታ በጥልቀት ያዩ በመሆናቸው የመፍትሄ አካል ለመሆንም ነው ይህንን ድርጅት የመሠረቱት።
‹‹ለምን ባይነት” ዳር ቆሞ ሌላውን መጠየቅ ሳይሆን ለመፍትሄው አስተዋጽኦ ማድረግን ያስቀድማልና ሰዎች ይህንን እንዲያደርጉ በማሰብም ራሳቸውን በማካተት እንዲሠሩ ለማድረግም እየተጉ ይገኛሉ። ይህ ደግሞ በሃሳብ ብቻ እንዳይቀር ለማድረግም የ‹‹ለምን አሻራ›› በሚል መጽሐፍ ጽፈው ለአንባቢያን አቅርበዋል። ብዙ ተነባቢነት ያገኘና ራስን ለማየት የሚያስችልም እንደሆነ ብዙዎች ምስክርነትን ሰጥተውታል። ሌላው የህይወት ምዕራፍ ጉዟቸውም ቢሆን ብዙ ተሞክሮዎችን የያዘ ነውና ለዛሬ የ‹‹ህይወት ገጽታ›› አምድ እንግዳችን አድርገናቸው ከዚህ ልምዳቸው እንዲያጋሩን ጋብዘናቸዋል። እናንተም ልምዳቸውን ቅሰሙ አልን።
አርአያው ልጅ
ተወልደው ያደጉት በአዲስ አበባ በተለምዶ ሐምሌ 19 በሚባል ሰፈር ነው። ብዙ ቤተሰቦችን አቅፎ ከያዘው ትልቅ ግቢ ውስጥም እድገታቸውን አድርገዋል። ይሁን እንጂ ብዙም የሚወጡና የሚጫወቱ አልነበሩም። ምክንያቱም ቤተሰብ ለልጃቸው ከመሳሳታቸው የተነሳ ከሌሎች ጋር ከተገናኙ መጥፎ ልማድ ያመጣሉ ብለው ስላመኑ ብዙም ውጭ ውጭ እንዲሉ አይፈቅዱላቸውም። በዚህም ትልቁ ግቢ ለእርሳቸው ስፋት እንጂ ማህበራዊ ህይወትን ያዩበት አልነበረም። በእርግጥ ቤተሰቦቻቸው ሁለቱም መምህር ስለነበሩ ክረምት ላይ የመምህራን ልጆች ተሰባስበው ወደሚጫወቱበት የተንጣለለ ሜዳ ወዳለበት ተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት ይወስዷቸዋል። የጨዋታ ጥማቸውንም እንዲያረኩ እድሉን ይሰጧቸዋል።
ክረምት ተጠብቆ ብቻ ሳይሆን ሌላም ራሳቸውን ዘና የሚያደርጉበት እድልም ይሰጣቸዋል። ይህም ቤተክርስቲያን እንዲያገለግሉ የተደረጉበት ሲሆን፤ ወደእንጦጦ መካነኢየሱስ ቤተክርስቲያንም ነበር የሚላኩት። በዚያ ቦታ ሥነ ምግባርና ልዩ ተሰጥአቸውን እንዲረዱ ይሆኑበታል ብለው ስለሚያምኑ ከትምህርት ውጭ ባለው ጊዜ እንዲሄዱ ይፈቅዱላቸዋል። እርሳቸውም ይህንን እድል ‹‹ለዛሬ ህይወቴ መስመር ያሳየኝ ነበር›› ይሉታል። ምክንያቱም የግጥም ጸሐፊነት አቅማቸውን ያዩት በዚህ ቤት ነው። የአመራር ብቃት እንዳላቸው የተረዱትም እንዲሁ በሚሰጣቸው ሃላፊነት ነው። ከዚህም በተጓዳኝ ማህበራዊ ሥራዎች ላይ ያላቸውን ችሎታም በደንብ ያዩበት ሰንበት ትምህርት ቤት መሆኑን ይናገራሉ።
በባህሪያቸው ዝምተኛ የሚባሉ አይነት ናቸው። መጽሐፍ ማንበብ የሚወዱና እንደ እግርኳስ ያሉ የተለመዱ ጨዋታዎች ላይ በሚሰጣቸው ፈቃድ አማካኝነት ልጅነታቸውን ያሳለፉ ናቸው። ከዚያ በተጓዳኝ የሰው ልጅ ሌሎች ችሎታዎችን የሚያየው ከቤተሰብ ወጣ ብሎ በሌሎች ተቋማት ውስጥ በሚያሳልፈውና በሚያደርገው ነገር ነው ብለውም ያምናሉ። ለዚህ ደግሞ ምክንያታቸው የሰንበት ትምህርት ቤቱን ጥቅም መረዳትና ማየታቸው ነው።
