ሰዎች ራሳቸውን እንዲሆኑ ሲመከር ይሰማል፤ ራሳቸውን ከመሆን ይልቅ ሌሎችን መሆን የሚፈልጉ ጥቂት ባልሆኑበት ሁኔታ ራስን መሆን እንዴት ይቻላል? ሲሉ የሚጠይቁም አሉ።እንደ እውነቱ ከሆነ ሰዎች ማንን መሆን አለባቸው? እኔ ሰዎች ራሳቸውን ለመሆን ነጻነትም መብትም አላቸው፤ መሆን ያለባቸው ራሳቸውን ነው እላለሁ።ይህን ሀሳብ ደግፎም ይሁን ተቃውሞ የቆመ ግለሰብ ካለም በዚሁ አምድ መልስ እንደሚሰጠኝ ተስፋ አደርጋለሁ።
ሰዎች ራሳቸውን የመሆን መብትም ነጻነትም አላቸው ለሚለው ሀሳብ እንዴት የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል።ምክንያቴን በማስመሰል ወጥመድ ውስጥ ያሉትን ሰዎች ሁኔታ በማሳየት እና እንዴት ራስን የመሆን ነጻነትና መብትን በመጠቀም ራስን መሆን ይቻላል የሚለውን ሀሳብ በቻልኩት እና ሀሳቤን ያደረጃል ባልኩት አመክንዮ በማስደገፍ ለማቅረብ እሞክራለሁ።
አንዳንድ ሰዎች ምንም ያህል ያማረ መልክና ቁመና በጣም ተወዳጅ ተፈጥራዊ ባህሪ እንዲሁም እውቀት ያላቸው ቢሆኑም ስለራሳቸው ጥሩ አመለካከት የላቸውም።ሰው ሁሉ የማይወዳቸው፣ በህብረተሰቡ ዘንድ ተቀባይነትን ያጡ፣ በስራቸው ብቃት የሌላቸው መስሎ ይሰማቸዋል።
ይህ አመለካከታቸው ግን በእውነት ላይ የተመሰረተ አይደለም።እንዴት አወቅህ? ከእነሱ በላይ ስለራሳቸው ማን ያውቃል ? በሚል የሚሞግትም ብቅ ሊል ይችል ይሆናል፡፡
እነዚህ ሰዎች በሚኖሩበት ህብረተሰብ ውስጥ ተቀባይነት እያላቸው፣ ራሳቸውንና ኑሯቸውን አሸንፈው የሚኖሩ ትጉህ ሰራተኞች ሆነውም እኮ ነው ሁልጊዜ ራሳቸውን ዝቅ አድገው የሚመለከቱት።በተለይ ከእነርሱ በበለጠ የተሳካላቸውን ሰዎች ሲመለከቱ ደስታቸው በቀላሉ ብን ብሎ ይጠፋባቸዋል፤ ለጊዜውም ቢሆን የነበራቸው በራስ መተማመን እንደ ጠዋት ጤዛ ይረግፍባቸዋል፡፡
በኑሯቸው ከእነርሱ የተሻሉ ሰዎችን መመልከቱ፣ ከእነርሱ ትምህርትም ቢቀስሙ ፣ እንዴት ለዚህ ደረጃ ደረሱ ብለው ቢጠይቁ ክፉ አይደለም።ከዚህ ውጪ ግን ራሳቸውን ከሌሎች ጋር አወዳድረው ራሳቸውን አሳንሰው ለመመልከት ብለው ከሆነ ሌሎችን የሚያዩት ይህ ይጎዳቸዋል እንጂ አይጠቅማቸውም፡፡
በከንቱ ራሳቸውን ዝቅ አድርገው በመመልከት “የማልረባ ነኝ” ብለው የሚደመድሙ ሰዎች ሲሳካላቸውም ደስተኛ ላይሆኑ ይችላሉ፤ ባገኙት ስኬት በመደሰት ፋንታ “የተሳካልኝ እንደ ዕድል ወይም እንደ አጋጣሚ ነው ብለው ያምናሉ እንጂ፣ ጥሬ ግሬ ያገኘሁት ነው ብለው አያምኑም።ይህ ትተው ሌሎች ከደረሱበት ለመድረስ ብለው የሌላው ሰው ቅጂ /ኮፒ/ ወይም ግልባጭ ለመሆን ይሞክራሉ፡፡
