ሚያዝያ 27 ቀን 1933 ዓ.ም በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ እጅግ ልዩ ስፍራ አላት። ምክንያቱም ኢትዮጵያውያን ሀገራቸውን የወረረውን ፋሽስት ኢጣሊያን ለአምስት ዓመታት በዱር በገደል ተዋግተው፣ የወቅቱ ንጉስ አጼ ሀይለስላሴም በውጪ ሆነው ባደረጉት የዲፕሎማሲ ተጋድሎ ድል አድርገው ሀገራቸውን የተቆጣጠሩት ሚያዝያ 27 ቀን 1933 ዓ.ም ነው። ከአምስት ዓመታት ተጋድሎ በኋላ የፋሽስት ኢጣሊያ ሠንደቅ አላማ ወርዶ የኢትዮጵያ ሠንደቅ ዓላማ ኢንዲውለብለብ የተደረገውም በዚሁ ቀን ነው። ይህን ተከትሎም ንጉሰ ነገስት ሀይለስላሴ ለሀገሪቱ ሕዝብ ንግግር አድርገዋል።
ኢጣሊያ በ1888 ዓ.ም አድዋ ላይ በግማሽ ቀን ጦርነት የውርደት ማቅ መከናነቧ ሲቆጫት ሲያንገበግባት ኖሯል። እናም ከ40 ዓመታት በኋላ በ1928 ዓ.ም ቂሟን ለመወጣት ኢትዮጵያን ወረረች። ኢትዮጵያ በወቅቱ ገና የተደራጀ ጦር ያልነበራት ናት። ፋሽስት ኢጣሊያ አሉ የተባሉ ዘመናዊ የጦር መሣሪያዎችን፣ መርዝ ከሚተፉ አውሮፕላኖች ጋር ይዛ ነው ኢትዮጵያን የወረረችው።
ወረራው የተደራጀ ስለነበር ወረራው በቀላሉ ሊቀለበስ አልቻለም። ኢጣሊያ በመርዝ ጋዝ ጭምር ወረራውን ለመቀልበስ የተሰማሩ ኢትዮጵያውያንን መፍጀት ጀመረች። ስለዚህ ንጉሠ ነገስቱ እዚሁ ሆነው የከፋ ነገር ከሚመጣ በውጭ ሀገር ሆነው ቢታገሉ ይሻላል ሲሉ የዘመኑ ሹማምንቶች እንድ አማራጭ አቅርበው ነበርና ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ወደ እንግሊዝ ተሰደዱ። ሀገር አልባ ሆኑ። በዚያ ሆነው ግን በዲፕሎማሲው መስክ ሲሰሩ ቆይተው ከእንግሊዝ ጦር ጋር ሆነው ወደ ሀገራቸው የተመለሱት።
ኢጣሊያም ኢትዮጵያን በወረራ ያዘች። ሮም በደስታ ተቀጣጠለች። ኢትዮጵያዊያን አሳፈረኝ ብለው ጫካ ገቡ። አርበኞቹ ፋሽስቶችን ለመፋለም በዱር በገደሉ ተሰማሩ። የኢጣሊያ ሰራዊትን መውጫ መግቢያ ይከለክሉት ጀመር። ጦርነቱ በየፈፋው ይካሄድ ጀመር።
ኢትዮጵያውያን በከተሞችም ለኢጣሊያ ጦር አንገዛም ማለታቸውን ቀጠሉ። በአዲስ አበባ በገነተ ልኡል ቤተመንግስት ግራዚያኒ ህዝብ ሰብሰብ ባለበት በኢትዮጵያውያን በተወረወሩ ቦምቦች ጉዳት ደረሰበት። ይህ የሆነው በየካቲት 12 ቀን 1929 ዓ.ም ነበር። ይህንን ተከትሎ የኢጣሊያ ጦር በወሰደው ርምጃ አዲስ አበባ በደም ታጠበች። በአዲስ አበባ ብቻ ሕጻናት፣ ሴቶችና እናቶች አረጋውያን ጨምሮ ከ30 ሺህ በላይ ነዋሪዎች በፋሽስቶች በአሰቃቂ ሁኔታ ተጨፈጨፉ። ርምጃው ከአዲስ አበባ ውጪም ደብረ ሊባኖስ ድረስ የዘለቀ ስለመሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ።