በልጅነታቸው በጣም የማይረሱት ነገር የአርአያነት ጉዳይ ሲሆን፤ እርሳቸው የቤተሰቡ የመጀመሪያ ልጅ በመሆናቸው ታናናሾቻቸውን ከማስጠናቱ ባለፈ በሁሉ ነገራቸው አርአያ እንዲሆኑላቸው ግዴታ ይጣልባቸው ነበር። በዚህም ብዙ መሞከር የሚፈልጉት ነገር ግን ትክክል አልመስል ያላቸውን ነገር ከማድረግ ይቆጠባሉ። መተዋቸው ግን ሲጎዳቸው ሳይሆን ሲጠቅማቸው እያዩም ነው ያደጉት። ታላላቆች አርአያ መሆን ካልቻሉ ተከታዮችም ያንን ያደርጋሉ። ስለዚህም በቤተሰቡ ውስጥ የእርሳቸው ዋነኛ ሃላፊነት አርአያ መሆን ነበር። እናም ይህንን ማድረግ መቻላቸው ቤተሰቡን ከማሳረፉም በላይ ራሳቸውንም በብዙ ነገር ጠቅሟቸው እንደነበር ያስታውሳሉ።
አርአያ መሆናቸው ጎበዝ እንዲሆኑ፣ የተለየ ጥሪያቸውን እንዲለዩና ምን መሆን እንደሚፈልጉ አሳይቷቸዋል። እንደውም ራሳቸውን መረዳት የጀመሩት ጭምር ለሌሎች ምሳሌ ከመሆን የመነጨ እንደሆነ ያስባሉ። ‹‹ብዙ ጊዜ ቤተሰብ ይህንን ትሆናለህ ባለን እንመራለን። የልጅነት ፍላጎታችንም ብዙ ገንዘብ አግኝቶ ቤተሰብን ማገዝ የሚያስችል ሙያ ላይ እንዲያርፍም ያስገድደናል። ይህ ደግሞ ብዙዎችን ያለ እቅድና ያለመስመራቸው እንዲጓዙ፤ የበለጠ አትራፊ እንዳይሆኑ አድርጓቸዋል። እኔን ግን ምሳሌ መሆኔ ከዚህ ነገር ጠብቆኛል። እናም ሰዎችም ቤተሰባቸውን መስማትና ለታናናሾቻቸው አርአያ መሆን ሲችሉ እነርሱም መጠቀም እንደሚችሉ ማየትን ከልጅነቴ ካገኘሁት ቢጋሩኝ እላለሁ›› ምክራቸው ነው።
እንደእርሳቸው እምነት ልጅነት የሁሉ ነገር መስመር መያዢያና የወደፊትን ህልም ማስቀመጫ ነው። በዚያን ጊዜ የተሰራ ሥራ እስከ ህይወት ህልፈት ድረስ አብሮ ይቆያል። ስለሆነም ቤተሰብ አርአያ ሁን ብሎ ሃላፊነት ሲሰጠን እሺ እንጂ እንቢ ማለት አይገባንም። ጥቅሙ ለሁሉም ስለሆነ ይላሉ። አርአያነት ሥነ ምግባርን ያላብሳል፤ አርአያነት ቁጥብ ያደርጋል፤ አርአያነት ለሌሎች መኖርን ያስለምዳል፤ አርአያነት ሰውን ሁሉ ማክበርን ገንዘብ ማድረግን ያስተምራል። በቃ አርአያነት የማይሰጠው ነገር የለም። ስለዚህም ለራስ፣ ለቤተሰብ ብሎም ለአገር ለመኖር በራስ መጠን አርአያ መሆን የልጅነት እድገት መሰረታችን መሆን አለበትም ከልጅነታቸው የሚያጋሩት መልዕክት ነው።
እርሳቸው የወላጆቻቸው ብቻ ሳይሆኑ የሁሉም ጎረቤት በመሆናቸው ለእነርሱ መታዘዝ ግዴታቸው እንደሆነ የሚያምኑ ናቸው። ከዚያ ሻገር ሲል የስማቸው ልጅ እንዲሆኑም ይፈልጋሉ። ቤተሰብ ስማቸውን ያወጣላቸው የተለያየ ትርጉም ባለውና ብዙ በሚስማማው ሃሳብ ላይ ተንተርሰው እንደሆነ አጫውተውናል። ይህም አዱኛ ማለት በኦሮምኛ አለም ፣ በጉራጌኛ ሀብት እያለ የሚቀጥል ሲሆን፤ አባትና እናታቸውም በዚህ ማህበረሰብ ውስጥ ያደጉና የተለያየ ቋንቋ ተናጋሪ ስለነበሩ በልጃቸው ይህንን ያዩ ዘንድ ስማቸውን አውጥተውላቸዋል። እርሳቸውም ለቤተሰቡ ሀብትም ዓለምም ለመሆን ጥረዋል።
