ሀገራችን ያለችበት አጣብቂኝ ብዙ ተስፋዎች ያሉባት ሀገር ባትሆን ኖሮ ነገሮች ይበልጥ አስቸጋሪ ሊሆኑ እንደሚችሉ መገመት አይከብድም። ችግሮቹ አይደለም አንዲህ ተሰባስበው መጥተው ለየብቻቸውም ፈታኝ ናቸው። በትግራይ ክልል ሲካሄድ ሲከናወን የቆየውና እየተከናወነ ያለው ተግባር ሲባዛ ግዙፍ ነው። ከታላቁ የህዳሴ ግድብ ሁለተኛ ዙር የውሃ ሙሌት ጋር በተያያዘ ግብፅና ሱዳን የያዙት አጀንዳ በሀገር ውስጥም በውጭ ሀገርም ብዙ መሥራትን የሚጠይቅ ነው። ግብፅ በሀገራችን ጠንካራ መንግሥት እንዲኖር ፈልጋም አታውቅም። ዘንድሮም ጠንካራ መንግሥት እንዳይኖር እየሠራች ትገኛለች።
ዴሞክራሲያዊ ስርዓት መሰረት ይሆናል ተብሎ የታመነበትን ምርጫ ለማስተጓጎል ጭምር እየሠራት ትገኛለች፤ ሱዳን የኢትዮጵያን ድንበር አልፋ መሬታችንን በወረራ ይዛለች። አሁንም እዚህም እዚያም የንጹሐን ዜጎችን ህይወት እየቀጠፉ ያሉ ሌሎች ፈተናዎችም አሉ። በእዚህ ላይ የኑሮ ውድነቱ ትልቅ ራስ ምታት ሆኗል። እነዚህ ፈተናዎች ሲታሰቡ በእርግጥም ምን መአት ነው የመጣብን ያሰኛሉ። ሀገራችን ግን በእነዚህ ፈተናዎች ብቻ የተወጠረች አይደለችም። የተስፋም ምድር ናት፤ ለዚያውም በቅርቡ ሊጨበጡ የሚችሉ ተስፋዎች ያሉባት። የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የመሰረተ ልማት፣ የኢንዱስትሪ፣ የኢንቨስትመንት፣ የቱሪዝም፣ የቤቶች ልማት፣ ወዘተ ፕሮጀክቶች የተካሄዱባትና እየተካሄዱባት የምትገኝ ናት።
የዳቦ ስንዴ ከውጭ ማስመጣት አንገፍግፏት ስንዴ በስፋት ማምረት ውስጥ ገብታለች። ለእዚህ ደግሞ ከተለመደው የስንዴ አመራረት ወጣ በማለት በመስኖ ስንዴ ማልማት ውስጥ ከገባች ሁለት ዓመታት ሞልቷታል። ይሄ በሀገራችን ግብርና ውስጥ ትልቅ ለውጥ ነው። የዚህን የግብርና ዘይቤ ምርት ዳቦ ለመብላትም በቅተናል። ይህ አዲስ ክስተት ነው፤ ለመስኖ የሚውሉ ወንዞች በብዛት ያሉባት እንደመሆኗ በቀጣይ የት ልትደርስ እንደምትችል መገመት አይከብድም።
በቱሪዝም ዘርፍ ትልቅ እምርታን የሚያስገኙት፣ የአዲስ አበባን ገጽታ በወሳኝ መልኩ መቀየር የሚችሉት የአንድነት፣ የወዳጅነትና የእንጦጦ ፓርኮች እንደመና የወረዱ አይደሉም፤ ተሠርተው ለአዚያውም ሌት ተቀን ክትትልና ቁጥጥር ተደርጎባቸው የተገኙ ናቸው። እነዚህ ግንባታዎች በቀጣይ ለሀገሪቱ ከፍተኛ ገቢ የሚያስገኙ እና የሥራ ዕድልም የሚፈጥሩ ናቸው።