ጀግኖቹን ስናስታውስ
በመጀመሪያ የጦርነቱ ተጋድሎ ጎላ ብለው የሚጠቀሱት ራስ እምሩ፣ ራስ ደስታ እና ወንድማማቾቹ አበራ እና አስፋ ወሰን ካሳ ወይም የራስ ካሳ ልጆች ናቸው። ራስ እምሩ በሽሬ ግንባር ያሳዩት የአመራር ችሎታ የሚደነቅ ነበር። በተለያዩ የአገሪቱ ቦታዎች ጠንከር ያለ ተቃውሞ እና ከፍ ሲል ጦርነት ገጠማቸው።
በተለይ ትግሉ ይቀጥል የሚል መልዕክት በስደት ላይ ከሚገኙት ንጉሰ ነገስት ይዤ መጥቻለሁ የሚለው የብላቴን ጌታ ህሩይ ወልደ ስላሴ ልጅ ፈቃደ ስላሴ መልዕክት መድረሱ ራስ እምሩ የአርበኞች መሪ እንዲሆኑ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሚና እንደተጫወተ ይነገርለታል። ራስ እምሩ ከሰሜን ይዘውት የመጡትን ጦር የጥቁር አንበሣን ወጣት አርበኞች እና በወለጋ እና ኢሉባቦር ሰፍረው የነበሩትን ነፍጠኞች አስተሳስሮ በድፍረት ለዘመቻው ወደ አዲስ አበባ አቀኑ።
በደቡብ ኢትዮጵያ ደግሞ የራስ ደስታ ጦር በዶሎ ላይ የሰነዘረው ደፋር የማጥቃት ርምጃ ከሽፎበት ከተመለሰ በኋላም ቢሆን ኦጣሊያኖችን እረፍት መንሳቱን አላቋረጠም፤ በዚህም በተለይ መጀመሪያው ላይ በደጃች በየነ መርዕድ ጦር እና በደጃች ገብረ ማሪያም ጦር ይታገዝ ነበር።
የመጀመሪያው ምዕራፍ ተቃውሞ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳየው በ1928 ማለቂያ ላይ የተደረገው በቅጡ ያልተቀናጀው በአዲስ አበባ የሚገኘውን የጠላት ጦር የማጥቃት ርምጃ ነው። በእቅዱ መሰረት ከገጠር የአርበኞቹ ኃይል በተለያዩ አቅጣጫ ሲያጠቃ ከተማው ውስጥ ደግሞ ህዝባዊ አመጽ ተቀስቅሶ የኢጣሊያን አገዛዝ ባጭሩ ለመቅጨት ታቅዶ ነበር።
ከገጠር የሚጠበቁት በሰሜን አበራና አስፋወሰን ካሳ፣ በደቡብ ደጃች ባልቻ ሳፎ፣ በሰሜን ምዕራብ ባላንባራስ (ኋላ ራስ) አበበ አረጋይ፣ በምስራቅ ደጃች ፍቅረ ማሪያም ይናዱ ነበሩ። የአርበኞችን መንፈስ በማነቃቃት ከፍተኛ ሚና ሲጫወቱ የነበሩት እና የጣሊያንን አገዛዝ በጽኑ የሚቃወሙት የወሎው ጳጳስ አቡነ ጳውሎስ ሚናም እዚህ ላይ ይጠቀሳል።