ስጦታን በትምህርት የመፈለግ ጉዞ
መጀመሪያ ከትምህርት ጋር የተዋወቁት በአብነት ትምህርት ቤት ውስጥ ሲሆን፤ እስከ መልዕክተ የደረሰ ትምህርት ቀስመዋል። ከዚያ ዘመናዊ ትምህርትን በምስካዬ ኅዙናን መድኃኒዓለም ትምህርትቤት ተከታትለዋል። በእርግጥ በዚህ ቦታ የተማሩት እስከ ስድስተኛ ክፍል ብቻ ነው። ምክንያቱም ቤተሰብ ቦታ ቀይሮ ወደ ቦሌ በማምራቱ የተነሳ እርሳቸውም አብረው መሄድ ነበረባቸውና በቦሌ አየር አምባ መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርትቤት ሰባተኛ እና ስምንተኛ ክፍልን እንዲከታተሉ ሆነዋል። ከዘጠነኛ እስከ 12ኛ ክፍል ደግሞ የተማሩት በቦሌ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው።
በትምህርታቸው የደረጃ ተማሪ ሲሆኑ፤ በተለይም ሂሳብ ላይ ያላቸው ብቃት ጥሩ የሚባል ነበር። በዚህም የ12ኛ ክፍል የመልቀቂያ ፈተናን በጥሩ ውጤት ማለፍ ስለቻሉ ከትውልድ ቀያቸው ሳይርቁ እዚሁ አዲስ አበባ ላይ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ተቀላቅለው ትምህርታቸውን ቀጠሉ። በኢንፎርሜሽን ሲስተምም የመጀመሪያ ደረጃ ዲግሪያቸውን መያዝ ቻሉ። በዚህ መስክ ለተወሰኑ ዓመታት ከሰሩ በኋላ ደግሞ አሜሪካን ከሚገኘው ከአሜሪካን አካዳሚ ኦፍ ፕሮጀክት ማናጅመንት የተመሰከረለት ዓለም ዓቀፍ ፕሮጀክት ማናጀር የሚል ስርተፊኬት አገኙ።
በርከት ያሉ ስልጠናዎችን በተለያየ የሙያ መስክም መውሰድ ችለዋል። በተለይም በሰላም ግንባታ ዙሪያ የወሰዱት ስልጠና መቼም የማይረሱት ነው። ምክንያቱም ስልጠናው ዛምቢያ ሄደው የማንዴላ የትጥቅ ትግል የተጀመረባት ኪትዌ የምትባል ከተማ የአፍሪካ የሰላም ኢንስቲትዩት ውስጥ የወሰዱት ሲሆን፤ የህይወት ምዕራፋቸውን የቀየረላቸው እንደነበረም ያስታውሳሉ። ለተጨማሪ ስልጠናም ሲሄዱ ፍላጎት አድሮባቸው እንዲንቀሳቀሱ ያበረታታቸው እንደነበር ይናገራሉ።
ትምህርት በቃኝ የማይሉት እንግዳችን፤ አሁንም ቢሆን ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በሞኒተሪንግ ኤንድ ኢቫሊዌሽን የትምህርት መስክ እየተማሩ ይገኛሉ። የመመረቂያ ጽሁፍ ዝግጅት ላይ መሆናቸውንም አጫውተውናል። ከዚህ በተጓዳኝ በመንፈሳዊው በኩልም የሥነ መለኮት ትምህርትን ያጠናቀቁ ናቸው።
ጥሪውን ያወቀ ሥራ
