በአንድ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ በቅርቡ የሰማሁትን ነገር መልሼ መላልሼ ሳስበው ሁሌም ይገርመኛል፡፡ ግለሰቡ ለጋዜጠኛው ቅሬታቸውን እያቀረቡ ናቸው፡፡ እሳቸውና የመንደራቸው ነዋሪዎች በውሃ እጥረት ሳይሆን እጦት ክፉኛ ተቸግረዋል፡፡ ፊት በአስራ አምስት ቀን አንድ ቀን ትመጣ ነበር፤ ውሃዋ፤ አሁን ጨርሳ ቀረች ነበር ያሉት፤ በእጅጉ ተቸገርን አቤት በሉልን ነበር ያሉት፡፡
እኚህ ሰው ውሃ በአስራ አምስት ቀን አንድ ቀን መምጣቷን በጸጋ ተቀብለውታል፡፡ እዚህ ላይ ችግር የለባቸውም፤ ምን ያርጉ፤ የእሳቸው ቅሬታ ተጨማሪ ጊዜ መጥፋቷ ላይ ነው፡፡ የክፉ ቀኑን እንደ መደበኛ ቆጥረውታል፡፡ ወደው አይደለም ተገደው ነው፡፡ አማራጭ የለማ፤ በተለይ በአረር በጋ ምን ይኮናል፡፡ በዝናብ በጣሪያ ውሃ ይኮረፋል፡፡
ከሁላችንም ህሊና የማይጠፋ ነገር የቱ ነው ተብለን ብንጠየቅ በተለይ ውሃ ሄደች፣ ውሃ መጣች፣ መብራት ሄደ መብራት መጣ የሚሉት ስለመሆናቸው አልጠራጠርም፡፡ እኛ ሰፈር እንደዚያ ነው፡፡
ቻይናውን የሀገራችን ልማት በማሳላጥ በኩል የሚደርስባቸው ያለ አይመስለኝም፤የሌሉበት ያልገቡበት ስፍራ የለም ፡፡ እንደልብ ናቸው፡፡ አንዱ ቻይናዊ ታዲያ አማርኛ ትናገራለህ ወይ የሚል ጥያቄ ቀረበለት አሉ፡፡ እሱም አዎን ለማለት ጊዜ አልወሰደበትም፡፡ እስቲ ተናገር ሲባል ውሃ ሄደች፣ ፣ውሃ መጣች፤ መብራት ሄደ ፤መብራት መጣ አለ ነው የተባለው፡፡
የውሃ መጥፋት ለአዲስ አበቤ ብርቁ አይደለም፡፡ ችግሩ በዚህ ሁኔታ ከቀጠለ ልጆች አርፍተ ነገር መስራት ሲጀምሩ የሚሰሩት አረፍተ ነገር እንደ ቻይናው ውሃ መጣች፤ ውሃ ሄደች ፣መብራት ሄደ ፤መብራት መጣ በሚለው ይሆናል ቢባል ስህተት አይሆንም፡፡ እመኑኝ ይሄው ነው የሚመጣው፡፡
እኚህ ሰውና የአካባቢያቸው ነዋሪዎች ውሃዋ / መቼም አንቺ ነው የምትባለው/ በአስራ አምስት ቀን አንዴ ስትመጣ በከፍተኛ ደረጃ እያቆሩ ካልሆነ በቀር እንዴት ሊበቃቸው ይችላል፡፡
