የዝግጅት ክፍላችን እሁድ እሁድ ይዞት ብቅ በሚለው ሳምንቱን በታሪኩ አምድ በሀገራችን በዘመን ትዝታ ውስጥ ጉልህ ስፍራ ያላቸውን ታሪኮች ይዞ ይቀርባል። ደጋግመን ብንከትባቸው እንኳ ልንማርባቸው እንጂ ሊሰለቹን የማይችሉ በርካታ ክስተቶች በታሪክ ውስጥ ተመዘግበው ይገኛሉ። በየአመቱ ብናሞግሳቸው ቢያንስባቸው እንጂ የማይበዛባቸው ታላላቅ የአገር ባለውለታዎች ሞልተዋል። ለዚህም ነው የታሪክ ዶሴዎችን በየሳምንቱ እየገለጥን ወደእናንተ አንባቢዎቻችን ፊት ልናቀርባቸው የወደድነው።
ሳምንቱ በተለያዩ የዓለማችን ክፍለ አገራት ታላላቅ ታሪኮች የተከሰተበት ነው፡፡ ይህ እውነት በኢትዮጵያ ውስጥም ተመሳሳይ ነው። በተለይ በያዝነው የግንቦት ወር አያሌ ሊታወሱ የሚገቡ የታሪክ አንኳሮች እጅግ ብዙ ናቸው። ከእነዚህ ሁነቶቹና ታሪካዊ ክስተቶች መካከል ለዛሬ በደርግ ዘመነ መንግስት የተሴረና ሳይሳካ የቀረ በዚህም ሳቢያ የበርካታ ሰዎችን ህይወት የቀጠፈ “መፈንቅለ መንግስት” እና ከእርሱ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን ለማጥራት የተፃፉ አስተያየቶችንና የአይን ምስክሮች ያሏቸውን ይዘንላችሁ ቀርበናል። ለዛሬ ሚዛን ደፍቶ ያገኘነው ስለጉዳዩ ከተፃፉ ፅሁፎች ውስጥ በቢቢሲ አማርኛ የዜና ማሰራጫ ይፋ የሆነ ትንታኔ ነው። በመሆኑም በዋናነት ምንጫችንን በዚህ ሰፋ ያለ ዘገባ ላይ ለማድረግ ወደናል።
የ1980 ዓ.ም መፈንቅለ መንግስት ለምን?
በወቅቱ የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት የነበሩት ጓድ ሊቀመንበር መንግስቱ ሀይለማርያም ምሥራቅ ጀርመንን ለመጎብኘት ከባለቤታቸው ክብርት ወ/ሮ ውባንቺ ቢሻውንና ልጃቸውን ትዕግስት መንግስቱን (ወይም ትምህርትን) አስከትለው፣ በትረ መኮንናቸውን እየወዘወዙ ቦሌ ተገኙ። ረፋድ ላይ። መንጌ ቆቅ ናቸው። ሆን ብለው ሰዓት ያዛባሉ። ጠላትን ለማወናበድ ወይ ረፈድ ወይ ቀደም ይላሉ። እርሳቸው ላይ የሚዶልተው ብዙ ነዋ። ያን ለታም እንዲሁ አደረጉ። ማልጄ ነው የምበረው ብለው ለደኅንነት ሚኒስትራቸው ተናገሩ። ሚኒስትሮቻቸውም እውነት መስሏቸው ቦሌ ማልደው ደረሱ። እርሳቸው ግን ረፋድ ላይ ግንባራቸውን ቅጭም አድርገው ከቸች … አሉ።