እያንዳንዱ ሰው ልዩ ልዩ ችሎታዎችን በተፈጥሮ ተቸሯል።ልዩነቱ ችሎታዎቹን ተረድቶ ሰርቶ መለወጥ አለመቻል ላይ ነው።በተሰጠው ጥበብ እና እውቀት ረክቶና ተደስቶ እንዲሁም ራሱን እንዳለ ተቀብሎ ከመኖር ይልቅ ሌላ ሰው ለመምሰል የሚጣጣረው ለምን ይሆን? የሚያሳዝነው ደግሞ ያ የሚቀዳው /ኮፒ የሚደረገው/ ሰው የተሳሳተ አቋም ቢኖረው እንኳ ከነስህተቱ የሚገለበጥ መሆኑ ነው።
ያለንበት ዘመን ከጥሩነታቸው ይልቅ መጥፎነታቸው ያየለ ሰዎች እየበዙ ያሉበት ስለመሆኑ ይታወቃል።በሀገራችን እየተፈጠሩ ለሚገኙ ችግሮች አንዱ ምክንያት ይህን አይነት ሰዎች እየተበራከቱ መምጣቸው ነው።እነዚህ ሰዎች በማጭበርበር፣ በሙስና፣ በአጠቃላይ በወንጀል ሀብት ያገኙ እና ቁሳዊ ሕይወታቸው ያማረ ናቸው።ገልባጮች ይህን አይነት ቁሳዊ ዓለም እንዲኖራቸው ይፈልጋሉ፤ ሀብቱ እንዴት ተገኘ የሚለውን ግን አይመረምሩም።
ትንሽዬ ሱቅ ይዘው ባለሚገርም የቤት መኪናና የመኖሪያ ቤት የሆኑ ብዙ ገንዘብ የሚያንቀሳቅሱ ሰዎችን መሆን ይፈልጋሉ።እነዚህ ሰዎች በዚያች ሱቅ ብቻ ሰርተው ነው ሀብት ያካበቱት ብሎ መመርመር የለም።ከሱቁ ጀርባ ያለውን ህገወጥነት አያውቁትም።ብቻ እነዚህን ሰዎች መሆን ይፈልጋሉ።ለመሆን ቢሞክሩ እንኳ ትርፋቸው ኪሳራ ሊሆን እንደሚችል አይገምቱም።ምክንያቱም እነዚያ ሰዎች ማንነታቸው ምን ላይ እንደቆመ ሳያውቁ እነሱን ለመሆን የሞከሩ ናቸዋ፡፡
ሰው ከፋብሪካ እንደወጣ ቁስ አንድ ዓይነት ተደርጎ አልተፈጠረም።ነገር ግን ሰው በማንነት የጋራ ጠባዮች አሉት፤ ይሄውም የሚያሰብ፣ የሚያመዛዝን፣ ስሜት ያለው ፣ የራሱ ነጻነት ያለው … ነው።እነዚህን በመሳሰሉት የሰው ልጅ በሙሉ ይመሳሰላል፡፡
በሌላ በኩል ግን አንዱ ከሌላው የሚለይበት የራሱ የተፈጥሮ ችሎታ እና ባህሪ እንዲኖረው ተደርጎ የተፈጠረ እንጂ፣ የሌላ ሰው ግልባጭ (ኮፒ) ተደርጎ አልተፈጠረም።ራሳችንን ትተን ሌላውን ለመምሰል የምንሞክር ከሆነ ከላይ የተጠቀሱትን እውነታዎች እንክዳለን፤ ከሰው መሆን እንጣላለን፡፡