የሆነው ሆኖ ይህ ብዙ ሀይሎችን ያቀፈ እቅድ በህብረት የኢጣሊያን ጦር ማጥቃት ቀርቶ የተበታተኑ ጀብዱዎች የታዩበት ሆነና ተሰናክሎ ቀረ። አቡነ ጴጥሮስም ተይዘው ስቃይ ከበዛበት ምርመራ በኋላ በአደባባይ ተረሸኑ።
ከዚያ በኋላ ጦሩ ራሱን አጠናክሮ “ደረቅ ጦር” እና “መደዴ ጦር” በመባል ተከፍሎ ትግሉ ቀጠለ። ይህም ደረቅ ጦሩ ሙሉ ለሙሉ በውጊው ላይ ሲያተኩር መደዴው ጦር ደግሞ ውጊያው ተግ ሲል በእርሻ ተግባር እንዲሰማራ ተደረገ።
በሌላ መልኩ ደግሞ ፋኖዎች መረጃ የመሰብሰቢያ ዘዴም ነበራቸው። ወደ ጠላት ጦር ጠጋ ብለው የሚያደፍጡ ቃፊሮች የጠላትን ጦር እንቅስቃሴ እየተከታተሉ መረጃ ይሰጣሉ። ከሁሉም በላይ መረጃ በመሰብሰብ በኩል ቁልፍ ሚና የተጫወቱት ግን የውስጥ አርበኞች ናቸው፤ ከጠላት ጋር አብረው እየዋሉ እያደሩ፣ የጠላትን ጦር ጥንካሬ የታለሙ ዘመቻዎችንም ሆነ ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን በተመለከተ ለአርበኞች አስቀድመው መረጃ በመስጠት እገዛ አርገዋል። በዚህም የጠላትን እቅዶች ማጨናገፍ የተቻለባቸው ሁኔታዎች ነበሩ።
ከዚያም አልፈው በአስተዳደሩ ውስጥ ባላቸው ኃላፊነት በመጠቀም ለአርበኞቹ የሐሰት የይለፍ ፈቃድ እና መታወቂያ ወረቀት ያወጡም ነበር። በዚህ ታሪክ ላይ ከወንዶች ይልቅ ሴቶች ስለማይጠረጠሩ በስለላው ሰርተዋል። ከሴቶች የውስጥ አርበኞችም ከፍተኛ ዝና ያገኛቸው አርበኞች አዲስ ዓለም የመሸገው የጠላት ጦር እንዲደመሰስ ሁኔታዎችን ያመቻቹት ሸዋረገድ ገድሌ ይጠቀሳሉ።
የውስጥ አርበኞች ድርጅት ከፍተኛ ደረጃ ሊደርስ የቻለው በአዲስ አበባ እና በጎንደር ነው። በተለይም በዋና ከተማው የምድር ባቡር ሰራተኞች በመዋቅሩ የተጫወቱት ቁልፍ ሚና እንቅስቃሴውን ላብ አደራዊ ባህሪ ሰጥቶታል። በአጠቃላይ ኢጣሊያኖች ናላቸው የዞረው አርበኞቹ ከሚያደርሱባቸው ጥቃት ይልቅ የውስጥ አርበኞች የሚያደርሱባቸው ግዝገዛ ነበር ማለት ይቻላል።
ምክንያቱም አርበኞቹን በርቀት የሚያውቋቸው ሲሆ፤ የውስጥ አርበኞች ግን እነሱኑ መስለው መገኘታቸው ነው። የውስጥ አርበኞቹ አንዳንዴ ቢጠረጠሩ እንኳ እንዳይያዙ የሽፋን ስም ይጠቀሙ ነበር።
