ድንበር ተሻጋሪ በጎ ፈቃደኝት ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ እየተለመደ የመጣ ተግባር ነው:: ነገር ግን የታሰበውን ያክል ወጣቶች ተሳትፎ እያደረጉበት አለመሆኑ ይነገራል:: በተለይ የኮቪድ 19 ወረርሽን ወደ አገሪቱ ከገባ በኋላ ወጣቶች በአካባቢያቸው ተደራጅተው አቅም ለሌላቸው ሰዎች ድጋፍ ማድረግ ጀምረዋል:: የተወሰኑት ደግሞ በማህበር በመደራጀት እውቅና አግኝተው ዘላቂ የሆኑ ስራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛሉ:: ለዛሬ መነሻውን ባህርዳር አድርጎ በተወሰኑ አማራ ክልል ከተሞች በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኘውን ድንበር የለሽ የበጎ አድራጎት ማህበር እንቃኛለን:: ከማህበሩ መስራችና ፕሬዚዳንት አቶ ከፍያለው እሸቴ ጋር ቆይታ አድርገናል:: መልካም ንባብ::
የማህሩ አመሰራረትና ያከናወናቸው ተግባራት
ማህበሩ የተመሰረተው ህዳር 15 ቀን በ2006 ዓ.ም ላይ ሲሆን በአሁን ወቅት ሰባተኛ ዓመቱን አክብሯል:: በወቅቱም የደም ልገሳ፣ በአካባቢ ፅዳትና በሌሎች በጎ ስራዎች ማሳለፍ ተችሏል:: ከሰባት ዓመት በፊት ማህበሩ ሲመሰረት መሪ ሃሳቡ የነበረው ‹‹በጎ እናስብ›› የሚል ነበር:: በዚህ ውስጥም ሰባት ዓላማዎችን ይዞ መንቀሳቀስ ጀመረ:: በጎ ፈቃደኝነትን ማስፋፋት፣ ሱሰኝነትን መከላከል፣ ንቁ ዜጎችን ማፍራት፣ ባህልና ወግን ማስጠበቅ፣ ፆታዊ ጥቃትን መከላከል፣ መተሳሰብና መረዳዳትን ማጎልበት እንዲሁም ሰላም ወዳድ ህብረተሰብ መፍጠር ናቸው:: ከላይ የተቀመጡትን በተለያዩ አጋጣሚዎች ወጣቶችን በማስተባበር በትርፍ ጊዜያቸው ማህበረሰቡን እንዲያገለግሉ እየተደረገ ይገኛል::
በጎ ፈቃደኝነትን ማስፋፋት ላይ የተሰራው ስራ ሲታይ ማህበሩ በተለያዩ ከተማዎች ስድስት ቅርንጫፎችን መክፈት ችሏል:: በመጀመሪያ ማህበሩ የተመሰረተው ባህርዳር ላይ ነበር:: አሁን በራያ ቆቦ፣ በቻግኒ፣ አዲስ ዘመን፣ ኮምቦልቻና ኮሶ በር ቅርንጫፎች ተከፍተው ከዋናው ማህበር ጋር ሲደመሩ ስድስት ቅርንጫፍ ሆነዋል:: በእያንዳንዱ ከተማ በተለያዩ በጎ ፈቃደኞች እየተስፋፉ የተለያዩ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ:: ከሱሰኝነት መከላል ጋር በተያያዘ በየትምህርት ቤቱ ግንዛቤ የመስጠት ስራ ይከናወናል:: ንቁ ዜጎችን ከማፍራት አንፃር ደግሞ በክረምት ወራት የሥነ ምግባር ትምህርት ይሰጣል:: በተጨማሪም በክረምት ወራት የትወና ትምህርትም ይሰጣል:: በዚህ ዓመት አስራ አንደኛውን ዙር ለማካሄድ ዝግጅት ተደርጓል:: በአስራ አንደኛ ዙር የደረሰው በተለያዩ ጊዜያት በዓመት ሁለት ጊዜ በመሰጠቱ ነው::