ብዙዎቹ ጄኔራሎች እስከዚያች ሰዓት ድረስ ይቁነጠነጡ ነበር። ቶሎ ወደ ቢሮ መመለስ አለባቸዋ። አጣዳፊ ሥራ ነው የሚጠብቃቸው። መንጌን ወደ ‘መንግሥተ ሰማይ’ ልኮ መሬት ላይ አዲስ መንግሥት የማቆም ብርቱ ሥራ አለባቸው።ጄኔራሎቹ ጦርነት ታክቷቸዋል። በመንጌ “ቆራጥ” አብዮታዊ አመራር ሺህ የድሀ ልጆችን መማገድ አንገሽግሿቸዋል፤ በአፋቤቴ፣ በቀይ ኮከብ፣ በባሕረነጋሽ ዘመቻ…አሥር ሺህዎች እንደ ቅጠል ረግፈዋል። ጀነራሎቹ ‘ጦርነትን እንደ ሥራ የያዘ መንግሥት ሕዝብ ሊመራ እንዴት ይቻለዋል?’ ሲሉ ነበር ድምጻቸውን ዝግ አድርገው የሚያጉረመርሙት።
መንግሥቱ ይሄን ማጉረምረም ከሰሙ ጄኔራሎቹን አይምሯቸውም። ማዕረጋቸውን በመቀስ ቆርጠው ሊጥሉት፤ ግንባራቸውን በሽጉጥ ሊነድሉት ይችላሉ፤ አድርገውታልም። የናደው ዕዝ ዋና አዛዥ ብርጋዲየር ጄኔራል ታሪኩ ዓይኔን፣ አሳዛኝ ፍጻሜን የሰማ ከመንጌ ጋር አይቀልድም።፡የአገሪቱ ምጣኔ ሐብት ደቋል፣ ሕዝብ ተርቧል፤ ወታደሩ ኮቾሮ እየበላ ነው የሚዋጋው። የገዛ ልጁንና ሚስቱን እንኳ ማየት አይፈቀድለትም። ጄኔራሎቹ ‘የገዛ ወገናችንን ትርጉም በሌለው ጦርነት ለምን እናስጨርሳለን?’፣ ‘ደግሞስ የሰሜኑ ችግር በፖለቲካ እንጂ በአፈሙዝ ይፈታል እንዴ?’…እያሉ ያጉረመርሙ ነበር፤…መንጌ ሳይሰሙ።
ኮ/ል መንግሥቱ ግን ሁሉም ነገር ወደ ጦር ግንባር እያሉ ጦርነቱን ገፉበት። በዚያ ላይ ከጦር አዛዦቻቸው ይልቅ ካድሬዎቻቸውን ማመን አበዙ። “ይሄ ሰውዬ እኛን የማይሰማ ከሆነ ለምን አናስወግደውም?” አሉ…ጄኔራሎቹ፤ ማንም ሳይሰማቸው።መፈንቅለ መንግሥት ለማካሄድ ዝግጅት ተጧጧፈ። ለዚያ ነው ግንቦት 8 ቀን 1980 ዓ.ም መንጌን ቶሎ መሸኘት የነበረባቸው…፤
ከሻዕቢያ ጋር ቶሎ ለድርድር መቀመጥ ያሻል። ይሄን የውጭውን ሽርጉድ፣ ገና ድሮ መንጌን የከዱት ሻለቃዳዊት ወ/ጊዮርጊስ አሰናድተውታል። ጄኔራሎቹ የመንጌን ወደ ምሥራቅ ጀርመን መሸኘት…ይቅርታ የመንጌን እስከወዲያኛው መሸኘት በጉጉት እየጠበቁ ያሉት ለዚሁ ነው።
ልክ የዛሬ 31 ዓመት፤ ግንቦት 8፤ ረፋድ ላይ
ሰዓቱ አልገፋ አለ… ወግ ነውና…መሪን መሸኘት… “ጓድ ሊቀመንበር በሰላም (አ)ይመልስዎ” እያሉ ቀኝ-ወ-ግራ ተሰይመው ተሰናበቷቸው፤ የገዛ ጄኔራሎቻቸው። መንጌ ያቺን ተወርዋሪ ኮከብ የመሰለች ፈገግታቸውን ቦግ እልም እያደረጉ አጸፋውን መለሱ። ለምን ይሆን ግን ፈጣሪ ለአምባገነኖች ችምችም ያለ፣ የተፈለፈለ በቆሎ የሚመስል ጥርስና ረዥም ዕድሜን የሚቸረው?