ጎበዝ ውሃ ማቆር ስልጠና የተሰጠው ለአርሶ አደሩ ነበር ፤ ስልጠናው ለእኛ ነበር የሚገባው፡፡ አርሶ አደሩን እኛ ሳንበልጠው አንቀርም፡፡ ቤቱን ግቢውን በርሜል በበርሜል አረግነው ፣የቢጫው ጀሪካን ውለታ እንዴት ይከፈል ይሆን፤ ዘይት መግቦን፣ ይሄው ውሃ ጉድጓዳችን ቧንቧችን እሱው ከሆነ አያሌ አመታት ተቆጠሩ፡፡ ወተት ተብዬውም በእሱው እየተደረገ ነው በየመንደሩ እየተዞረ የሚሸጠው፡፡ ይህ ቢጫ ጀሪካን ውሃ ከሩቅ ይመጣበታል፤ ይታቆርበታል፤ ወዘተ፤
ወደ ጉዳዬ ልመለስ፡፡ እኚህ ሰው መነሻ ሆኑኝ እንጂ ሁላችንም እንደዚያው ነን፡፡ በየቀኑ 24 ሰአት ይመጣልን የነበረው ውሃ በሳምንት አራትና ሶስት ቀን ሲለቀቅልን ጮቤ ረግጠን ስናቁር ፣የጎደለውን ስንሞላ እንውላለን፤ እናድራለን፡፡ የጠባቧ ቤታችንን ጥቂት የማይባል ስፍራ በርሜልና ጀሪካን ይዘውት ተመስገን ብለን እንቀመጣለን፡፡
በዚህ ሳምንቱን እየቆጠብን እንገፋለን፡፡ ይህን ስለለመድን ውሃ በየቀኑ መምጣት ያለበት ስለመሆኑ ማሰቡን ትተናል፡፡ ከዚህ በኋላ የምንጮኸው ለምን ፈረቃ ውስጥ ገባን ብለን አይደለም ፤ ወደ መደበኛ አገልግሎት መልሱን ብለን አይደለም፡፡ በፈረቃው መሰረት ለምን ሳይመጣ ቀረ ብለንም ነው፡፡ እንደገና ሌላ አዲስ ፈረቃ እንዳይመጣ ነው የምንፈራው፡፡
በቃ የተሰጠንን ይዘን አገልግሎቱን እንደመደበኛ አገልግሎት ይዘን ዘልቀናል፡፡ ፈረቃውን ለመድነው፤ እውነት ለመናገር በጣም ለማዳዎች ነን፡፡
የለማዳነታችንን ልክ ለማሳየት ብዬ ነው ውሃን በስፋት ያነሳሁት፡፡ ሌሎች አገልግሎቶችም እንዲሁ በመደበኛነት ሲቋረጡብን አቤት ማለት ትተናል፤ ምክንያቱ ግልጽ ነው፤ ሰሚ የለም፤ ሰምቶም የሚፈጽም የለም፡፡ ግን ማቆም አለብን? የለብንም፡፡
እኛ ግን መልመድን ነው አጠናክረን የቀጠልነው፡፡ ለእዚያም ለጊዜው የተሰጠን መፍትሄ ዘላቂ አድርጎ መመልከት ተጠናውቶናል፡፡ በዚህ የተነሳ ፈረቃ እና የመሳሰሉትን አገልግሎቶች የመቀበል የመልመድ አቅም አጎልብተናል፡፡ ለችግር ተብሎ የተፈጠረውን ዘዴ መደበኛ አገልግሎት አርገን ተቀምጠናል፡፡ በተለያዩ እጥረቶች የተነሳ ያካበትነው ልምድ ጊዜያዊ መፍትሄን እንደዘላቂ ይዞ መቀመጥ ነው፡፡ በቃ ይህንን ነው፡፡ ግን እስከመቼ?