ባህልና ወግን ከማስቀጠል አንፃር እስካሁን ከተሰሩት ስራዎች ውስጥ ጎላ ያለ ነው ተብሎ የሚጠቀሰው ከባህርዳር በመነሳት ላሊበላ ድረስ የእግር ጉዞ ተደርጓል:: በእግር ጉዞው አካባቢው ሰላም መሆኑን ለማሳወቅ በተጨማሪም ደግሞ ቀደምት አባቶች ከሸዋ ተነስተው ጎጃምን አቅንተው ጎንደርን ወሎ ድረስ ይሄዱ ነበር:: የሚማፀኑት ለማህበረሰቡ ሲሆን የሚይዙት ስንቅ ብዙ አልነበረም ምክንያቱም በየሄዱበት ማህበረሰቡ ደግነት የተሞላበት በመሆኑ ያለውን እያካፈለ ይሸኛቸው ስለነበር ነው:: አሁን ግን ሁሉም በራሱ ጊቢ ውስጥ በመከለል አብሮ የመኖርና የመረዳዳት ባህል እየቀነሰ መጥቷል:: ከአካባቢዬ ውጣ ከሰፈሬ ውጣ ለመባባል ተደርሷል::
ይህ የተፈጠረው ቀድሞ የነበረውን ወግ ባለመከተል በመሆኑ ምክንያት በማህበሩ ውስጥ የሚገኙ ወጣቶች ተወያይተው ዘጠኝ ወጣቶች አስራ ሁለት ቀን የፈጀ ከባህርዳር ላሊበላ የእግር ጉዞ በማድረግ በላሊበላ የገና በዓልን ማክበር ተችሏል:: የተወሰኑ ወጣቶች በዓሉ ከመከበሩ በፊት ወደ ባህርዳር ተመልሰዋል:: ሌላው ደግሞ የባህላዊ አልባሳት የፎቶግራፍ ውድድር ተከናውኖ ነበር:: በማህበራዊ ሚዲያም በኩል ገፅ ተከፍቶ በባህላዊ ልብስ ፎቶ ተነስተው በመላክ ብዙ ላይክ ያገኘውንና በማህበሩ የውድድር ኮሚቴ የተመረጡ ሰዎች ሽልማት የተሸለሙበት ሁኔታም ነበር::
ከሴቶችና ህፃናት ጥቃት ጋር በተያያዘ የማስተማር ስራዎች ይከናወናሉ:: በአሁኑ ወቅት የሚሰሙ ነገሮች ከባድ እየሆኑ መጥተዋል:: ለምሳሌ መደፈርን ብንጠቅስ በሰለጠነ ዘመን ሴቶችንና ህፃናትን መድፈር እየተስፋፋ ይገኛል:: ባደጉ አገራትም ሁኔታው እየቀነሰ የመጣ ሲሆን በአገሪቱ ጎልቶ የሚታይ ክስተት ሆኗል:: በፆታዊ ጥቃት ትንኮሳው እየተባባሰ የመጣ ሲሆን ስለዚህም በየአካባቢው የማስተማር ስራው እየተከናወነ ነው:: በየትምርት ቤቱ መተሳሰብ መረዳዳት እንዲሁም ሌሎች ስራዎች ይከናወናሉ:: ማህበራዊነትን ማጎልበት የሚለው ዓላማ ደግሞ በዓላት ሲሆኑ ለምሳሌ ለትንሳኤ በዓል ለአረጋውያንና ለአቅመ ደካማዎች ዶሮ፣ ዘይትና ሽንኩርት ድጋፍ ተደርጎላቸዋል:: ለኢድ አልፈጥር በዓልም ከሙስሊም ማህበረሰቡ ጋር የኢፍጣር ፕሮግራሞች ተከናውነው ነበር:: በተደረገው ፕሮግራም ከእስልምና እምነት ውጪ ያሉ ሃይማኖት ተከታዮችም እንዲሳተፉበት ተደርጓል::