የሚደንቀው ታዲያ…በዚያች ዕለት የቦሌ ሽኝት ጄኔራል መርዕድ ንጉሤ አልተገኙም። ይሄ ቀላል ፕሮቶኮሏዊ ህጸጽ ተብሎ ሊታለፍ ይችላል። ጊዜ አጥተው ነው ሊባልላቸውም ይችላል…። ምክንያቱም ዘመኑ የጥድፊያ ነዋ…የጦርነት። በየግንባሩ ‹‹ገንጣይ-አስገንጣይን›› ለመፋለም የወገን ጦር ከሺህ “የወንበዴው ጦር” ጋር ተናንቆ እየተዋደቀ ነው። ፈንጂ እየረገጠ ነው…በእንዲህ ያለ ቀውጢ ጊዜ ለሽኝት መኳኳል ቅንጦት ሊሆን ይችላል። ቢኾንም…ጄኔራሉ ደግ አልሠሩም።
“መርዕድ ምነው ቀረ? ምንስ ብርቱ ጉዳይ ቢገጥመው፣ ቆራጡን መሪያችንን መሸኘት አልነበረበትም?” የምትል የስናፍጭ ቅንጣት ታህል ጥርጣሬ ሳይገባቸው አልቀረም፤ የደኅንነት ሹሙን፤ ኮ/ል ተስፋዬ ወልደሥላሴን…። ኢታማዦር ሹሙ ደግ አልሠሩም፤ እንደምንም ብለው አለቃቸውን መሸኘት ነበረባቸው። እርሳቸው በተቃራኒው መከላከያ ሚኒስቴር ውስጥ፣ ከኢትዮጵያ ሆቴል ፊት ለፊት፣ ከአምባሳደር ሲኒማ ጎን፣ ከቢሯቸው ቁጭ ብለው የክፍለ ዘመኑን አስገራሚ የስዒረ መንግሥት ‘ተውኔት’ እየጻፉ ነበር።
ከጦላይ የመጣው ሠራዊት
መፈንቅለ መንግሥቱን ለማቅናት ከአሥመራ በጄ/ል ቁምላቸው እየተመራ አዲስ አበባ ከገባው ኃይል ሌላ ከጦላይም አንድ ሻለቃ ተንቀሳቅሷል።
ጄኔራል ውበቱ ፀጋዬ ከሴረኞቹ ጋር በስሱም ቢሆን ሳይመሳጠሩ አልቀሩም። አሁንም ድረስ በሕይወት አሉ፤ አሜሪካ አገር። ወደ አዲስ አበባ የሚላከውን ጦር አዘጋጅተው እሳቸው ከሰሜን ኮሪያ የመጣ ልኡካን ቡድንን ተቀብለው እያነጋገሩ ነበር።
ጦላይ ያለው ልዩ ኮማንዶ የቁልምጫ ስሙ ”ስፖርታ” ይባላል። ሰሜን ኮሪያዎች ለከተማ ውጊያ፣ ለጨበጣ ፍልሚያ በልዩ ጥንቃቄ ያሰለጠኑት ጦር ነው።
ጄ/ል ውበቱ ጥርት ያለ መመሪያ ባይደርሳቸውም 150 የሚሆኑትን ምርጥ ምልምሎች በወታደራዊ ሄሊኮፕተር ወደ አዲስ አበባ ላኳቸው። ፖስታ ቤት መገናኛ ሚኒስትር አካባቢ በሚገኝ ሜዳ ላይ ሆነው ትዕዛዝ እንዲጠባበቁ ተደረጉ። ኋላ ላይ 4ኛ ክፍለ ጦር…
የመከላከያ ሚኒስትሩ መገደል
የደኅንነት ሚኒስትሩ ተስፋዬ ወ/ሥላሴ ሴራ ሸትቷቸዋል፤ ባምቢስ ከሚገኘው የደኅንነት ቢሯቸው እየበረሩ ወደ ምኒልክ ቤተ መንግሥት ነዱ። የመንጌን ልዩ ረዳት መንግሥቱ ገመቹን ጠርተው አስቸኳይ ስብሰባ ጀመሩ። እነ ፍቅረሥላሴ ወግደረስም አሉበት። እንዲያውም ሰብሳቢው እርሳቸው ናቸው።
ምንድነው እየሆነ ያለው? እነ መርእድ ምንድነው እየዶለቱ ያሉት?
