በዘገባዎቹ በዘመኑ በይዘት ምን አይነት ጉዳዮች ይስተናገዱ ነበር፣ እንዴትስ ይዘገቡ ነበር የሚሉትን ትመለከቱባቸዋላችሁ ብለን በማሰብ ያቀረብናቸው። መልካም ንባብ።
የከብት አርቢዎች ማኅበር ሊቋቋም ነው
አዲስ አበባ (ኢ-ዜ-አ) በጃንሆይ ሜዳ ለመጀመሪያ ጊዜ በተካሄደው ውድድር ላይ የተካፈሉት ግለሰብ ገበሬዎች፤ “የከብት አርቢዎች ማኅበር “ ለማቋቋም ማቀዳቸው ተገለጠ።
በዚሁ በወተት ሀብት ልማት ድርጅት በተዘጋጀው የወተት ከብቶች ትርዒትና ውድድር ላይ ተካፋይ የሆኑት አሥራ ሰባት ከብት አርቢ ገበሬዎች ፤ከትናንት በስቲያ ማታ በሐራምቤ ሆቴል ውስጥ ባደረጉት ግብዣ ላይ ክቡር አቶ ወርቁ መካሻ የወተት ሀብት ልማት ድርጅት ፤ዋና ሥራ አስኪያጅ በተናገሩት ቃል ፤ገበሬዎቹ የውድድሩና ትርዒቱ ፕሮግራም በመልካም ሁኔታ እንዲዘጋጅ ላሳዩት ኅብረት አመስግነዋል። ዋና ሥራ አስኪያጁ ፤ከዚህም በቀሩ በዝግጅቱ ተባባሪ የሆኑትን የወተት ልማት ድርጅት የቦርድ አባሎች የግል ድርጅት ኩባንያዎችን ፤ማስታወቂያ ሚኒስቴርን የክቡር ዘበኛን የፖሊስና የጦር ሠራዊትን ከልብ አመስግነው የትርዒቱና ውድድር ዝግጅት ገበሬዎችን በማቀራረብ በመካከላቸው አንድነት በመፍጠር በሥራቸው ወደፊት በበለጠ እንዲተጉበትና የከብት ርቢ አያያዛቸውንም በዘመናዊ ዘዴ ለማካሄድ መልካም ዕድል የሠጠ መሆኑን አስረድተዋል።
ቀደም ሲል በተካፋይ ገበሬዎቹ ስም አቶ በቀለ እሸቴ ባደረጉት ንግግር ውስጥ፤ “በከብት አርቢ ገበሬዎች መካከል አለመተማመንን አስወግዶ ለሥራ እንዲሠለፉ የሚያበረታታ የከብት አርቢዎች ማኅበር ለማቋቋም መታቀዱን ገልጠዋል። አቶ በቀለ ቀጥለውም ሲናገሩ ፤በኢትዮጵያ ውስጥ የመጀመሪያው የወተት ከብቶች ትርዒት ሲደረግ እኛም የዚሁ ትርዒት ተካፋይ ሆነን የድርጅቱን ድካምና ምኞት የተሟላ ለማድረግ የተቻለንን ያህል አቅርበን ዝግጅቱ በጥሩ ሁኔታ እንዲፈፀም በመጣራችን ውጤቱ ሊያምር ችሏል።” ካሉ በኋላ ፤ለመጀመሪያ ጊዜ የተዘጋጀው የወተት ከብቶች ውድድርና ትርዒት ላይ የተሳፉት ጥቂት ገበሬዎች መሆናቸውንና በአንዳንድ ምክንያትና እክል ለጊዜው ተካፋዮች ያልሆኑት አብዛኞቹ ገበሬዎች ፤ወደፊት እንደሚካፈሉ ያላቸውን ተስፋ ገልጠዋል።