ከዚህ ውጪ ማህበሩ ድጋፍ የሚያደርግላቸው መቶ ህፃናት ያሉ ሲሆን በየዓመቱ የመማሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ እየተደረገላቸው ይገኛል:: መከባበርና መረዳዳትን የሚያጎለብቱ ስራዎችን ለማሳደግ ህፃናትን ብቻ መርዳትና መደገፍ በቂ አደለም:: ከፍተኛ ድጋፍ የሚፈልጉ ልጆችን በማህበሩ በኩል መርዳት ከተቻለ ሌሎች ሰዎች በራሳቸው ተነሳሽነት ሌሎች መደገፍ ይችላሉ ማለት ነው:: ለተማሪዎች የሚያስፈልገው ደብተር፣ ስክርቢቶና እርሳስ ከተጠበቀው በላይ ድጋፍ ሲገኝ በማህበሩ ላልታቀፉ ችግረኛ ህፃናት እንዲሰጥ ይደረጋል::
ሰላም ወዳደድ ማህበረሰብ ከመፍጠር በርካታ ስራዎች ተከናውነዋል:: ከነዚህም ውስጥ ህብረተሰቡ ያለምንም ምክንያት ወደ ግጭት የሚገባበት ሁኔታ እየተባባሰ መጥቷል:: ከሚመራው ይልቅ የሚነዳው ሰው በመብዛቱ ከዓላማው ውጪ የሆነ እንቅስቃሴ በሁሉም ህብረተሰብ ውስጥ እየታየ ነው:: ውጤታማና ፍሬያማ የሆነ ነገር ላይ ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን ሊያባክኑ እንደሚገባ የግንዛቤ ስራ ይሰራል:: ሰላም ወዳድ የሆነ ህብረተሰብ እንዲፈጠር ማህበሩ የተቻለውን ያክል እየሞከረ ነው:: በማህበራዊ ገፆች በተለይ በጎ ነገሮችን እናስብ በሚል በበጎ ፈቃደኞች አማካኝት ፎቶ በማንሳት ለህብረተሰቡ ግንዛቤ እንዲውል እየተደረገ ነው:: ማህበረሰቡ ሰላም ወዳድ እንዲሆንና ቀደምት ባህሎች እንዲቀጥሉ ማህበሩ ጥረት እያደረገ ነው::
የኮሮና ወረርሽኝ ከተከሰተ በኋላ ቤት ውስጥ ሆነው የተቸገሩ ሰዎችን ቤታቸው ድረስ በመሄድ ከበጎ ሰዎች የተሰበሰቡ እህሎችና ሌሎች መሰረታዊ ነገሮች ድጋፍ ተደርገዋል:: በሌላም በኩል በማህበሩ ውስጥ የሚገኙ በጎ ፈቃደኞች በጉልበት ለችግረኞች አስፈላጊ ስራዎችን ሲያከናውኑ ነበር:: ለምሳሌ ባህዳር ሙሉአለም የባህል ማእከል ላይ ህረተሰቡን ሊጠቅሙ የሚችሉ ስራዎች ይከናወኑ ነበር:: ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር በጋራ በመሆን የማስማር ስራዎች የተከናወኑ ሲሆን የፀረ ኮሮና ወረርሽኝ ዘመቻ በመውጣት ከቀይ መስቀልና ከመሰል ድርጅቶች ጋር በመተባበር ዘመቻዎች ተደርገዋል:: ‹‹እኔ እራሴን ከኮሮና እጠብቃለው›› የሚሉ ሃሳቦች በዘመቻው ወቅት ጎልተው እንዲወጡ ተደርጓል:: ከከተማ ወጣ ብለው በሚገኙ አካባቢዎች ስለ ኮሮና ወረርሽን በጭውውት መልኩ የማስተማር ስራዎች ይሰራሉ::
