አህያ ያገለግላል ግን ይናቃል ፤ የሰነፍና የደደብ ምሳሌ ይደረጋል። ይህ በሀገራችንም ብቻ ሳይሆን በውጪዎችም ጭምር ያለ አመለካከት ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 21 እንደተጠቀሰው ፤ለጽዮን ልጅ ፡-እነሆ ንጉሥሽ በአህያ ላይና በአህያይቱ ውርንጫ(ግልገል) ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል ሲል ይገልጻል። ጌታ ኢየሱስ አህያይቱንም አምጥተው ልብሳቸውን ጭነው ተቀመጠባት፤ ሲል የተከበሩ ፈረሶች እያሉ በተናቀችው አህያ ለትህትና መቀመጡን ለማሳየት ነው የሚሉ ምሁራን አሉ።
የአህያ ዘሩ የሚመዘዘው ከሜዳ አህያ ዝርያ ነው ። የሰው ልጆችን ወደ አምስት ሺ ዓመት ለሚሆን ጊዜ አገልግሏል። ፈረንጆቹ አህያ ከፈረስ ዝርያ ይመደባል ሲሉ እኛ ደግሞ አህያ ፈረስ በቅሎን ጠቅልሎ በሚጠራው ስያሜ ከጋማ ከብት እንመድበዋለን።
በዓለም ደረጃ በ2006 አ.ም ወደ 41 ሚሊዮን አህዮች እንደነበሩ ተገምቷል። ከዚህ ውስጥ ቻይና 11 ሚሊዮን የነበራት ሲሆን፣ ፓኪስታን ኢትዮጵያና ሜክሲኮ ይከተሉዋታል። ኢትዮጵያን በአህያ ብዛት በሁለተኝነት የሚያስቀምጧትም አሉ።
አህዮችን በተለይም በማደግ ላይ ባሉ ሀገሮች በብዛት ደረቅ ጭነቶችን ለማጓጓዝ ይጠቀሙባቸዋል። በሀገራችን አህዮች ደረቅ ብቻ ሳይሆን ፈሳሽ ጭነቶች በማመላለስ እንደሚያገለግሉም ይታወቃል። ፈሳሽ ጭነት ስላችሁ ነዳጅ መስሏችሁ ፍስስ እንዳትሉ። ውሃ ራቅ በሚልባቸው ወይም የውሃ እጥረት በሚታይባቸው ቦታዎች አህዮች በጣውላ የተሠራ ርብራብ በጀርባቸው ተደርጎ ውሃ በጀሪካን ያመላልሳሉ። ከሸራ በሚዘጋጅ የውሃ መያዣም ውሃ እንዲጭኑ ይደረጋል።
በሰለጠኑ ሀገሮች ጥቂት አህያ ነው የሚያረቡት። እነሱኑ በእንክብካቤ ለመያዝ ብቻ ይፈለጋሉ፤ ከእጅ ወደ አፍ የሚኖሩ ሰዎች ግን የጭነት አህዮች ኑሮዋቸውን ለመደገፍ ይጠቀሙባቸዋል።
አህዮች በገጠር ብቻ አገልግሎት የሚሰጡ እንዳይመስላችሁ። በከተሞችም አገልግሎት ይሰጣሉ። በኢትዮጵያ ዋና ከተማ፣ በአፍሪካ መዲና በአለም አቀፍ ተቋማት መቀመጫዋ አዲስ አበባ ከተማ እምብርት ላይ አህዮች ሰፊ አገልግሎት ሲሰጡ ይታያሉ። በየሰፈሩ አህያ የሚታይበት ሁኔታ አለ። በተለይ ደግሞ ዋና የእህል ግብይት ከሚፈጸምበት አማኑኤል እህል በረንዳ የዘለቀ በርካታ አህዮችን ይመለከታል። አንድ ሰው እስከ ሃያ የሚደርሱ አህዮችን በመጠቀም የጭነት አገልግሎት የሚሰጥበት ሁኔታ ስለመኖሩ የአካባቢው ሰዎችም ይጠቁማሉ።
እኔ እንደ አህያ የሚሠራ እንስሳ ያየሁ አልመሰለኝም፤ ከላይ እንደተጠቀሰው ግን አህያ የሰነፍና የደደብ ምሳሌ ተደርጋ ትቆጠራለች።”የበሬውን ውለታ ወሰደው ፈረሱ” የሚል ብሂል አለ። ለኔ ግን የ‹‹አህያውን ውለታ›› ወሰደው ፈረሱ ቢሉ ይስማማኛል። አህያ ሰርክ ሲያገለግል የሚውል እንስሳ ስለሆነ።