የሥራ ሀሁ የተጀመረው እሸት በሚባል የማይክሮ ፋይናንስ ድርጅት ውስጥ ሲሆን፤ የማይክሮ ፋይናንስ ሶፍትዌር አዘጋጅ በመሆን ለሦስት ዓመታት አገልግለዋል። ጥሪያቸው ይህ እንዳልሆነ በተለያየ ምክንያት ሲመለከቱና ውጤታማነታቸውን ሲለኩት ብዙ አላስደሰታቸውምና ደስታን በሥራ ውጤታማነት ለማምጣት ፍለጋ ጀመሩ። ራስን ያላረካ ሥራ ሰዎችንም ሆነ አገርን አያመረቃም ብለው በማመንም ነው ሥራቸውን አቋርጠው ወደሚፈልጉት ተግባር ለመግባት የታተሩት። ብዙም ግን ጊዜ አልፈጀባቸውም። የጥሪያቸውን ዋጋ የኢትዮጵያ ወንጌላዊያን አቢያተ ክርስቲያናት ህብረት ውስጥ አገኙት።
ፍላጎታቸው ማህበረሰብን ማስተባበርና የለውጥ መሪ ማድረግ ነው። እናም በዚህ ድርጅት ውስጥ ገብተው የወጣቶችና የሚሽን ሃላፊ ሆነው መሥራት ጀመሩ። በተለይ በሰላም ግንባታ ዙሪያ፣ በወጣቶች ለውጥ ዙሪያ በርካታ ሥራዎችን ከተለያዩ አጋር አካላትና ከሌሎች የእምነት ተቋማት ጋር በመሆን ሠርተዋል። ለሦስት ዓመት ከመንፈቅም በዚህ ቆይታን አድርገዋል። ከዚያ ኪዩር ኢንተርናሽናል ድርጅት ውስጥ የክለብ ፉት ፕሮግራም ካንትሪ ማናጀር ሆነው መሥራታቸውን ቀጠሉ። ይህ ቦታ አገርአቀፍ ሥራዎችን ለማከናወን ያስቻላቸው እንደነበር ያነሳሉ። ምክንያቱም እግራቸው ዞሮ የሚወለዱ ህፃናትን የማገዝ ሥራ ነው በዋናነት የሚሠራው።
እርሳቸውም በየሆስፒታሎቹ ውስጥ በመዘዋወር ያግዛሉ። እንደውም በቁጥር ሲያስቀምጡት በኢትዮጵያ ውስጥ በዓመት እስከ አምስት ሺህ ህፃናት እግራቸው ዞሮ (የክለብ ፉት) ይወለዳል። እነርሱን የመንከባከብና በተለያዩ ነገሮች የማገዝ ተግባር ከሆስፒታሎቹ ጋር በመሆን የእነርሱ ሥራ ይሆናል። ምክንያቱም ከአምስት ዓመት በታች ሆነው እያሉ ህክምና ካልወሰዱ የአካል ጉዳተኛነታቸው ቋሚ ይሆናል። ስለዚህም ይህ ነገር እንዳይፈጠር በመሥራት ነው ሦስት ዓመት ተኩልን ያሳለፉት።
ሲጀምሩ አካባቢ 15 ሆስፒታሎችን በመደገፍ ነበር። ሆኖም ሆስፒታሎቹ እየሰፉ በሚሄዱበት ጊዜ የሚያግዟቸው
ህፃናትም ሆኑ ሥራው ወደ 37 ሆስፒታል አደገ። በዚህም እርሳቸው ሐኪሞችን በማሰልጠን፣ ለህክምና የሚያስፈልጉ አቅርቦቶችን መስሪያቤታቸው እንዲያሟላ በማድረግና ሁኔታዎችን በማስተካከል እንዲሁም በመምራት ማገልገል ችለዋል። በዚህ ውስጥ እየሰሩ ባለበት ወቅት አንድ ሌላ መጋቢ ድርጅት ማለትም ክርስቶፎር ብላይንድ ኤንድ ሚሽን ወይም ሲቢኤም የሚባል ፕሮግራም ነበርና በፕሮግራም ማናጀርነት እንዲሰሩ ቀጠራቸው። ይህ ድርጅት መጀመሪያ የሚሰሩበት ፕሮግራም ይረዳ ስለነበር የመጀመሪያውንም እያገዙ ሌሎች 37 ፕሮጀክቶችን ጨምረው እንዲመሩም ሆኑ።