በሌላ ወቅታዊ ስራ ደግሞ የእንቦጭ አረምን ከጣና ሀይቅ ላይ ለማፅዳት በተደረገው ዘመቻ ክፉ ሃሳቦችን ከአዕምሮ በማውጣት እንቦጭን ከጣና እናስወግድ የሚል ሃሳብ ተይዞ በተኬደበት ሁሉ በጎ ስራዎችን በማሳየት ማህበረሰቡ ላይ ጥሩ አመለካከት ለመትከል እየተሞከረ ስራዎች እየተሰሩ ናቸው:: በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የተፈናቀሉ ሰዎችን ቦታው ድረስ በመሄድ የመደገፍ ስራም ተከናውኗል:: በመጀመሪያው ዙር አንድ ሺህ የሳሙና ድጋፍ ተደርጓል:: በሁለተኛው ዙር ደግሞ ምግብ ማብሰያ የሆኑ እንደ ብረት ድስትና ብረት ምጣድ ተገዝቶ እንዲሰጣቸው ተደርጓል:: በሶስተኛው ዙር ደግሞ እህልና ለህፃናት የሚሆኑ አልሚ ምግቦች እንዲሁም አልባሳት ድጋፍ ተደርጓል:: አሁን በቅርቡ በአጣዬ ከተማ የተፈናቀሉ ሰዎችን ለመደገፍ አልባሳት ተልኮ በአካባቢው በሚገኙት ማህበራት አማካኝነት እንዲሰጥ ተደርጓል::
የህብረተሰቡ አቀባበል
የህብረተሰቡ አቀባበል በፊት የነበረውና አሁን ያለው በጣም ልዩነት አለው:: በፊት የነበረው ሁሉም ሙሉ ጊዜውን ሰጥቶ የሚሰራው ስራ አልነበረም:: ፕሮጀክቶች በመንደፍና የተለያዩ ሃሳቦችን በማምጣት የተወሰኑ ሰዎች ነበር የሚሳተፉት:: ሌላው የትኛውም ስራ ላይ ከሰው ምንም የሚጠበቅ ነገር አልነበረም:: ማህበሩ ወደ ስራ ሲገባ የመጀመሪያ ተግባሩ የነበረው የደም ልገሳ ማድረግ ነበር:: በወቅቱ በማህበሩ ውስጥ የሚገኙ አባላት ደማቸውን እንዲሰጡ ተደርጎ ነበር:: ይህን ሁኔታ በማሳደግ የተወሰነ ገንዘብ በማዋጣት የተቸገሩ ወገኖችን ምግብ የማብላት ስራ ተጀመረ:: እነዚህን ስራዎች ህብረተሰቡ ሲመለከት ወደ ማህበሩ መቀላቀል ጀመረ:: በተጨማሪም ዝግጅቶች ሲኖሩ የገንዘብ ድጋፍ ከህብረተሰቡ ማግኘት ተቻለ::
የተለያዩ በጎ ስራዎች ሲጀመሩ ህብረተሰቡ በመምከርና ድጋፍ በማድረግ ከማህበሩ ጎን እየሆነ መጣ የማህበረሰቡ አቀባበል በተለይ አሁን ያለው ሁኔታ አበረታች ነው:: በሌላ በኩል ማህበሩ በሚሰራቸው ስራዎች ትልልቅ ድርጅቶች ትኩረት እያደረጉ መጥተዋል:: የተለያዩ ሽልማቶች ከጣና አዋርድ፣ ከባህርዳር ከተማ አስተዳደርና አማራ ክልልን በመወከል ማህበሩ በፌዴራል ደረጃ እውቅና ማግኘት ችሏል::
ያጋጠሙ ችግሮች