የውድድሩና ትርዒቱ ዝግጅት ስላስገኘው ውጤት አቶ በቀለ አንስተው በተናገሩት ቃል “ይህ ዝግጅት ለእኛ ለከብት አርቢዎች መገናኛ መተዋወቂያ ፤ብዙም ትምህርት ልንገበይ የቻልንበት ዓደባባይ ከመሆኑም በላይ በርከት ያሉ የእርሻና የከብት እርባታ መሣሪያ ሻጮችና መድኃኒት ነጋዴዎች ፤እንዲሁም መኖ አቅራቢዎች ጋር ለመነጋገርና ብዙ ነገር ለመረዳት በመቻላችን ፤ትርዒቱን ያዘጋጁት የወተት ሀብት ልማት ባለሥልጣኖችንና ሹማምንቶችን ከልብ ልናመሰግን ይገባል።በኛ በከብት አርቢዎችና በወተት ሀብት ልማት ድርጅት መካከል ባለፈውም ጊዜ ጥሩ መግባባት ቢኖርም ፤ለወደፊቱ የበለጠ ተቀራርቦና ተመካክሮ አብሮ ለመሥራት ለሕዝቡም የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚቻልበት ደረጃ ለመድረስ ጊዜው ሩቅ አይደለም።” ብለዋል።
አቶ በቀለ በመጨረሻም ትርዒቱ በተለይም ሐኪሞችን ፤ነጋዴዎችን ከብት አርቢ ገበሬዎችን በአንድነት አገናኝቶ በሙያው ያላቸውን ዕውቀትና የሥራ ልምድ እንዲለዋወጡ በማብቃቱ ፤በዝግጅቱ የደከሙትን ሁሉ በከብት አርቢ ገበሬዎች ስም አመስግነዋል።
በ፳፭ ሳንቲም መዋጮ የተሠራው መንገድ ተመረቀ
ከመረዳጃ በቀር ለልማት ተብሎ በተጨማሪ የተዋጣው የ፳፭ ሳንቲም ክፍያ የተሠራው መንገድ ተመረቀ። መንገዱን ያሠራው በገፈርሳ ወረዳ ግዛት የሰፈረ ገነት የልማት ድርጅት ነው። ድርጅቱ የተቋቋመው በሰፈረ ገነት ዕድር ውስጥ ሲሆን ለልማት ተብሎ በተዋጣው ገንዘብ ተሠርቶ የተመረቀው ገንዘብ በሩፋኤል ቤተክርስቲያን አቅራቢያ ካለው መንገድ አንስቶ ወደ ህዝቡ መኖሪያ የሚደርስ ነው።
ይህም መንገድ ቀድሞ ለእግር ጉዞ እንኳ አስቸጋሪ እንደነበረና በክረምት ወራትም የማጡ ኃይል በሕዝብ ላይ ከባድ ጉዳት ይፈጥር እንደነበር አቶ ግርማ ሸንቁጤ የሰፈረ ገነት የልማትና ፀጥታ ድርጅት ሊቀ መንበር አስታወቁ።
በ፳፭ ሳንቲም የልማት መዋጮ አዲስ የተሠራው መንገድ ከ፱፻ ሜትር በላይ ርዝመት ሲኖረው ሊሠራ የቻለው፤ከልማት መዋጮ ከሠፈሩ አካባቢና ከሌሎች በጎ አድራጊዎች በተገኘው የገንዘብ እርዳታ ነው። በጠቅላላው መንገዱ ከ፬ ሺህ ብር በላይ ፈጅቷል። መንገዱ ተመርቆ የተከፈተው በቀኛዝማች ዘለቀ ይጥና የሰሜን ማዘጋጃ ቤት ረዳት ከንቲባ ነው። ይህም የኅብረት ሥራ ለቀሩት ወረዳዎች ሁሉ ታላቅ ምሳሌ መሆኑን ረዳት ከንቲባው በምረቃው ወቅት ገልጠዋል።
የምረቃው ሥነ ሥርዓት የተካሄደው ከትናንት በስቲያ ነው። በዚህም ወቅት በሥራው ተባባሪ በመሆን ልዩ ልዩ አገልግሎት ያበረከቱ ሰዎች ከረዳት ከንቲባው የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል።