እዚህ ላይ የአርበኞችን የትግል ስልት በተመለከተ ሊጠቀሰ የሚገባው ነገር አንዳንዴ የማዘናጋት ታክቲክ መጠቀማቸው ነው። በተለይም በ1932 ራስ አበበ አረጋይ ለኢጣሊያ ሹማምንት እጄን ለመስጠት ዝግጁ ነኝ ብለው በማቄል የተጠቀሙት ታክቲክ ለዚህ አንድ ጥሩ ማስረጃ ነው። የሸዋ ገዥ ምክትል እንደራሴ የነበረው ጄኔራል ናዚ በእንዲህ ዓይነቱ የመታለል ታክቲክ ተሞኝቷል።
አበበ ለናዚ እጅ ለመስጠት ዝግጁ መሆናቸውን ይግለጹ እንጂ፣ ዓላማቸው ግን ሌሎች የአርበኞች መሪዎች ፋታ እንዲያገኙ ለማድረግ ነው ወደዚህ ታክቲክ የገቡት። በዚህ ላይ ምንም ጥርጣሬ ያልነበረው ናዚ በነገሩ ተታሎ የሠላም ድርድሩን ከልቡ ተያይዞት ነበር። በመጨረሻ ራስ አበበ ጦሩ ቀደም ብሎ ከደረሰበት ጥቃት ማገገሙን በቅጡ ካረጋገጡ በኋላ ኢጣሊያኖች በሌሎች አርበኞች ላይ ያደረሱትን አንድ ዕልቂት ሰበብ በማድረግ ድርድሩን አፍርሶ ትግሉን ቀጥሏል።
በአጠቃላይ መልኩ ስናየው የአርበኞች የነጻነት ትግል በዘመናዊ የኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ አንድ አኩሪ ምዕራፍ ነው። ኢትዮጵያውያን ለአርነትና ለነጻነት ሲሉ ለመሞት ዝግጁ ለመሆናቸው አንድ ሌላ ማረጋገጫ ነው። ለትግሉ የበለጠ ግምት የሚያሰጠው የወራሪውን ሀይል እና ጭካኔ በመገንዘብ አመቺ የሆኑ አዳዲስ ስልቶች ለመቀየስ መቻሉ ነው። አርበኞቹ በጠላት ላይ ያገኟቸው ድሎች የወሳኝነት ባህሪ ባይኖሯቸውም የኢጣሊያ ሰራዊት በአርበኞች ጥቃት ተደናብሮ እና ተጎሳቁሎ በመጨረሻ እንግሊዞች ለከፈቱት ዘመቻ ክፉኛ ተጋለጠ።
በአርበኞቹ ተጋድሎ የታዩ አንዳንድ ድክመቶችም ነበሩ። ይህን ሳይጠቅሱ ማለፍ ከድል በኋላ በአገሪቱ የተዘረጋውን ስርዓት በቅጡ ለመረዳት ያዳግተናል። መጀመሪያ ነገር ወራሪውን የኢጣሊያ ጦር ከኢትዮጵያ ለማስወጣት አርበኞች ከፍተኛ ተጋድሎ የፈፀሙበት እንደነበር ተጠቅሷል፤ በታሪክ ተደጋግሞ እንደሚታየው ድልን ለመቀዳጀት በሚደረግ ተጋድሎ ወቅት ባንዳዎችም ያጋጥማሉ። በዚህ ሀገር እና ህዝብ በተወረሩበት ወቅት ባንዳዎችም ለኢጣሊያ በማደር ሀገራቸውንና ኢትዮጵያውያንን ወግተዋል።
በዚህ መሰረትም አያሌ ኢትዮጵያውያን በግል ጥቅም ተታለው ወይም “ራስህን አድን” በሚለው መርህ የኢጣሊያ ባንዳ ሆነዋል። ውስጠ አዋቂ በመሆናቸውም እኒዚህ ባንዳዎች በተጋድሎው ላይ የኢጣሊያ ሰራዊት ካደረሰው የበለጠ ጉዳት አድርሰዋል። ይህም ሆኖ ግን ነጻነት ከተመለሰ ወዲህ በስደተኞች እና በባንዳዎች መካከል የተፈጠረው ግንባር ተጠቃሚ በመሆን ከቅጣት እና ውርደት ይልቅ የጠበቃቸው ሹመትና ሽልማት ነበር።