ማህበሩ ተመስርቶ ወደ ስራ ከገባ በኋላ ለአራት ዓመታት ያክል ማህበሩ ቢሮ አልነበረውም:: ምክንያቱም በተለያዩ ስራዎች ለማከናወን በተለያዩ ቦታዎች ላይ በመሰባሰብ ውይይት ተደርጎ መዋጣት ያለበት ገንዘብ እንዲዋጣ ይደረግ ነበር:: ከህብረተሰቡ መጠየቅ የሚገቡ ነገሮች ካሉ በመጠየቅ ወደ ስራ ይገባ ነበር:: ከዛም ቢሮ እንዲሰጥ ሁለት ሶስት ቦታዎች ላይ ጥያቄ ቀርቦ ነበር:: ለበጎ አድራጎት ስራ የሚሰጠው ትኩረት አናሳ ስለነበር ሰዉ በአግባቡ ስራው የሚሰራ አይመስለውም ነበር:: አንዳንዱ ደግሞ ከተጠቃሚነት ጋር አያይዞ የሚኮንንበት ሁኔታም ነበር:: አንዳንድ ሰው ደግሞ የፖለቲካ ዓላማ ያለው አድርጎ ያስበው ነበር::
በጎ አድራት ማህበሩን የመሰረቱ በጎ ፈቃደኞች ከፖለቲካ ገለልተኞች ናቸው:: የበጎ አገልግሎት ስራው ፈቃድ ሲሰጥ ከሃይማኖትና ከፖለቲካ ውጪ እንቅስቃሴ እንዲያደርግ ታስቦ ነው:: ለምሳሌ ማህበሩ በየሳምንቱ ከተማውን የማፅዳት ስራዎች ያከናውን ነበር:: በዚህም የመንግስት በዓላት በመጡ ቁጥር ከተማውን ማህበሩ እንዲያፀዳ ጥሪ ይቀርብ ነበር:: ይህ ሁኔታ ምቾት የሚነሳ ነገር ነበር:: የበጎ አድራት ማህበሩን ፈቃድ በክልል ደረጃ ከሆነ በኋላ ነገሮች እየተስተካከሉ መጥተዋል:: ሌላው የበጎ ፈቃደኞች ወሰን የሚባለው ሲሆን የማህበረሰቡ የግንዛቤ ክፍተት ችግር ፈጥሮ ነበር::
የማህበሩ ቀጣይ እቅድ
ማህበሩ ባከናወናቸው ተግባራት ጥሩ መሰረት ይዟል ተብሎ ይታሰባል:: የተወሰኑ የማህበሩ መስራቾች በአሁኑ ወቅት ከኢትዮጵያ ውጪ ነው የሚገኙት:: በውጭ አገራት ለማህበሩ ድጋፍ እንዲደረግ የማስተባበር ስራ እያከናወኑ ይገኛሉ:: በቀጣይ ሰፋ ያለ ሃሳብ በማሰብ ስራዎችን ለመስራት ታቅዷል:: ንቁ ዜጋን ከማፍራት አንፃር አነስተኛ ቤተ መፅሀፍ እንዲከፈት ተደርጓል:: ይህ ቤተ መፅሀፍ ሰው መጥቶ እዛው እንዲነብ ብቻ ሳይሆን መፅሀፍ ተውሶ አንብቦ እንዲመልስና ሌሎች መፅፎችን እንዲቀይር እየተደረገ ነው:: በጎ ሰዎችም መፅሀፍ ገዝተው እየሰጡ ናቸው:: ይህን ስራ ለማስፋት ታስቧል:: ወጣቱ አንባቢና ንቁ እንዲሆን የንባብ ልምድ መዳበር አለበት:: ችግሮች እየተፈጠሩ ያሉት ካለማንበብና ከለመንቃት በመሆኑ ነው::
ቁንፅል ሃሳቦችንና መረጃዎችን ተይዞ አላግባብ በሆኑ ቦታዎች መነዳቶች ይታያሉ:: ስለሆነም ቅድሚያ በአስተሳሰብ ላይ መሰራት አለበት በሚል እቅዶች ተይዘዋል:: ሌላው ደግሞ የማህበሩን ቅርንጫፍ ቁጥር ወደ አስር ለማሳደግ እቅድ አለ:: በአሁኑ ወቅት ለመክፈት የተጀመሩ ያሉ ሲሆን በደብረ ብርሃን፣ በደብረ ታቦር፣ ደብረ ማርቆስና ፍኖተ ሰላም ቅርንጫፍ ለመክፈት ስራዎች ተጀምረዋል::
መርድ ክፍሉ
አዲስ ዘመን ግንቦት 13/2013