የመጀመሪያዋ አውቶሞቢል ወደ ኢትዮጵያ አዲስ አበባ የገባችው በ1900 ዓ.ም ነው፤ አውቶሞቢሏ የመጣችው ከእንግሊዝ አገር ነበር። መኪናይቱን ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት ሀሳቡን ያቀረበው ቤንትሌይ የተባለ ግለሰብ ነበር።
ቤንትሌይ ስለምኒልክ ፍላጎት ለማወቅ ባለው ጉጉት እያጠያየቂ ብዙ መረጃ አግኝቷል። ለቴክኖሎጂ ያላቸውን ጽኑ ፍላጎት፣ ዘመናዊቷን ኢትዮጵያ ለመፍጠር እየሄዱ ያሉበትን ጎዳና ሁሉ ጠይቆ ተረድቷል። በዚህም ምክንያት ቤንትሌይ መኪና ይዞ አዲስ አበባ ለመግባት እና ለምኒልክ ለማሳየት ወሰነ። ለእንዲህ ዓይነቱ ረጅም እና መንገድ ለሌለበት ጉዞ ጠንካራ አውቶሞቢል እንደሚያስፈልገው አመነ።
ይህንንም ሀሳቡን የዌልሲሌይ ቱል ኤንድ ሞተርስ ማኑፋክቸሪንግ ኩባንያ ስራ አስኪያጅ ለሆነው ለሚስተር ሲድሌይ አጫወተው። ሚስተር ሲድሌይም ሀሳቡን ደግፎ መኪና መረጣው ተጀመረ።
የአውቶሞቢሉ ጉዳይ በኩባንያው በኩል የሚፈጸም ሆነ፤ ለቤንትሌይ ሌላ ችግር የሆነበት ጓደኛ ወይም ሹፌር ማግኘት ነበር። የሚፈልገው ሰው ደስተኛና የማይደክመው፣ የማይማረር፣ የማይበሳጭ የራሱን መኪና ብዙ ጊዜ የነዳ እና ጥሩ የሹፌርነት ልምድ ያለው መሆን እንዳለበት አሰበ።
ቤንትሌይ እንዲህ ዓይነቱን ሰው ለማግኘት ለንደን ከተማ ውስጥ ሲፈልግ እና ሲያስፈልግ ቆየ። አንድ ቀን ከሚስተር ዌልስ ጋር በመኪና ሲሄዱ የዌልስን የመኪና አነዳድ አይቶ ተደሰተ። ወዲያውኑ “ስማ ዌልስ በሚመጣው ሳምንት ከእኔ ጋር ወደ አቢሲኒያ ትሄዳለህ?” ሲል ጠየቀው። ዌልስም “በደስታ፤ ጌታው ግን አቢሲኒያ የት ነች?” ሲል ጠየቀው።
የእንግሊዝ ጋዜጦች ይህንን ይከታተሉ ስለነበረ ቅዳሜ ማታ ሚያዝያ 18 ቀን 1900 ዓ.ም የእንግሊዝ ጋዜጠኞች ማህበር አባላት ትሮካዲሮ በተባለ ሆቴል የመሰነባበቻ ግብዣ አደረጉላቸው።
አውቶሞቢሏ ከእንግሊዝ አዲስ አበባ ጉዞ የጀመረችው ሚያዝያ 19 ቀን 1900 እሁድ ሲሆን፤ የመጀመሪያ ጉዞዋ ደግሞ ወደ ፎልክስተን ነበር። ዌልስ እየነዳ ቤንትሌይ ከጎኑ ተቀምጦ ነው ጉዞው የቀጠለው። ከኋላው መቀመጫ “ከደረሳችሁበት እደርሳለሁ” ያለ አንድ ቡሊ የሚሉት ወጣት ተቀምጧል። ቤትሌይ የዙሉ ቋንቋ በሚገባ የሚችል ሲሆን፤ አማርኛም አጥንቶ በመጠኑ ይናገራል።
ከፈረንሳይ ዋና ከተማ ፓሪስ ሲደርሱ ጋዜጠኞች ቃለ መጠይቅ አደረጉላቸው። ከሶስት ቀናት በኋላ ወደ ማርሴል ተጓዙ። ለጉዟቸው የሚሆን 750 ጋሎን ቤንዚን የሰጣቸው ደግሞ ላካፓኝ ጀኔራል ዱፔትሮሊየም የተባለ ኩባንያ ነው።
በምግብ በኩል ሳጥን የጣሳ ስጋ፣ ሻይ ቅጠል፣ ብስኩት፣ ፍራፍሬ፣ ስኳር፣ ወተት፣ ሰርዲን፣ የቡና ዱቄት፣10 ቀረጢት ዱቄት፣ ውስኪ፣ የመነረገድ እና የከተማ ልብሶች ፣መድሐኒት፣ ጠመንጃ፣ ሽጉጥ ፣ የሁለት ጊዜ ቅያሬ ጎማ እና የመነረገድ መለያ ካርታ ይዘው ጉዟቸውን የጀመሩት። ዲ 3130 የሆነችውን መኪና በመርከብ ጭነው መንገዳቸውን ቀጠሉ።
