ተገኝ ብሩ
አይኔን ስገልጥ የማየው ብርሀን ሁሌም በህይወቴ አዲስ ቀን የጀመርኩ ያህል እንዲሰማኝ ያደርገኛል። የንጋት ብርሀንን የማየት ያህል ደስታ የሚፈጥርብኝ ነገር ጥቂት ነው። ሰው ደካክሞትና ሰውነቱ ዝሎ ወደ አልጋው ሲሄድ ያየው ጭለማ ንጋት ላይ ከድካሙ ተላቆ ሰውነቱ ቀሎት ሲነቃ ጭለማው ተገፍ ሰማዩ ጠርቶ ማየቱ በራሱ ድጋሚ እዚህ ምድር ላይ እንዲኖር የተፈቀደለት ለመሆኑ ማረጋገጫው ነውና ሳያውቀው ደስ ይሰኛል።
የጠዋት ብርሀን ናፍቆቴን ለመወጣትም ስል ነው አልጋዬን በመስኮት በኩል አስጠግቼ ማንጠፍ የምወደው ። ዛሬ በሳምንት በጉጉት የምጠብቀው ቀን እሁድ እንደመሆኑ ከአልጋዬ ላይ አርፍጄ “በቀኝ አውለኝ” በሚል መልካም ምኞት እና ጸሎት እራሴን አነቃሁ። የምኖርበት “አፓርታማ” ዙሪያው በመኖሪያ “ቪላዎች” ተከቧል። እኔ ካለሁበት ክፍል 4ኛ ወለላ ላይ ወደ መስኮት ጠጋ ተብሎ ወደታች የአብዛኛዎቹ ቤቶች ውጫዊ ገፅታና ግቢ ውስጥ ያሉ ሰዎች እንቅስቃሴ መመልከት ያስችላል።
አፓርታማው ላይ የሚገኝ ባለ አንድ ክፍል ጠባብ ክፍል ተከራይቼ ከገባሁ ገና 6ኛ ቀኔ ነው። በጣም የምወደው የቅርብ ጓደኛዬ እሁድን አብረን ልናሳልፍና ቤቴን ሊያየው በዚያውም እዚያው እኔ የተከራየሁበት ሰፈር ካለችው እህቱ ጋር ሊያስተዋውቀኝ ቀጠሮ ይዘናል። እኔም ብቸኝነቴን የሚቀርፍልኝ ጎረቤት ላገኝ ነውና ደስ ብሎኛል።ከእንቅልፌ ስነቃ ገና ያስታወስኩት ጓደኛዬ እስኪመጣ ቁርሴን ላሰናዳ አሰብኩ።
ሁሌም ልማዴ ሆኖ በእድል አምናለሁ። ጠዋት ላይ የሚገጥመኝ መልካምም ሆነ መጥፎ ገጠመኜ ያንን ቀን የሚወስንልኝ ይመስለኛል። ኡፉ ጥሩ ነገር ሰማሁ በደስታ ስሜት የሚገልፁት ጩኸት። “ብራቮ ጎልል…..ብራቮ… ገብቷል” ህፃናት ኳስ እየተጫወቱ መሆኑ ገባኝ። አፍታ ቆይቶ ወደ ጭቅጭቅ ተለወጠ መሰለኝ “… አልገባም …አትፈሩ.. እፍርታም…ፎሪ ነው” ከሌሎቹ ህፃናት የሚሰማው የክርክር ድምፅ። ክርክር …ክርክሩን አልወደድኩትም። ወይ! ምን አለ ቢስማሙ። ገና ከመንቃቴ መግባባት የተሳናቸው ህፃናት መመልከት … ኡፉ!….ቀኔ ወዝጋባ ሊያደርጉብኝ ነው።”
ልጆቼን እየወቀስኩና አይኔን እያሸሁ ወደመስኮቱ ጠጋ ብዬ ሁኔታቸውን ለማየት ሞከርኩ። ጨዋታውን አቁመው አንድ ቦታ ላይ ሰብሰብ ብለው ይጨቃጨቃሉ። ወደመስኮቱ በደንብ ጠጋ ብዬ የልጆቹን ሁኔታ በደንብ ማየት ጀመርኩ። ህፃናቱ በጠባቡ የአስፓልት መንገድ ላይ ነው ኳስ እየተጫወቱ ያሉት።
የአስፓልት መንገዱ ዳር ዳሩን ይዞ የታጠረ ትልቁ የግንብ አጥር ውስጥ ሶስት ህፃናት በተንጣለለ ግቢያቸው እየተሯሯጡ ኳስ ይጫወታሉ። ግቢ ውስጥ ያሉቱ የሚጫወቱበት ቦታ ውጪ አስፓልት ላይ ከሚጫወቱት እጅጉን ሰፊና ምቹ ነው።