በዋናነት በአምስት ዘርፎች ላይ ተመስርተው የሚንቀሳቀሱ ሲሆን፤ አንዱ ዘርፍ በጤና ላይ ይሰራል። ለዚህ ደግሞ ከ12 የመንግሥት ሆስፒታሎች ጋር በዓይን ህክምና ዙሪያ ከባለሙያ ስልጠና እስከ ግብዓት አቅርቦት ድረስ በመደገፍ በጥምረት ይሰራሉ። ኦርዳና (አመልድ)፤ ግራር ቤት የተሀድሶ ማህበርን የመሰሉ የአገር በቀል ድርጅቶች ጋር በመሆንም በትራኮማ ዙሪያ ሰፊ ሥራ ይሰራሉ። በተመሳሳይ በውሃ አቅርቦትና ልማት ላይም በብዙ ነገር ይደግፋሉ። በእግር ማገገም ዙሪያ ቼሻየር ሰርቪስ ኢትዮጵያ ከመሰሉ ድርጅቶች ጋር በጥምረት ይሰራሉ። እንዲሁም በምግብ ዋስትና ፕሮግራም ላይ ከወላይታ ዴቨሎፕመንት አሶሴሽንና ከአመልድ ጋር በመሆን ሰፋ ያሉ ተግባራትን እያከናወኑ ይገኛሉ።
ሁሉን አቀፍ የማህበረሰብ አገልግሎት ላይም ብዙ የሰሯቸው ሥራዎች አሉ። በተለይም ማህበረሰቡ ውስጥ ያሉ አካል ጉዳተኞች በሁሉም መልኩ እንዲታገዙ ማድረግ ላይ ጥልቅ ሥራ የሚሰሩ ናቸው። ሁሉን አካታች ትምህርት ላይም እንዲሁ አሻራቸውን እያሳረፉ ይገኛሉ። ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ ከዓመት በፊት የጀመሩትን ‹‹የለምን ኢትዮጵያ›› እንቅስቃሴን ጀምረዋል። በሥሩ በርካታ ሰዎችን በማቀፍም ሃሳቡ በሰዎች ውስጥ እንዲቀመጥ እያደረጉም ይገኛሉ። ይህ ነገር ሁሉም ላይ እንዲደርስ ለማድረግም ‹‹የለምን አሻራ›› በሚል በልቦለድ መልክ መጽሐፍ ጽፈው ለአንባቢያን አድርሰዋልም።
ለምን ኢትዮጵያ ለምን?
የ”ለምን ኢትዮጵያ” እንቅስቃሴ ዋና አላማ ሰዎች በራሳቸው፣ በቤተሰባቸው፣ በተቋማቸው ይሁን በሀገራቸው ጉዳይ ለምን ብለው እንዲጠይቁ እና መልካም ለውጥ እንዲያመጡ ማበረታታት ነው። ” ለምን ባይነት” ከልጆች ተነስቶ ሁሉንም የእድሜ ደረጃ አዳርሶ በአገር ውስጥ ዳብሮ ዳር ቆሞ ሌላውን መጠየቅ ሳይሆን ለመፍትሄው አስተዋጽኦ ማላመድን መሰረት አድርጎ የሚሰራም ነው። በተለመደው የትምህርት መመዘኛ ተማሪ የሚመዘነው በሚመልሰው ጥያቄ ብዛት እንደሆነ ሁሉ ለምን ባይነትም በሚታየው ለውጥ ተመዝኖ አገር በልጆቿ መፍትሄ ራሷን እንድትለውጥ መሥራትም ነው።
በለምን ባይነት የተለመዱ አሰራሮች ቀርተው ዘመኑን የዋጁ ሥራዎች እንዲፈልቁ ያግዛል። ተጨባጭ የህይወት ለውጥም ለማምጣት ፍቱን መድሃኒት ነው። በስልጠና፣ በመመካከር እና በሌሎች መደበኛ እና መደበኛ ባልሆኑ ዘዴዎች እውቀትን ወደ ተለያዩ ታዳሚዎች ለማስተላለፍም ይረዳል። ራስን የመፍትሄ አካል አድርጎ ሌሎችም መፍትሄ ሰጪ፣ መፍትሄ አመንጪ እንዲሆኑ ያበረታል። ከሁሉም በላይ ራስን ከነበሩበት አሰራር ለማውጣት ያስችላል። ግለሰብ ወጣ ማለት ደግሞ አገር ከችግር ተላቀቀች ነውና የለምን ኢትዮጵያም ለምንነት ከዚህ አንፃር የሚተገበር ነው።