ሃያ ሰባት ቀን ሙሉ በባህር ላይ ሲጓዙ ከርመው ጅቡቲ ደረሱ። ጅቡቲ ሰደርሱ ከእንግሊዝ ከወጡ ሁለት ወር ሆኗቸዋል። ጅቡቲም እንደደረሱ ለጅቡቲም የመጀመሪያ መኪና ስለነበረች ታሪክ ሰሪዎች ተብለው የጂቡቲው አገረ ገዥ ሙሴ ፓስካል የራት ግብዣ አደረጉላቸው።
በዚያ የእራት ግብዣ ላይም ሌሎች ሁለት አውቶሞቢሎች ከፈረንሳይ አገር ሊመጡ መነሳታቸውን ቤንትሌይ ሰማ። በዚህ ምክንያት እንዳይቀደም ብሎ ቤንትሌይ ጅቡቲ ሊቆይ አልፈለገም።
በጅቡቲ ህዝቡ መኪናዋን እየከበበ በአድናቆት ሲመለከት ቆየ። መኪናዋ ለ10 ቀናት ጅቡቲ ሰንብታለች። ምክንያቱ ደግሞ ስለንግዳቸው ጥናት ማድረግ መፈለጋቸው ነው። ጅቡቲ ያሉት ፈረንሳዮች መኪናይቱ ወደ ኢትዮጵያ እንዳትገባ በይፋ ባይናገሩም በተግባር ይገልጹ ነበር እና በመንገድ ላይ ታርደው እንደሚቀሩ ነገሯቸው። በመጨረሻ የጂቡቲ ባለስልጣናት ከጅቡቲ ወደ ኢትዮጵያ ለመግባት ፈቃድ እንደማይሰጣቸው አስረድተው፤ ወደ እንግሊዝ ሶማሌ ቢሄዱ ግን እንደማይከለክሏቸው ነገሯቸው።
እነ ቤንትሌይ ከጅቡቲ ወደ እንግሊዝ ሶማሌ ዕቃቸውን በኪራይ ግመል አስጭነው በመኪናቸው ጉዞ ጀመሩ። ከጅቡቲ ከተነሱ በአራተኛው ቀን ዘይላ ደረሱ። ዘይላ እንደደረሱም የዘይላው አገረ ገዥ “ወደ ጅቡቲ ተመልሳችሁ መኪናዋን በባቡር ድሬዳዋ ድረስ ላኩ እንጂ ከዚህ ከዘይላ በመኪናዋ እንድትሄዱ አልፈቅድም። ከድሬዳዋ በኋላ ግን የራሳችሁ ጉዳይ ነው” አሏቸው። እነቤንትሌይ ፈለገው ይሁን ሆን ብለው ዕቃዎቻቸውን በግመል ጭነው አስቀደሙና በመኪናቸው ጉዞአቸውን ወደ ኢትዮጵያ ጀመሩ።
“. . .ከኢትዮጵያ ግዛት ዱአሌ ላይ ስንደርስ በየቤቱ በራፍ የኢትዮጵያ ባንዲራ ተሰቅሎ አየን። በእኛም መኪና ላይ የኢትዮጵያ እና የአንግሊዝ ባንዲራ በቀኝ እና በግራ ተሰቅሏል። ከመንደሯ ስንገባ ብዙ ተኩስ ተሰማ፤ የተተኮሰው ለክብራችን መሆኑ ተነገረን። ወደ መሀል ስንገባ በሰልፍ የቆሙ የኢትዮጵያ ወታደሮች አጋጠሙን። ቤትሌይም ከመኪናው ወርዶ ሰላምታ ሰጠ። ከሰልፉ አዛዥ ጋርም ተጨባበጡ።
ግሪካዊው ነጋዴ ጆርጂም ከዚያው ነበረ። ጆርጅ ኢትዮጵያ ከገባ ከአስር እስከ አስራ አምስት ዓመት ስለሚሆነው የመኪና ነገር አዲሱና ብርቁ ሆነ። ከዚያም ግብዣ ተደረገልንና ጠጅ ጠጣን። መኮንኑም በጉዞአችን ሁሉ ምንም ችግር እንዳይገጥመን የሚቸግረንን ሁሉ እንዲረዳን ከምኒልክ መታዘዙን ነገረን።… ሲል ሐሊ የተባለ ጸሀፊ አስፍሯል።
ድሬዳዋ ሲደርሱ ታላቅ አቀባበል ተደረገላቸው። ህዝቡም የኢትዮጵያንና የእንግሊዝን ባንዲራ እየያዘ በሰልፍ ተቀበላቸው። ስለክብራቸውም ብዙ ጥይት ተተኮሰ። ቤንትሌይ በወቅቱ የሆነውን ሲገልጽ “ . . . በድሬዳዋ ከመኳንንቱ ጋር ስጨባበጥ የመጨባበጡ ስርዓት ብቻ እኩል ሰዓት ፈጀብኝ . . .” ብሏል። በድሬዳዋ ታላቅ ግብር ተደረገ። ግብዣውን አዘጋጅተው ግብር ያገቡት የድሬዳዋ ጉምሩክ ኃላፊ አቶ ንጋቱ ናቸው።