ሁሌም እዚያ መስኮት ላይ ቆሜ ዙሪያውን ያሉት የመኖሪያ ቪላዎቹ የያዙት ስፋት እያየሁ ተጣቦ የሚኖረው የአዲስ አበባ ሕዝብ አስባለሁ። አይኔ አንዳች ነገር እንደሚፈልግ ሁሉ ወደሌላኛው ግቢ ተሻገረ። በሰፊው ታጥሮ በተከለለው ሌላኛው ግቢ ውስጥ የሚገኘው ትልቁ ቪላ ከፊት ለፊት መውጫ በሩ በኩል አንዲት ልጅ አጎንብሳ ልብስ ታጥባለች።
አንድ ወንድና አንድ ሴት ከልጃቸው ጋር እዚያው በረንዳ ላይ ቁጭ ብለው ቁርስ ነገር እየበሉ ይታያል። ሰራተኛዋ ከእነሱ ፊት ለፊት ባለ ቦታ ላይ አጎንብሳ ልብስ ታጥባለች። ልጅትዋ ማልዳ ተነስታ ወደ አጠባ መግባትዋን የሚያመለክቱ በርከት ያለ ነጫጭ አንሶላ በልብስ ማስጫው ገመድ ላይ ይታያል። አንድ እድሜው 6 ወይም 7 አካባቢ የሚሆነው ልጅ እናትና አባቱ ካሉበት በረንዳ ኳስ ይዞ ልብስ እያጠበች ወዳለችው ልጅ ሲጠጋ ተከተልኩት።
ለመጫወት እጅጉን የጓጓ በሚመስል እርምጃ በረንዳውን ወርዶ ከመቅስፈት ኳስዋን ሲጠልዛት ልጅትዋ አጥባ ወዳሰጣችው አንሶላ ተወንጭፎ አንሶላውን አበላሸባት። ልጅትዋ ወዳንሶላው ሄዳ በኳስ መልሶ የወየበውን አንሶላ ከመስቀያው ላይ በድጋሚ ማጠብ ጀመረች። ልጁ ኳሱን እየጠለዘ መጫወቱን ቀጥሏል። በረንዳ ላይ ያሉት ባልና ሚስት የልጃቸው ድርጊት እያዩ ይሳሳቃሉ። ልጁ በአቧራ ያደፈውን ኳሱ በእናትና አባቱ ጭብጨባ ታግዞ መጠለዙን ቀጥሏል።
ድጋሚ ሌላ የታጠበ አንሶላ እንደ መረብ በኳሱ ሲነርተው ተመለከትኩ። ዕድለ ቢስዋ ሰራተኛ ድጋሚ የቆሸሸውን አንሶላ በማውረድ ወደ ማጠቢያዋ ይዛ ተመለሰች። እናትና አባት ልጃቸው ትልቅ ጨዋታ ላይ በተጋጣሚ ቡድን ላይ ጎል ያገባ ያህል እያጨበጨቡ ይሳሳቃሉ፤ይዝናናሉ።ልጁም በተግባሩ ቀጥሏል፤ልጅቱም ደጋግማ አጥባ በማስጣት ተግባርዋ ቀጥላለች።
ታዳጊው ልጅ ኳሷን እየያዘ ወደተሰጡት አንሶላዎች እየጠለዘ መጫወቱን ቀጥሏል።ከእናትና አባቱ የሚሰማው ጭብጨባ አበርትቶት ሁሉንም አንሶላዎች ማነካካት ሲጀምር ልጅትዋ ወደልጁ ስትቀርብ መሮጥ ጀመረ። የሰራተኛዋ ድምፅ ባይሰማም ልጅቱ የተቆጣች በሚመስል ሁናቴ ኳሱን ይዞ ወደ እናትና አባቱ ወደተቀመጡበት ሮጠ።
ልጅትዋ ልጁ ወደ ወላጆቹ እየሮጠ ሲጠጋ ትንሽ አሯሩጣው ተመልሳ አጎንብሳ አጠባውን ቀጠለች። ልጁ የበረንዳውን ደረጃ በሩጫ ሲወጣ አደናቅፎት ፊት ለፊቱ ሲደፋ ልጅቱ በፍፁም አላየችም ነበር።
አባት ከመቀመጫው ተነስቶ በሩጫ ወደልጁ አመራ እናት ተከተለችው። ልብስ የምታጥበው ልጅ የሆነውን ስትመለከት ደነገጠቸው። እሷም በሩጫ ወደልጁ ተጠጋች። ልጁ መጎዳቱ የእናትና የአባቱ ሁኔታ ያየ በቀላሉ ይረዳል። የልጁ እናት “ወይኔ ልጁ ኡኡኡ ጥርሱ ረገፈ….ኡኡኡ…”እያለች በጩኸት አካባቢውን ሞላችው። አባትየው ልጁን ከተኛበት አቅፎ አስነስቶ ወደ ቤት አስገባው።