ከተራ ጊዜያዊ ተወዳጅነት ይልቅ በህዝቡ ውስጥ ያለውን ኢዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ እንዲሁም አላስፈላጊ የጥላቻ ትርክት የሚሞግት፣ ከሌሎች ብሔረሰቦች ጋር በፍቅር እና በአንድነት መቆምን የሚሰብክ በህይወት ያለ ወጣት አገራችን ትፈልጋለችና ለምን ኢትዮጵያም ይህንን ለማድረግ የተነሳ ነው። በተጨማሪ ለምን ኢትዮጵያ የባህል እና የቋንቋ ብዝሃነት የሚስተናግድባት ሁሉን አካታች አገር መመስረት በቀላሉ እውን የሚሆን አይደለምና ለምን እያለ ለመፍትሄው የሚተጋ ተተኪ ማፍራትንም አላማው ያደረገ ነው።
ለምን ኢትዮጵያ ሁሉም አካባቢውን ቢያፀዳ አገር ትፀዳለች ብሎ ያምናል። ሰፈር ላይ ከመጠቆም በአጠገባችን ያለውን መጥረጊያ ይዘን የሚደርስበትን ሰፈር አብሮ ለእኔ ብቻ የሚል እኩይ አስተሳሰብን ትቶ ማጽዳትም ያስፈልጋል ብሎ የሚሰራም ነው። ተገቢ ያልሆኑትን እንደ ዕጣ ፈንታችን ከመውሰድ ይልቅ መለወጥን ያነግባል። ከመቀበል ይልቅ ለምን? ብሎ መጠየቅ መፍትሄን እንደሚያመላክትም ያስባል።
ለኛ የሚገባንን የምናውቅ እኛ ስለሆንን ሁሌም ነገሮችን እንደመጡ ከመቀበል ይልቅ ምክንያቶቻቸውን ለማወቅ መሞክር፤ ይህ ለኛ ይገባናል ወይ? ብሎ መጠየቅ የህይወት መመሪያ መሆን እንዳለበትም ያስቀምጣል። ለምን የሚመለሰው በመፍትሄ እንጂ በጥያቄና ንግግር ብቻ አለመሆኑን አምኖ ይሠራል።
የህይወት ፍልስፍና
ሰው በፈጣሪ አምሳል የተፈጠረ በመሆኑ የምንችለውን ያህል የምናደርግለት፣ የምንሳሳለትና የምንጠነቀቅለት ሊሆን ይገባል እምነታቸው ነው። በምድር ላይ ስንኖር አቅማችንን ሙሉ በሙሉ እንድንጠቀም ከፈለግን ነገሮችን የምናመቻች እንጂ የምንገፋ ሊሆን አይገባምም ብለው ያስባሉ። የሰው ልጅ ትልቁ ሀብት ነውም ብለው ያምናሉ። በምክንያትነት የሚያነሱትም መሬትና ገንዘብ በሰው አዕምሮ ተገርተው ምርታማነታቸው ሲጨምር እንጂ ብቻቸውን ሀብት አይደሉም። እናም የሀብቱ አመንጪ እንጂ ገንዘቡ በራሱ ሀብት አይሆንም ባይም ናቸው።
ሀብት መቼም ውስን አይደለም። አዕምሯችን ያመረተውን ያህል ስለምናገኝበት። በዚህም ሰው ካልሞተና መሥራት ካላቆመ በስተቀር ሀብት መወሰን አይችልም። ስለዚህም የሀብት ልኩ አዕምሮ ያመረተው ያህል ነው። የሰውን ልጅ ማልማትም ሀብትን ወሰን የለሽ ማድረግ ነው ይላሉ። ሰው እኔ ይህንን ነኝ ያለውን ማክበር ግድ መሆን አለበት። ከዚህ ጎን ለጎን ግን ከመስመራችን እንዳንወጣ የሚያደርጉንን የማህበረሰብ ሕጎችን መተግበር ያስፈልጋል ብለው ያምናሉ።
ስኬታማነት
ስኬት ሰዎች በራሳቸው ልክ ገደባቸውን አርቆ የሚጓዝ ነው። ከማንም ጋር የማይወዳደሩበትና ከራስ ዛሬ በልጠው የራስ ነገን ማግኘትም ነው። በዚህም ሰው ስኬቱን ሲመዝን ከመክሊቱ መነሳት አለበት። በእቅዱ የሚነሳበት ምን እንዳተረፈና ለነገው ምን እንዳስቀመጠ የሚያይበት፤ ራሱን በሚዛን ላይ አስቀምጦ ደረጃ የሚያወጣበት ነው። ይህ ሲሆን ደግሞ በቁስ፣ በተገኘ እውቀት ብቻ ለክቶ የሚቆም መሆን የለበትም። ምክንያቱም በሁለቱም የሚለካ አይደለም። የሚለካው በሚታየው መልካም ውጤት ነው።