ታዋቂው የስነ ልቦና ምሁር “ፍሪትዝ ፐርልስ” የተዛባ የአዕምሮ አቋም ያለው ሰው በተለያዩ የስሜት ደረጃዎች ውስጥ እንደሚያልፍ ይገልጻል።ምሁሩ “መስሎ የመታየት ደረጃ”ን የመጀመሪያ ደረጃ ብሎ አስፍሮታል።በዚህ ደረጃ ላይ ያለ ሰው ያልሆነውን እንደሆነ ለማስመሰል ይሞክራል።ራሱን ብርቱ፣ ታላቅ፣ ደስተኛ፣ ለዓለም ታላቅ በረከት ወይም ስጦታ አድርጎ ይመለከታል።
ይህ ዘመን ያልሆኑትን እንደሆኑ አስመስለው ራሳቸውን የሚያቀርቡ ሰዎች የበረከቱበት ነው።ማንኛውም ራሱን እንዲሆን ተደርጎ ነው የተፈጠረው።
ህጻን ልጅ ቢጣፍጠውም ባይጣፍጠውም ወላጆቹ አፉ ውስጥ ያደረጉትን ሁሉ መብላት አለበት።ጨቅላ ነውናም የራሱን ምርጫ ማድረግ አይችልም፤ ወላጆቹ ናቸው የሚመርጡለት።እያደገ ሲመጣ ግን የማይፈልገውን ምግብ ሲሰጡት ፣ ከሚችለው በላይ ሲመግቡት መትፋት ይጀምራል፤ በእምቢታ መወራጨት ውስጥም ይገባል። አልበላም አልጠጣም የማለት ያህልም አፉን ጥርቅም አድርጎ የሚዘጋበት ጊዜም ቀስ በቀስ ይመጣል።ከእነዚህ ህጻናት ህይወት እንኳ ብናይ አእምሮ እየበሰለ ሲሄድ ወደ ምርጫ ውስጥ እንደሚገባ እንረዳለን፤ ሰው ራሱን ለመሆን ወይም ለመምረጥ በተፈጥሮ የቸረችው እንዳለ ከዚህም እንገነዘባለን፡፡
ስለዚህ ሰዎች በሙሉ በየትኛውን ጉዳይ ላይ የራሳችን አቋም ሊኖረን ይገባል።በግል፣ በቤተሰብ እንዲሁም በአገር ጉዳይ ላይ የራሳችን አቋም ሊኖረን የግድ ነው፤ እንደ ወራጅ ውሃ ከሚፈሰው ጋር መፍሰስ የለብንም።
ወዳጄ ሆይ ! ራስህን ለመሆን ነጻነቱና መብቱ አለህ፤ ግለሰቦች ወይም ቡድኖች እንደ መንጋ የሚነዱህ እና የማንም ግልባጭ መሆን የለብህም።ከሰዎች ልትወስዳቸው የምትችላቸው ጥሩ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ፤ ስትወስድ ግን ተጠንቅቀህ ሊሆን ይገባል።በዙሪያህ ለሚከናወኑ ነገሮች እንቅፋት ይሆናሉ ብለህ የምታስባቸውን ነገሮች ለመለየት መጠየቅ፣ የሚያጠራጥርም ነገር ሲገጥምህም ከመጠራጠር አለመቆጠብ ያስፈልጋል፡፡
መጠንቀቅ ያለብህ የራስህን አቋም ሳይሆን፣ የሌሎች ግልባጭ (ኮፒ) ላለመሆን ነው፤ ግልባጭ ሆነህ እነ እንቶኔን ልሁን ካልክ እናፍርስ ሲሉህ ስታፈርስ ፣እንግደል ሲሉህ ስትገድል ፣ስታቃጥል እና ያንተ ባልሆነ እኩይ ሀሳብ ውስጥ ስትዳክር ትኖራለሀ።ስለዚህም ራስህን ለመሆን ነጻነቱም መብቱም አለህና ራስህን በመሆን በጎነት ስራ ተነስ!!
አብረሃም ተወልደ
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 26/2013