ሐረር ያሉ መኳንንቶች መኪናዋን ማየት ስለፈለጉ መኪናዋን ይዘው ሐረር ሄዱ። ከሐረሩ እና ከድሬዳዋ ጉብኝት በኋላ መንገዳቸውን ወደ አሰቦት አደረጉ። ከአገራቸው ከተነሱ በሰባተኛው ወር አዲስ አበባ መግቢያ አካባቢ ታህሳስ 20 ቀን 1900 ደረሱ፤ መረሳት የሌለበት ጉዳይ መኪናዋ ሰው ትጫን እንጂ ሌሎች ቁሳቁስ የተጫኑት በግመሎች ነበር።
አዲስ አበባ ለመግባት ጥቂት ሲቀራቸው እጅግ ብዙ ህዝብ ተሰልፎ ጠበቃቸው። ከፍተኛ አቀባበል ተደረገላቸው። ከዚያም ትልቅ ድንኳን ተተክሎ ስለነበር ፊት አድርገው ሲጋበዙ ውለው ድንኳን ውስጥ አደሩ። በማግስቱም ወደ አዲስ አበባ ከተማ ጉዟቸውን ጀመሩ።
አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሲደርሱ ሁለት ሺህ ያህል ፈረሰኛ ተቀበላቸው። የአዲስ አበባ ከንቲባ በስፍራው ነበሩ። ህዝቡ ሆ! እያለ አቀባበል ሲያደርግ እነሱም የመኪናይቱን ጥሩንባ እየነፉ አደመቁት።
መኪናይቱን የሚነዳው ዌልስ ኮራ ብሎ ጉዞውን ቀጠለ። ዳግማዊ ሚኒልክ “ካዲሱ ሆቴል ይረፉ” ብለው ስለነበር ታህሳስ 21 ቀን 1900 ዓ.ም በጊዜው እቴጌ ሆቴል ይባል ከነበረው የእቴጌ ጣይቱ የግል ሆቴል ገቡ። መንገደኞቹ ተጣጥበው ሲጨርሱ ታላቅ ግብር ቀረበ። ግብሩም እንዳለቀ የዳግማዊ አጤ ምኒልክ መልዕክተኛ መጣና “መኪናዋን ቶሎ አምጡና ልያት ብለዋል” አላቸው። ቤንትሌይም “መኪናዋ ስለቆሸሸች እስክናጥባት ድረስ ጊዜ ይሰጠን” ብሎ ለእንግሊዙ ጉዳይ ፈጻሚ ለሆለር ነገረው። ሆለርም ይህን መልዕክት ይዞ ወደ ዳግማዊ ምኒልክ ዘንድ ሄደና በጉዳዩ ተነጋግሮ ለጠዋት አምስት ሰዓት ቀጠሮ ተቀብሎ ተመለሰ።
በቀጠሮው መሰረት መኪናዋን ይዘው ወደ ግቢ ሔዱ። መኪናዋን ከህዘቡ መሐል አቁመው እጅ ለመንሳት እና ከምኒልክ ጋር ለመተዋወቅ ወደ አዳራሽ ገቡ። ከምኒልክ ጋር በአዳራሹ ውስጥ ከተዋወቁ በኋላ ምኒልክ መኪናዋን ለማየት ወጡ። መኪናዋ አጠገብ ሆነው በቤንትሌይ አስረጅነት ስለመኪናዋ ጉዳይ አንድ ባንድ ተረዱ። በዚህ ጊዚ አብዛኛው መኳንንት እና ህዝቡም ጭምር መኪናዋን መጠጋት ፈርቶ ነበር። ምኒልክም መኪናዋን እንዳይጠጉ መክረዋቸው ነበር። ምኒልክ ግነ የማንንም የማስፈራሪያ ምክር አልሰማ ብለው መኪናዋን ተጠግተው አዩ።
ቀጥለውም ምኒልክ ታህሳስ 22 መኪናው ላይ ወጥተው ከነጂው ዌልስ ጋር ተጓዙ። ምኒልክ ደስታቸው ወደር የለውም ነበር። የመጀመሪዋን መኪናም ተከትሎ ጥር 15 ቀን ጀርመናዊው አርኖልድ ሆልዝ ሌላ ናኪ የተባለች መኪና ይዞ አዲስ አበባ ገባ።
አብርሃም ተወልደ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 24/2013