ለራሳችን በሰበሰብነው ሳይሆን በሰዎች ላይ ባመጣነው መልካም ለውጥ ነው። ለዓለም ምን ያህል ጨው ሆኛለሁ የሚለው ሲመለስም የሚመጣ ነው። በምሰጠው መጠን እንጂ በምሰበስበው ልክ ስኬትን አልለካም። ስለሆነም ከዚህ አንፃር እኔ መስመሩን ይዥያለሁ ብዬ አምናለሁ፤ የፈለኩት ላይም እንድደርስ እሰራለሁ ይላሉ።
በማህበራዊ ሚዲያ የምንለጥፋቸውም ሆነ በምናደርጋቸው ነገሮች እንደግል የልቦለድ ሥራ የፈለግነውን ቅርፅ እና እይታ እንዲይዙ ማድረግ ሃላፊነት የጎደለው ሰው ሥራ ነው። ሃላፊነት የማይሰማው ሰው “መልካም የምታገልበት አላማ አለኝ” ሊል አይችልም። አላማውን ለማስፈፀም የሚጽፈው ወይም የሚያካፍለው መረጃ፤ መነሻ ሀሳቡ፣ የገለፀበት መንገድ እና ውጤቱ ትክክለኛ፣ሚዛናዊ እና ፍትሃዊ ካልሆነ ለምን እየታገለ እንደሆነ ቆም ብሎ ማሰብ መቻል አለበት። ከዚያ ውጭ መልካም ነገሩም ሆነ ስኬታማነቱን አያመጣውም። ምክንያቱም ለስኬቱ የሚፈፀመውና የሚፈፅመው አካል በመልካሙ ተግባር መተሳሰር ይኖርባቸዋል። የለውጥ ጉዟቸውም እየታየ መፍትሄ እየሰጠ መሄድ ይገበዋል።
ቤተሰብ
ከባለቤታቸው ጋር የተገናኙት በቤተክርስቲያን በአገልግሎት ምክንያት ሲሆን፤ በእጮኝነት ሦስት ዓመት ያህል ቆይተዋል። ፍቅር የሚባለው ነገር ሳይጀመር በነፃነት በእህትና ወንድምነት በሚገባ የተዋወቁ ናቸውም። ስለዚህም ባለቤታቸው፤ ለእርሳቸው ጓደኛም፣ ሚስትም፣ የልጆቻቸው እናትም እንደሆነች ይሰማቸዋል። በ11 ዓመት የጋብቻ ጉዞ ውስጥ አልፎ አልፎ ጊዜ ቢጋጩም በይቅርታ ብዙ ነገሮቻቸውን አርመው እንዳለፉም አይረሱትም። ለሁለቱም ይቅርታ መባባል ግዴታም መርህም ነው።
ለልጆች ምሳሌ መሆንን ከልጅነታቸው የተማሩ በመሆናቸውም ይህንን ማድረግ ላይ አብዝተው ይጥራሉ። አሁን የሁለት ልጆች አባት ሆነዋልና ደስተኝነትን በቤቱ ለማምጣት ጥሩ አባወራ የመሆን ተግባርን ይከውናሉ። ባለቤታቸውም ብትሆን ከእርሳቸው የተለየ ማንነት ያላት ስላልሆነች ይህ ሥራ የጋራቸው እንደሆነም በጭውውታችን መካከል አንስተውልናል።
የቀጣይ ዕቅድ
ለምን ኢትዮጵያን ማሳደግና ብዙዎች የሚጠለሉበት ማድረግ ነው። ብዙ ሰዎች ሀሳቡን እንዲገዙት፣ የመፍትሄ አካል እንዲሆኑ ንቅናቄውን ማስፋትም ነው። ብዙ ማሳያ የሚሆኑ ፕሮጀክቶችን እስክሰራና ውጤታማ እስክሆን ድረስ መሥራትም ነው። ከዚያ ባሻገር ለራሴ፣ ለቤተሰቤና ብሎም ለአገሬ ይጠቅማሉ የምላቸውን ሥራዎች በአዲስ ፈጠራ መሥራት ይሆናል።
መልዕክት