በሬ ለሥራ የሚፈለገው እርሻ በሚኖርበት ጊዜ ብቻ ነው። አህያ በገጠር የታጨዱ ሰብሎች ተከምሮ ወደሚቆይበት ወይም ውድማ (እህል የሚወቃበት ቦታ)ለማድረስ እንዲሁም እህሉ ከተወቃ በኋላ ጎተራ ለማስቀመጥ በአህያ ነው የሚጫነው። የሰብሉ ተረፈ ምርት/ ገለባው/ ወደሚከማችበት ስፍራ የሚወሰደው በአህያ ነው። ለከብቶች ሣር ሲያስፈልግ ታጭዶ የሚጫነው በአህያ ነው። እህሉ ወደ ገበያ የሚወሰደውም ሆነ ከገበያ የተገዛው የሚጫነውም እንዲሁ በአህያ ነው። እህል ወፍጮ ደርሶ ዱቄቱ ቤት የሚመለሰው በአህያ ጫንቃ ነው። እናም አህያ በጭራሽ እረፍት የለውም። ይህ እንስሳ ነው እንግዲህ ደደብ የሚባለው።
በጥንቱ ዘመንም አህያን በጦርነት ጊዜ ስንቅ እና ትጥቅ (ጦርና ጎራዴ) ቀለብም ጭምር በመጫን ይገለገሉበት ነበር። የጦር መሣሪያ ተሽከርካሪዎች መምጣታቸው ለአህዮች ፋታ ሰጥተዋል። አህያ ትንሽ የምታርፈው ስትወልድ ነው፤ አህያ በወለደች አረፈች የሚባለውስ ለእዚህ አይደል፤ የሚያግዛት ስለምታገኝ እንጂ ለመታረስ ብላ እንዳልሆነ ይያዝልኝ።
ከሸገር እስከ ጅቡቲ የተዘረጋው ባቡር የሀገሪቱ ኢኮኖሚ ደም ስር እንደሆነው ሁሉ ፤አህያ በገጠር አካባቢዎች በተለይ በደጋና በወይና ደጋ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ ዋልታና ማገር ነው ማለት ይቻላል። የገጠር ገበያዎች ዋናው ተዋናይ አህያ ነው ብንል ማን ይቀየመናል? የመኪና መንገድ ባልተዘረጋባቸው በገጠራማ ቦታዎች ሸቀጥም ሆነ እህል ለማመላለስ አህያ ወሳኝ ነው።
አህያ ሲቸግር ለእርሻም ያገለግላል። በሬ የሌላቸው ድሃ ገበሬዎች አህዮቻቸውን ጠምደው ሲያርሱ አይቻለሁ። በሬ ግን ከእርሻው ውጪ የአህያን ቦታ ሸፍኖ እህል ጭኖ በማጓጓዝ ሊያገልገል አይችልም፤የቀንድ ከብቶች ከእርሻ በዘለለ ወተትና ስጋቸው ለምግብ፣ ቆዳቸው ለልብስና ለቦርሳ ለጫማ አጥንታቸው ለመጠጫ (የቀንድ ዋንጫ ያስታውሷል) እንዲሁም ለማዳበሪያ ያገለግላል። የበሬ ድምጹ ብቻ ነው የሚወድቀው ሲባል የሰማሁ መሰለኝ። በዚህም በኩል ቢሆን በአንዳንድ ሀገሮች አህያ ስጋ ለመብልም እንደሚገለገሉበት ማስታወስ ያሻል።
በአንድ ወቅት በቢሾፍቱ የአህያ ቄራ ተከፍቶ ከህዝቡ ባህል ጋር ስለሚቃረን ትችት ተሰንዝሮ እንደነበር ይታወሳል። ወዲያው ተዘጋ መሰለኝ። ተመሳሳይ ነገር በኬንያ ሆኖ እንደነበር ሰምቻለሁ። በዚህ ካየነው አህያ ለጭነትም ለእርሻም ስጋዋ ለመብልም(በአንዳንድ ሀገሮች) ያገለግላል ፤ምሉዕ በኩልሄ እንበላት ይሆን?
እንደ አፋር በመሳሰሉ ቆላማ አካባቢዎች ግመል ሁሉም ነገር ነው። ለጭነት ያገለግላል፤ወተቱና ስጋውም ለምግብነት ይውላል። ከሆነ ከሆነ አህያ በአገልግሎት መወዳደር ያለባት ከግመል ነው። ሌሎቹማ ምን ሰርተው?