እዚህ ላይ በተገኘው ትንፋሽ በመጠቀም ሌሎች ሦስት ግዙፍ የቱሪዝም መስህብ ስፍራዎች ግንባታም በኮይሻ፣ በወንጪ እና በጎርጎራ እየተካሄዱ ይገኛሉ። የዋሆች ያለው የሚዝናናባቸው ናቸው እያሉ ያጣጥሏቸዋል። ፕሮጀክቶቹ ወደ ሥራ ሲገቡ የቱሪዝሙ ዘርፍ ከፍተኛ መጠን ያለው ሀብት እንዲያመነጭ የሚያስችሉ ናቸው። ከዚህ በሚገኝ ሀብት ሀገርና ህዝብ ሌሎች የልማት ሥራዎችን ይሠራሉ።
በአዲስ አበባና ዙሪያዋ ተማሪዎችን ዩኒፎርም በማልበስ፣ የምግብ አገልግሎት በማቅረብ እየተከናወነ ያለው ሥራ ስንት ቤት እንደሚደርስ ማሰብ ነው። የሚመገቡት አጥተው ባዶ ሆዳቸውን ትምህርት ቤት ይውሉ የነበሩ የከተማዋ አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ይወድቁ የነበረበትን ሁኔታ አስታውሳለሁ። አንዳንዶቹም ጠዋት ተምረው ረፈድ ሲል ምግብ ፍለጋ ይሄዱ እንደነበርም በሥራ አጋጣሚ ሰምቻለሁ። የምግብ አቅርቦቱ እንዴት ያሉ ችግሮችን እየፈታ ስለመሆኑ ይህ አንድ ጥሩ ማሳያ ተደርጎ ሊወሰድ ይገባል።
በከተማዋ በቅርቡ ከእጅ ወደ አፍ በሆነ ዝቅተኛ ኑሮ እየተፍጨረጨሩ ለሚኖሩ እና ገቢያቸውም አብዛኛው የቤት ኪራይ ወጪ ለሚወስድባቸው ሰዎች የቀበሌ መኖሪያ ቤቶች ተሰጥቷቸዋል። አንድ ክፍለ ከተማ ላይ ብቻ ከ100 ቤቶች በላይ ለችግረኞች ሲሰጡ በመገናኛ ብዙሃን አይቻለሁ። ተመሳሳይ ሥራ በሌላም ክፍለ ከተማ መደረጉን የሰማሁ መሰለኝ።
ከዚህ አንጻር አሁንም ብዙ ሥራዎች ይቀራሉ። አሁንም የደረሳቸውን ኮንዶሚኒየም ቤት እያከራዩ በቀበሌ ቤት ውስጥ የሚኖሩ አሉ፤ የቀበሌ ቤት ዕድለኛ ያደረጋቸው ምርጥ ምርጥ ሕንፃ ያላቸው ሰዎች የቀበሌ ቤቱን ለዘመድ ሰጥተውታል። የከተማ አስተዳደሩ ባለስልጣናት በነካካ እጃችሁ እነዚህንም ድረሱባቸውና ቤቶቹን ለተቸገሩ መስጠታችሁን ቀጥሉ።
በኑሮ በእጅጉ ፈተና ለሆነባቸው የከተማ ነዋሪዎች የከተማዋ አስተዳደር ከአጋር አካላት ጋር በመሆን በተለያዩ አካባቢዎች የመመገቢያ ቦታዎች ተከፍተው የምግብ አገልግሎት ሲያቀርቡ አይቻለሁ፤ ይሄም ጅማሬው የሚደነቅ መሆኑን ማሰብ ይገባል።
በአዲስ አበባ የሸገር ዳቦ ፋብሪካ ግንባታ ሲጀመር የብዙዎችን ቀልብ መሳቡ ይታወሳል፤ ፋብሪካው ተመርቆ ሥራ ሲጀምር የኤሌክትሪክና የመሳሰሉት ችግሮች ቢኖሩበትም የሚጠበቅበትን ያህል ባይሆንም ዳቦ እያቀረበ ይገኛል። ስንዴ ማግኘት ከባድ በሆነበትና ሌሎች በርካታ ዳቦ ቤቶች ከሚጠበቀው ግራም በታች የሆነ ዳቦ በአራት ብር እያቀረቡ ባለበት በዚህ ዘመን በአንድ ብር ዳቦ እያቀረበ ያለበት ሁኔታ ስንቶችን ከረሀብ ሊታደግ እንደሚችል መገመት አይከብድም።
የከተማዋን ትራንስፖርት አገልግሎት ችግር ለመፍታት የሸገር ድጋፍ ሰጪ አውቶቡሶችን በማሰማራት የተከናወነው ተግባር መጠቀስ ያለበት ነው።