በአጠቃላይ ግን ጠላት በ1928 ዓ.ም አገሪቱን በወረረ ጊዜ ከጫፍ ጫፍ አርበኞች ተዋድቀዋል። ለምሳሌ በኦጋዴን እነ ነሲቡ ዘ አማኑኤል፣ እነ ደጃች ኡመር ሠመተር፣ በጎንደር እነ ውብነህ አሞራው፣ በጎጃም ሸበል በረንታ እነ ደጃዝማች በላይ ዘለቀ፣ በሸዋ እነ ራስ አበበ አረጋይ፣ ጃጋማ ኬሎ፣ ሸዋ ረገድ ገድሌ፣ ደጃዝማች ባልቻ ሶፎ (አባ ነፍሶ)፣ ገረሱ ዱኪ፣ ደጃች ብዙነሽ (በሜታ ሮቢ)፣ በሲዳሞ ራስ ደስታ ዳምጠው ወ.ዘ.ተ መተኪያ የሌላትን ህይወታቸውን እስከ መገበር በዘለቀ ተዋድቀዋል።
እነዚህ አርበኞች የነበሩባቸው ቦታዎች የድል ችቦ የተለኮሰባቸው ቦታዎች ናቸው እንጅ ተዋጊዎቹ ከአራቱም ማዕዘን ቋንቋ፣ ሀይማኖት፣ ፆታ ሳይገድባቸው ለሀገራቸው ነፃነት ተማምለው የተሰባሰቡ ኮኮቦች ነበሩ። ለዚህ ማስረጃው ጀነራል ጃጋማ ኬሎ በመፀሀፋቸው ላይ በስራቸው ከነበሩት 6 ሺህ ተዋጊ ሰራዊት ውስጥ ከኤርትራ፣ ከትግራይ፣ ከርቀት የአማራ አካባቢዎች የመጡ እንደነበሩበት ጠቅሰዋል።
ይህ የአርበኞች ታሪክ ከብዙ በጥቂቱ ነው።
አንደሚታወቀው የኢትዮጵያ አርበኞች ውለታ በቅጡ እንዳልተዘከረ ግልጽ ነው። የአምስት ዓመቱ የወረራ ዘመን በኢትዮጵያዊያን ላይ ያስከተላቸው የፖሊቲካ፤ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ተጽዕኖዎች በሚገባ እንዳልተዳሰሰም አሙን ነው።
የኢትዮጵያ አርበኞች የተጋድሎ ሚና የታሪክ ትምህርት (ሥርዓተ ትምህርት) አንዱ ክፍል እንዲሆን በማድረግ፤ አርበኞችን የሚዘክር ብሔራዊ ቤተመጻሕፍት በማቋቋም፤ የአርበኞች ማህበርን ከፖለቲካ ፍላጎት በፀዳ መልኩ በማጠናከር ወዘተ…ተግባራትን በአገር አቀፍ ደረጃ በማከናወን ተተኪ ትውልድ መፍጠር አስፈላጊ ነው። አገር ተረካቢ ትውልድ ለማፍራት ኃላፊነት የሚሰማው መንግስት ሊኖር ይገባል። የኢትዮጵያ አርበኞች ውለታ በተገቢ ሁኔታ ሊታወስም ሆነ ተተኪ ትውልድ ማፍራት የሚቻልበት መንገድ መፍጠርም ግድ ነው። ክብር ለአንዲቱ አገራቸው ኢትዮጵያ ለተዋደቁት ለአርበኞች!
(ለዚህ ጽሑፍ ዊኪፒዲያን፣ ማህበራዊ ትስስር ገጽን፣ ቀዳማዊ ሐይለ ስላሴ በመርስዔ ኀዘን ወ/ቂርቆስ እና የኢትዮጵያ ታሪክ ከ1847 እስከ 1983 በባህሩ ዘውዴ ተጠቅመናል)
አብርሃም ተወልደ
አዲስ ዘመን ግንቦት 1/2013