የደኅንነት ሚኒስትሩ ተስፋዬ ወ/ሥላሴ
መከላከያ ሚኒስትሩን ጄኔራል ኃብተጊዮርጊስን ጠርተው፣ ለመሆኑ በቢሮህ ምን እየተካሄደ እንደሆነ ታውቃለህ? ብለው ጠየቁ። ‹‹አረ በፍጹም›› አሉ ሚኒስትሩ። ሄደው እንዲያጣሩ ሐሳብ ቀረበ። በሄዱበት ይቀራሉ ያለ አልነበረም። ሚኒስትሩ ቁልቁል ወደ አምባሳደር በረሩ። ወደ ቢሯቸው ገብተው ወጡ።
ጄ/ል ኃብተጊዮርጊስ ወትሮም ከጄ/ል አበራ ጋር እስከዚህም ናቸው። እረ እንዲያውም ዐይንና ናጫ…። ጄ/ል አበራ የሆነ የቀፈፋቸው ነገር ያለ ይመስላል። ጄ/ል መርዕድ ከሚመሩት ስብሰባ በየመሀሉ እየወጡ ኮሪደሩን፣ አካባቢውን ይቃኙና ይመለሳሉ። ድንገት ለቅኝት ደረጃውን ሲወርዱ፣ መከላከያ ሚኒስትሩ ደግሞ ደረጃውን ሲወጡ ተገጣጠሙ።
“አበራ! ምንድነው እኔ የማላውቀው ስብሰባ?” ሳይሉ አልቀሩም። መከላከያ ሚኒስትሩ፡፡ አንድ ሁለት ተባብለውም ሊሆን ይችላል። ብቻ ጄኔራል አበራ በቅልጥፍና ሽጉጣቸውን አውጥተው መከላከያ ሚኒስትሩ ላይ አከታትለው ተኮሱ። ጦር ኃይሎች ቢወሰዱም አልተረፉም።
ጄኔራሎቹ ራሳቸውን ለምን አጠፉ?
ግንቦት ስምንት ቀትር ስምንት ሰዓት ግድም የጀመረው መፈንቅለ መንግሥት ራሱን በራሱ እየተበተበ አንድም ፋይዳ ያለው ነገር ሳያከናውን መሸበት። ደኅንነቱ ተስፋዬ ወ/ሥላሴ ሻምበል መንግሥቱ ገመቹን ይዘው መከላከያን አስከበቡ፤ ለዚያውም በታንክና በብረት ለበስ።
ከዚያ በፊት ግን ነገሩን በሰላም እንጨርሰው በሚል ሽማግሌ ተልኳል፤ ሌ/ኮ አዲስ ተድላና ኮ/ል ደበላ ዲንሳ ነበሩ አደራዳሪዎቹ። ‹‹መፈንቅለ መንግሥቱ ያበቃለት ጉዳይ ነው፤ ምንም ድርድር ብሎ ነገር የለም። ባይሆን አግዙን›› ሳይሏቸው አይቀርም፣ እነ ጄ/ል መርዕድ። ዞሮ ዞሮ ሰዓቱ ነጎደ። ማስታወቂያ ሚኒስቴር አልተያዘ፣ ሬዲዮ ጣቢያ አልተያዘ፣ ቴሌ አልተያዘ…ሰዓቱ ነጎደ። የሳር ቅጠሉ አዛዦች በሙሉ እዚያ መሆናቸው ሳያዘናጋቸው አልቀረም። የጄ/ል አበራ ድንገት ሰው ገድሎ መሰወር ግን ነገሮችን አወሳሰበ።
የመንጌ ቀኝ እጅ ሞክሼያቸው መንግሥቱ ገመቹ የልዩ ብርጌድ ኃይላቸውን ከ4ኪሎ አንቀሳቀሱ። በሂልተን አድርገው አምባሳደር ጋ ሲደርሱ ‘መከላከያ ሚኒስቱሩን
ክበብ’ አሉ።
ውስጥ እነ ጄ/ል ፋንታ በላይ፣ እነ ጄ/ል አመሃ፣ እነ ጄ/ል መርዕድ…ምን እያደረጉ እንዳሉ የሚያውቅ ምድራዊ ኃይል የለም። ሆኖም በዚያ ሰዓት መከበባቸውን እንደተረዱ ከአሥመራ ይመጣል የተባለው ኃይል ባለመድረሱ ተስፋ ቆርጠው ሊሆን ይችላል። ብቻ ጄ/ር መርዕድና ጄ/ል አመሐ ዛሬም ድረስ ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ እዚያው ራሳቸውን አጠፉ።