እዚህ ሁሉንም መጥቀስ አይቻልም። የሐገሪቱ ጠላቶች እነዚህን ሁሉ ሥራዎች እንደሌሉ አድርገው በመቁጠር ላይ ናቸው፤ ከዚህ ይልቅ ፈተና መስጠት ላይ ተጠምደዋል። ቢያንስ አርጩሜም ገድ አለው ብለው እንኳ አያውቁም። ይሄ መንግሥት መጥፎ ነው፤ ነገር ግን እዚህ እዚህ ጋ ጥሩ ሥራዎች አሉ ማለት የሚፈለጉ አይደሉም። እስከ አሁን የመጡበትን ነገር ስንመለከት መገመት እና መጠርጠር የምንችለውም ይህንኑ ነው። ምክንያቱም ጭር ሲል አይወዱም ፤ጭር ካለ የሚበሉም ይመስላቸዋል። ሥራቸው ያውጣቸው።
እኛ ግን ማድረግ ያለብንን ማድረግ አለብን ነው። ከእነሱ ጋር እየተፋልምን በልማቱ ተዋናይ ፣አጋር ፣ባለቤት፣ ገንቢም አስገንቢም ሆነን መቀጠል አልብን። ለእዚህ ደግሞ እንደ እስከ አሁኑ ሁሉ ለፈተናዎች እጅ ሳንሰጥ የመንግሥትን የልማት የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ለማሳካት በንቃት መሳተፍ ይኖርብናል።
በልማቱ በመሳተፍ ከምናደርገው ርብርብ ጎን ለጎን ለተካሄደውና እየተካሄደ ላለው ልማት እውቅና መስጠትና ምስጋና ማቅረብ ይኖርብናል። እስከ አሁን ባለው ሁኔታ ሲወርድ ሲዋረድ አብሮን የመጣውን የምስጋና ባህል እዚህ ላይ ልንጠቀምበት አልቻልንም። ከዚህ መውጣት አለብን። ስናመሰግን እና እውቅና ስንሰጥ ተመሰጋኙ ይበልጥ ተበራታትቶ ይሠራል፤ሌሎችም እሱን ይቀዳሉ።
አንዳንዶች የምን እውቅናና ምስጋና ነው፤ሊሠራ ነው የተቀመጠው ፤ የመደበኛ ሥራው አካል ነው በቃ ሲሉ ይደመጣል። ሊሠራ ተቀምጦ የነበረ ብዙ ባለስልጣን እያየን መጥተናል፤ ለራሱ እንጂ ለህዝብ ምን ሠርቶ ነበር ብለን እስቲ እንጠይቅ። ራሳቸውን ቡድናቸውን ከመጠቀም ውጪ ለይስሙላ ካልሆነ በቀር ሀገርና ህዝብ የጠቀሙ መሪዎች አልነበሩንም። አሁን የሠራ ሲገኝ ለሥራዎቹ እውቅና መስጠትና ማመስገን ይኖርብናል። የምስጋና ባህላችንን ከቆልፍንበት አውጥተን መጠቀም ይኖርብናል።
ምስጋናው ሲያንስ ወይም ሳይኖር ሲቀር ቀደም ሲል በጎ ሥራዎች ሲጀመሩ የማመስገን ባህላችን ሠፊ ነበረ፤ዛሬ የማመስገን ባህላችንን ማን ወሰደብን እላለሁ፤ ለራሴ። ከነጉድለታቸውም ቢሆን መልካም ሥራዎች መሠራታቸውን መቀበል ብቻ ሳይሆን ማመስገን ይገባናል። መልካም ሥራዎች ሲጀመሩ ስናበረታታ የሠራው አካል ከዚህ የበለጠ መሥራት አለብኝ ብሎ እንዲነሳሳ ያስችለዋል። ሌሎችም የእሱን ሥራ ዓይተው ለመሥራት ይነቃቃሉ። በመሆኑም የማመስገን ባህላችንን ከገባበት እናውጣና የሠሩ ሥራዎችን ለማመስገንና እውቅና ለመስጠት ተግባር እናውለው።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ግንቦት 10/2013