ራቁቱን ለተወለደ ህጻን እራፊ ጨርቅ መች አነሰው ይባላል፡፡ የመኖሪያ ቤት አለመኖር ክፉኛ የፈተናቸው አዲስ አበቤዎች ኮንደሚኒየም ሲደርሳቸው ምን ያህል እንደሚፈነጥዙ የማያውቅ የለም፡፡ ጎበዝ ቅድሚያ ክፍያ ፈጸመው፣ ቤቱ ተጠናቆ ተረክበው የሚያዩት የመኖሪያ ቤት ግን ብዙ ዋጋ የሚያስከፍል ነው ፡፡
ያ ሁሉ ገንዘብ ወጥቶበት የሚገዛው ይህ ቤት የውስጥ መዘጊያ የሌለው ዋናው መዝጊያና መስኮት መቀየርን የሚፈልግ፣ ቀለም ያልዞረበት ፣ ወለሉ እንደ ምንጣፍ ተቀርፎ የሚነሳ፣ አግሮ ስቶኑ ክፍተት ፣ የመጸዳጃ ቤቱን ጉድ ቤቱን ከቤትነት እንደሚያጎሉት እያወቅን ተቸግረናልና ቤት ብለን ጮቤ ረግጠን ተቀብለን ማስተካከል ውስጥ እንገባለን፡፡
መሆን የነበረበትማ መጠነኛ ማስተካከያ እንደ ፍላጎታችን አንዳንድ ማስተካከያዎችን ማድረግ እንጂ እዚህ ሁሉ ስራ ውስጥ መግባት አልነበረብንም፡፡ ይህም አለ፡፡ ገዝተህ ስትገባ አሟልተህ ነው በእርግጠኝነት ቤት የምታደርገው፡፡ ሁላችንም ከነችግሩ መረከብን ጤነኛ አካሄድ እንድናረገው ተገደናል፡፡
ቤቱ ቤት መሆን ይቀረዋል፤ አልቀበልም እንዳትል ማኩረፊያ የለህም፡፡ የውሃ አገልግሎት የሚሰጠው መብራት የሚሰጠው አካል በቅጡ አላገለገለኝም ብለህ ውል እንዳታቋርጥ ሌላ አማራጭ የለም፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መብራት እንዳሰኘው እየጠፋ ነው፡፡ እኛ ሰፈርማ አምና ለፋሲካ ጠፍቶ ነበር ፤ ዘንድሮም ጠፋ፡፡ በቃ በየአመቱ ለፋሲካ ይጠፋል ብሎ መገመት ውስጥ ሳልገባ አልቀርም፡፡ ማስታወቂያ የለ ምን የለ ቀኑን ሙሉ ይጠፋና ማታ ከሰራተኛ ጋር ይመጣል፡፡ ሲመጣ ጮቤ ረግጠን እንቀበለዋለን፡፡ ጠፍቶ የዋለ ወይም ያመሸ መብራት ሲመጣ ህዝቡ እንዴት በደስታ እንደሚጮህ አታውቁትም አይባልም፡፡ ያኮረፍነው ሁሉ ታርቀነው ቁጭ እንላለን፡፡ ችግሩን ለምደነዋላ፡፡
ችግሩ ግዙፍና ስር የሰደደ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ በሁሉም ዘርፍ የተሟላ አገልግሎት መሰጠት ቢጀመር በእርግጥ ተጀምሯል ብለን እምንጠይቅ ይመስለኛል ማመን ይከብደናል፡፡
ሰውዬው እስር ቤት ለበርካታ አመታት ቆይቷል አሉ፡፡ የሆነ ምህረት የሚያሰጥ ነገር በመንግስት በኩል ተፈጠረና በምህረት ተለቀሃል ይባላል፡፡ ይህ ሰው መደሰት እንደሚኖርበት ምንም አይጠራጠርም፡፡ ሰውዬው ግን ቆሞ ቀረ ነው የተባለው፡፡ ምን ሆንክ ሲባል የኖረበትን የለመደውን እስር ቤት መልቀቅ እንደሚቸግረው፣ የረሳውን የውጪውንም አለም መልመድ እንደሚቸገር ተናገረ አሉ፡፡
ልብ በሉልኝ እያነሳኋቸው ያሉት ችግሮች ለአብነት የተነሱ ናቸው፡፡ እኛም ከዚህ በኋላ ውሃ ለአንድ አፍታም አይቋረጥም ብንባል እንኳ ማመን እንቸገራለን፡፡ ካላዘሉኝ አላምንም ነው አለች የተባለው፡፡ ውሃ ያለ ፈረቃ ሲመጣ እንዴት እንደምንሆን አስቡ ፡፡ እኔ አላምንም ውሃ መጥታለች የሚሉ ብዙዎች ናቸው እኮ፡፡ የክፉ ቀኑን እንደ መደበኛ ከመቁጠር ያውጣን!
ኃይሉ ሣህለድንግል
አዲስ ዘመን ግንቦት 8 ቀን 2013 ዓ.ም