ድኅረ ታሪክ
ግንቦት 9 ማታ ኮ/ል መንግሥቱ ከምሥራቅ ጀርመን ጉብኝታቸውን አቋርጠው ኮሽታ ሳያሰሙ ተመለሱ።
ግንቦት 10፣ ጄኔራል ደምሴ ቡልቶ በገዛ ወታደሮቻቸው ተገደሉ፤ ከእርሳቸው ጋር በድምሩ 18 ከፍተኛ መኮንኖች ተመሳሳይ ክፉ እጣ ገጠማቸው። በሟቾቹ ሬሳ ላይ እጅግ የሚቀፍ፣ አጸያፊ ድርጊት ተፈጸመ።
ከሦስት ቀናት በኋላ ጄኔራል ፋንታ በላይ ከተደበቁበት ኮንቴይነር ወጡ። ለጥቂት ወራት ማዕከላዊ ለብቻቸው ተነጥለው ታስረው ሳሉ እስከዛሬም ይፋ ባልሆነ ሁኔታ “ጠባቂያቸውን ገድለው ሊያመልጡ ሲሉ ተገደሉ” ተባለ።
በሦስተኛው ሳምንት መከላከያ ሚኒስትሩን ገድለው ያመለጡት ጄ/ል አበራ /ከወራት በኋላ ሳይሆን አይቀረም/ ጉለሌ አካባቢ ከተደበቁበት ዘመድ ቤት ተከበቡ። በመስኮት ዘለው ጣሪያ ላይ ወጥተው ሊያመልጡ ሲሉ በአንድ ወጣት ፖሊስ ግንባራቸውን ተመትተው ወደቁ። አንዳንድ የሰው መረጃዎች ጄ/ል አበራን አሳልፎ የሰጣቸው ዘመድ ዛሬም ድረስ በጸጸት ይኖራል ይላሉ። ከሆኑ ወራት በኋላ የአሥመራውን አየር ወለድ ጦር አዲስ አበባ ይዘው የመጡት ጄኔራል ቁምላቸው በአንዳች ተአምር አምልጠው አሜሪካ ገቡ ተባለ። ሲአይኤ እንዳሾለካቸው ተጠረጠረ።
ከዓመት በኋላ ግንቦት 13 ቀን 1981 መፈንቅለ መንግሥቱ ላይ ተሳትፈዋል የተባሉ 12 ጄኔራሎች ድንገት ለውሳኔ ተጠሩ። የወታደራዊ ፍርድ ቤት የመሀል ዳኛው ጄ/ል አሥራት ብሩ በብጣሽ ወረቀት የተጻፈችና ከኮ/ል መንግሥቱ እንደተላከች የምትገመት አንዲት ወረቀት እንባ እየተናነቃቸው አነበቧት ተባለ። በ12ቱ ላይ ሞት ተፈረደ። ፍርደኞቹም እንዲህ እያሉ ይጮኹ ነበር፤ ‹‹ቤተሰባችንን ሳንሰናበት አትግደሉን…››፣ ‹‹ፈላጭ ቆራጭ አገዛዝ ዕድሜ የለውም››፣ ‹‹ልጆቻችንን አደራ››። ያንኑ ምሽት ተረሸኑ።
የተነቃነቀ ጥርስ እንዲሉ በሰሜን ኢትዮጵያ ከአማጽያን ጋር ሲካሄድ የነበረው ውጊያ በአማጽያኑ ድል አድራጊነት እየገሰገሰ ወደ አዲስ አበባ ሲጠጋ መፈንቅለ መንግሥት ሙከራው ከከሸፈ ከ2 ዓመት በኋላ ግንቦት 13 ቀን ኮ/ል መንግሥቱ ከአገር ሸሹ። የኮ/ሉን ሽሽት ተከትሎ ለአንድ ሳምንት ርዕሰ ብሔር የሆኑት ጄ/ል ተስፋዬ ገብረኪዳን ሞታቸውን እየተጠባበቁ ለነበሩ ጥቂት የመፈንቅለ መንግሥቱ ተከሳሾች ምሕረትን አወጁ።
በጋዜጣው ሪፖርተር
አዲስ ዘመን ግንቦት 8/2013