አገራችን አንድ ብቻ ነች። ለያውም በእጃችን መዳፍ ላይ የተቀመጠች። እናም ማፍረሰም መገንባትም የእኛ ድርሻ ይሆናል። ከሰራንና ከገነባናት ራሳችንን አትርፈን ቤተሰባችንን ጠብቀን አገራችንን ለሌሎች ሁሉ ጥላ እናደርጋታለን። ሆኖም በጥላቻ ውስጥ ሆነን ሳንሰራ እየኮነንን የምንቀመጥባት ከሆንን የሚማረኩባት ብዙዎች ናቸውና እንደ ጭልፊት ከዓይናችን ይነጥቁናል። የእኛነታችንንም ያሳጡናል። ባለአገርነታችንም ይጠፋል። ምክንያቱም የእነርሱን ሀሳብ፣ የእነርሱን ፍላጎት ብቻ ፈፃሚ እናደርጋታለን። ስለዚህም ይህ ከመሆኑ በፊት ዛሬ ነቅተን ልንሰራባት፣ ልንለወጥባት ያስፈልገናል። የአገራችን ውበቷ፣ ብርታቷና ማንነቷ ከእኛ ውጭ አይኖርምና ይህንን አስበን ልንቀሳቀስ ይገባል ምክራቸው ነው።
ማንም ሰው እጅ ከመጠቆም ሊቆጠብ ይገባል። እኔ ምን አበረከትኩንም ማስቀደም አለበት። ልጄ ቢጠይቀኝ የምመልሰው ምን ነገር ሰርቻለሁ፣ በቂ መልስ ሰጥቻለሁ ወይ ብሎ መጠየቅና ምላሹን ማግኘት ያስፈልጋል። ከዚህ ባሻገር ይህ ኑሮ ለእኔ አይገባም ብሎ በቁጭትና በቅንአት መነሳትን ገንዘብ እናድርግ። ከተነጋገርን፣ የተሰጠንን ፀጋ በህብረት መጠቀም ልምዳችን ካደረግን ሁሉ መልካም ይሆንልናል።
በአገር ደረጃ መሰረታዊ የአሰራር ችግር ሊኖር ይችላል። ሆኖም ከግለሰብ ለውጥ ካልተጀመረ በስተቀር መፍትሄው ቀላል አይሆንም። እናም በብርሃን ውስጥ የሚዋኘውን ተስፋችንን በጨለማ ተውጧል ብሎ እንዳይወጣ ካፈነው መቼም ለውጡን፣ ተስፋውንና ብርሃኑን አናገኘውም። ስለሆነም የተከደነውን መክፈት የግለሰቦች ሥራ መሆን ያስፈልጋል። ሀሳብ ወደ ተግባር ካልተለወጠና ንግግር ብቻ ከሆነ ቁም ነገር የለውም። ወሬ ብቻ ሆኖ ይቀራል። የእስከዛሬያችን ጉዞም ከንግግር ያላለፈው ሀሳቡ ሀሳብ ብቻ ሆኖ መቅረቱ ነው። ስለዚህም ለተግባራዊነቱ ግለሰቡ እኔ ምን አበረከትኩ ማለት መጀመር አለበት መልዕክታቸው ነው።
ሌላው ከመፈረጅ አባዜ እንውጣ ያሉት ሲሆን፤ ለዚህም እባብን ያነሳሉ። እባብን ስናስብ ወዲያው ወደ አዕምሯችን የሚመጣው መርዛማነቱ ነው። በመርዙ ሰውን ይገላል እንጂ ምን የሚጠቅሙ ነገሮች አሉት የሚለውን አናስተውልም። ነገር ግን እባብ የተፈረጀው መርዛማ በሆኑት ከ15 እስከ 25 በማይበልጡት ባህሪያቱ ነው። ከ75 እስከ 85 በመቶ የሚሆኑት ጥቅም የሚሰጡ ናቸው። ነገር ግን ያለግብራቸው የመፈረጅ አስተሳሰብ ተጠቂ ስለሆኑ ማንም እነዚህን አያያቸውም። እናም መርማሪ እንጂ ፈራጅ መሆን የለብንም። ምክንያቱም ብዙውን ጥቅማችንን ትንሹ መፈረጃችን ያጠፋብናልና ሲሉ የማሳረጊያ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። እኛም ሃሳባቸው ሃሳባችን ይሁን በማለት ተሰናበትን። ሰላም!
ጽጌረዳ ጫንያለው
አዲስ ዘመን ግንቦት 22/2013