የሰራተኛዋ በነበረችበት በድንጋጤ ደንዝዛ ቆመች። የልጁ እናት ከቤት ውስጥ ሮጣ ወጥታ ሰራተኛዋን አንቃ ይዛ ትጮህባት ጀመር። “ልጄን ገደልሽብኝ ጥርሱን አረገፍሽብኝ…አንቺ ገልቱ” እየጮኸች ልብስዋን ይዛ ገፈተረቻት። ለጥቂት ወደኋላ ከመውደቅ ተረፈች። አባት ልጁን ይዞ ከቤት ወቶ ቀጥታ ወደመኪናው አመራ በሩን ከፍቶ ልጁን አስገባውና ሚስቱን ጠራት። ወደ ህክምና ሊያመሩ መሆኑን ከሁኔታቸው መረዳት ይቻላል። የልጁ እናት ልጅዋ ወዳለበት መኪና ስትገባ አባትየው ወረደና ወደሰራተኛዋ ተጠጋ። ሁኔታዋ በጣም ያሳዝናል። በሁኔታው ልቤ ተሰቅሎ መከታተሉን ቀጠልኩ።
በድንጋጤ ፈዛ የቆመችው ልጅ የሰውየው ሁኔታ አስፈርቷት ወደኃላ አፈግፍጋ የትልቁ ቪላ ቤት ግድግዳ ተደግፋ ቆመች። ሰውየው ጠጋ ብሎ በጥፊ ሲመታት ከቆመችበት ወደ መሬት ዘጭ አለች። “ተነሽ በር ክፈቺ..” ብሎ አንባረቀባት። እየተንቀጠቀጠች የግቢውን በር ለመክፈት ተጣደፈች። ሰውየው መኪናውን በፍጥነት እየነዳ ግቢውን ለቆ ወጣ።
ሰራተኛዋ ግቢ ውስጥ ተኮራምታ ቁጭ ብላ አቀርቅራ ስታለቅስ ቆየች። ከቆይታ በኋላ ወደ ውስጥ ገብታ አንድ ቢጫ ፌስታል አንጠልጥላ በሩን ከፍታ ከግቢ ወጣች። ሰዎቹ ሳይመጡ ከዚያ ችግርዋ ልታመልጥ እንደሆነ ገባኝ። ሳላውቀው የልጅትዋ ቤቱን ጥላ መጥፋት ወደድኩት። ከዚያ መከራ መገላገልዋ ሳስብ መሄድዋን ደገፍኩት። በጥድፊያ ከዋናው በር ወጥታ ወደ አንዱ መንገድ ገብታ ታጥፋ ስተጓዝ በአይኔ ተከተልኳት።
ስልኬ ከኋላ እሪታውን ሲያቀልጥ እከታተለው ከነበረው ጉዳይ አነቃኝ። ከመስኮቱ ወደኋላ ተመልሼ ቻርጅ ላይ ተሰክቶ ወዳለው ስልኬ አመራሁ። አንስቼ አየሁት፤ አዲስ ቁጥር ነው። መልካም ነገር በመመኘት ወደጆሮዬ አስጠጋት። እንዳየሁት ባላሰብኩት የሚያውለኝ እንዳይሆን ተመኘሁ። “ሀሎ ጓደኛዬ እንዴት ነህ” ድምፁ አዲስ ባይሆንም በቀላሉ ማስታወስ ግን ተሳነኝ። “ሀሎ ማን ልበል?” የኔ ጥያቄ ነበር። “ባክህ በላይ ነኝ።ስልኬ ቻርጅ ዘግቶ በሌላ ነው የምደውልልህ ” አለኝ ከወዲያኛው ወደ ጆሮዬ የደረሰው ድምፅ። አብሬው ልውል የቀጠረኝ ጓደኛዬ ነው።
“ወዬ በልዬ እንዴት ነህልኝ” አልኩት በደስታ። “ሳምዬ አሁን ወዳንተ አልመጣም፤ እቆያለሁ። እህቴ ልጄ ሰራተኛዬ ደረጃ ላይ ወርውራብኝ ሀኪም ቤት ነኝ ብላ ደወለችልኝ ወደዚያ እየሄድኩ ነው።” ሲለኝ ግራ ተጋባሁ። “የትኛዋ እህትህ አዲስ እኔ የገባሁበት ሰፈር ያለችው?” ስለው “አዎን ዛሬ አስተዋውቅሀለሁ ያልኩህ…” ሲለኝ ጠዋት መስኮቴ ላይ ያየሁት ትርዒት ከጓደኛዬ እህት ቤት መሆኑ ገባኝ።
አጓጊው ጉርብትና …ተፈፀመ
አዲስ ዘመን ታህሳስ 2/2013