ነፍስ ሔር መስፍን ሀብተማርያም ባንድ ወቅት ስለ አህያ በጻፉት ጽሁፍ ሰው የሚያገለግለውን አሜን የሚለውን የሚታገሰውን አይወድም ሲሉ ገልጸዋል። በፍጥነት ለሚያደርሰን ፈረስ ምርጥ ሣር ስናበላ፤ ጦር ጎራዴ ለሚሸከምልን አህያ ለምለም ሣር ቆጥበን በመስጠታችን ያለምንም ክርክርና ማድበስበስ ጥንቱን የተመሠከረ ነው። እነ አንበሳና ነበር አልቻልንም የሚሉትን ዝናብ ለአህያ ማዋላችን እንኳ መቼ እንደሆነ አይታወቅም አንጂ በነገደ እንስሳ ለፍርድ እንደሚቀርብ ተስፋ አለኝ ብለው ነበር ደራሲው።
አህዮች በዚህ ሁሉ አገልግሎታቸው ኩንታሉን /100 ኪሎ/ ተጭነው ሲጓዙ በዱላ ይነረታሉ፤ በአለንጋ ይገረፋሉ። አዲስ አበባ የማያቸው አህዮች ሥራ ስለሚበዛባቸው ስለሚገረፉም ከሲታ ጀርባቸው የቆሰለ፤አካላቸው የጎሰቆለ ናቸው ። በገጠር ቢያንስ ለምለም ሣርና ውሃ ስለሚያገኙ በአንጻራዊነት ጥሩ ቁመና አላቸው። ዘመናት አገልግለው ታዲያ አካላቸው እግራቸው ቢታመም የሚያሳክማቸው የለም፤ቢያነክሱ ስለማይሸከሙ እንደ አሮጌ ቁና ይጣላሉ፤በሸገር መንገድ ታመው ቆመው ሳይቀመጡ ሳይተኙ ቆይተው ወድቀው የሞቱ ያየሁባቸው አጋጣሚዎች አሉ።
በገጠር እንዲሁ ሲታመሙ መዋያ ማደሪያቸው በውጪ ስለሆነ ወዲያው የጅብ ራት ይሆናሉ፤ለጅብ ደግሞ የአህያ ስጋ ሠርግና ምላሹ ማለት ነው፤ የአህያ ስጋ ሲወድ ተብሎም አይገለጽም ፤ተረቱም “ጅብን ሲወጉ ከአህያ ተጠልሎ ነው” በሚል ይገልጸዋል። ግን አህያና ፈረስ በቅሎ ታመው መንገድ ቆመው ሲታዩ ህክምናና መኖ የሚያቀርቡ ለእንስሶች ተቆርቋሪ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ቢፈጠሩ እላለሁ።
በሱፊ ተረት ሲጠቅሱ “ብዙ መጻሕፍት የተሸከመች አህያ ያው አህያ ናት!” ይላሉ። እኔ ግን በተረቱ አልገረምም ፤ በሬም መጻሕፍት ቢሸከም መምህሬ አልያም ምሁሬ ልለው አልችልም ያው በሬ ነው። በርግጥም መጻሕፍት የተሸከመች አህያ ያው አህያ ነች ምሁር አትሆንም፤ ቤተመፃሕፍት ሥራው መፃሕፍት መያዝ ነው። መጻሕፍት ስለያዘ ግን ከልሂቃን ጎራ አይመደብም። እውነተኛ ጥበብ የሚገኘው መጻሕፍት በመሸከም አይደለም፤ ቁምነገሩን በማንበብም አይደለም፤ ቁምነገሩን በመኖር ነው።
ቅዱሳን መጻሕፍትን አንብበናል፤ ግን ምሳሌውን ተከትለን በፍቅር አልኖርንም። የሳይንስ ሰነዶችንም አገላብጠናል፤ለምስኪኑ ወገናችን አንጀቱ ላይ ጠብ የሚል ነገር ግን አልፈጠርንለትም ፤ ይልቁንም ጎጥና ብጥብጥ እየተፈጠረለትና እንዲባላ እየተደረገ ነው። (ለእዚህም እያሳፈሩንም እያጫረሱንም ያሉትን አሸባሪዎች ይመለከቷል) ።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ዓርብ ግንቦት 20/2013 ዓ.ም