የሰፈረ ገነት የልማትና የፀጥታ ጥበቃ ድርጅት አሁን ካሠራው ሌላ በተጨማሪ አራት አውራ መንገዶችን ከፍቶ ከዋና ዋና መንገዶች ጋር ለማገናኘት ዕቅድ እንዳለውና የ፳፭ ሳንቲም መዋጮ እንደቀጠለ መሆኑን አቶ ግርማ ገልጠው ፤አዲስ በተመረቀው መንገድ ሥራ ላይ ሴቶች ተካፋይ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ወደፊት የሚከፈቱ መንገዶች በጠቅላላው ፲ ሺህ ብር የሚጠጋ ገንዘብ የሚፈጁ ናቸው ተብሎ ተገምቷል።
በባቡር የሞቱት ፪ ፈረንጆች
ባለፈው በታህሳስ ፲፯ ቀን አቃቂ በሰቃ ላይ በባቡር ተገጭተው የሞቱት ሶስቱ ጣሊያኖች ለቁልቢ ገብርኤል ስዕለት ከሮማ ድረስ የመጡ መሆናቸው ተገለጠ።
በባቡሩ አደጋ የሞቱት ጣሊያኖች ሪንስቶ ማሪኒ ቶኒኖ እንዲዩ የተባሉ ናቸው። እንዲሁም ከነሱ ጋር ከሮማ ድረስ መጥቶ የነበረው ቶበሊ ማፊያ የተባለው በባቡሩ አደጋ በጠና ቆስሎ ሆስፒታል በመታከም ላይ ነው። ሶስቱ የውጪ ዜጋዎች ከአዲስ አበባ ባቡር ተሳፍረው ወደ ቁልቢ ገብርኤል ለመሔድ በጉዞ ላይ እንዳሉ አቃቂ ባቡር ስለቆመ አገር ለማየት ከመሬት ስለወረዱ በድንገት በባቡሩ ስለተገጩ ሁለቱ ወዲያው ሲሞቱ አንደኛው በጠና ቆስሎ በፖሊስ እርዳታ ለህክምና አዲስ አበባ ተመልሷል።
ጣሊያኖቹ ለስለት የሚሆን ልዩ ልዩ ዕቃዎች ሳይዙ እንዳልቀሩ ከሸዋ ፖሊስ የማስታወቂያ ክፍል የተሰማው ጭምጭምታ ይገልጣል።
የመብል ዘይት አስበልጠው የሸጡ ሁለት ሰዎች 300 ብር ተቀጡ
አዲስ አበባ (ኢ ኤ አ) የንግድ ኢንዱስትሪና ቱሪዝም ሚኒስቴር ያወጣውን የንግድ መመሪያ በመተላለፍ በአዲስ ከተማ ሁለት ነጋዴዎች የምግብ ዘይት ዋጋ አስበልጠው ሲሸጡ በመገኘታቸው እያንዳንዳቸው ሶስት መቶ ብር ትናንት ተቀጡ።
አቶ ተስፋዬ ምትኩ የተባሉ ነጋዴ አዲስ ከተማ ገበያ አዳራሽ ጎን ከሚገኘው የሸቀጣሸቀጥ መደብራቸው ውስጥ አንደኛው ደረጃ የሆነውን አንድ ሊትር የመብል ዘይት ፩ ብር ፺፭ ሳንቲም መሸጥ ሲገባቸው ዋጋ በመጨመር ፪ብር በመሸጣቸው እንዲሁም አቶአሊ ሐሰን የተባሉ አዲስ ከተማ ከድሮ በርበሬ ተራ አጠገብ ከሚገኘው የምግብ ሸቀጣሸቀጥ መሸጫ መደብር ውስጥ ሁለተኛ ደረጃ የሆነውን አንድ ሊትር የመብል ዘይት ፩ ብር ከ፹፭ ሳንቲም ሂሳብ መሸጥ ሲገባቸው ዋጋ በመጨመር ፩ ብር ከ፺ ሳንቲም ሲሸጡ በመገኘታቸው በሁለቱም ተከሳሾች ላይ ዐቃቤ ህግ አማካይነት የወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ትናንትና በዋለው ችሎት አንደኛ ወረዳ ፍርድ ቤት ቀርበው ለተደረገላቸው የእምነት ክህደት ጥያቄ ተከሳሾቹ አድራጎታቸውን ሳይሸሽጉ በማመናቸው እያንዳንዳቸው ሶስት ብር መቀጣታቸውን ከፍርድ ቤቱ የደረሰው ዜና አረጋግጧል።
በጋዜጣው ሪፖርተሮች
አዲስ ዘመን ግንቦት 16/2013 ዓ.ም