ተገኝ ብሩ
አራት ነን አንድ ክፍል የምንጋራ። አራት ነን በአንድ ቤት የምንኖር ።አራት ነን የኑሮ መወደድ ያቆራኘን ።አራት ነን ነፃነታችንን ማወጅ እየፈለግን ችግር ያዋደደን ጓደኛሞች ።አስማተኛ ሆነን በምናዘግምባት አዲስ አበባ ወጪያችን ገቢያችንን ስለሚበልጥ አመጣጡም እንዲሁ ግርምት ይፈጥርብናል፡፡
ለኔ ቢጤ ደሃ ኑሮን ሲኖሩ ማየት እንጂ ማኖር በማትፈቅደው አዲስ አበባ አንዱን በጠኔ ክርችም ሌላውን በተቃራኒው በቁንጣን እያጨናነቀች ታጅበኛለች። ከጓደኞቼ ጋር ማጌጥ አማረንና ተመካከርን። እናም ጃኬት ገዛን ።አንድ ጃኬት ለአራት በተራ ለመልበስ ።በአንድ ጃኬት በተራ ለማጌጥ ።አራታችንም በጃኬቱ መገዛት ላይ ድምፅ ለመስጠት ተሰባሰብን በሙሉ ድምጽ ጸደቀና በመዋጮ ተገዛ፡፡
የኛ ቤት ይለያል፤ ሙሉ የቤቱ አባል ካልተሟላ ምንም ርእስ ተነስቶ ውይይት አይደረግበትም። ምክንያቱም ብዙውን ጊዜ የምንወያየው በመዋጮ ላይ ስለሆነ ስብሰባው ላይ የሌለው አላዋጣም እንዳይለን በመስጋት ነው። እኔ ሀሳብ አቀረብኩ ፤ ጃኬቱ እንዲገዛ ምክኛት ስጠየቅ አብሮን በተማረ የሌላ መስሪያ ቤት ሰራተኛ ተለብሶ ማየቴን እንዳማረበት እኛ ከሱ ማነሳችንማ ማሳየት የለብንም በማለት በእልህ እንዲደግፉኝ ደግሞ በማራራት ተናገርኩ። የሌላ መስሪያ ቤቱ ጥሩ ደመወዝ የሚከፈልበት መስሪያ ቤት የሚሰራን ሰው ጠቅሼ አስረዳሁ፡፡
“እኛ ከሱ በምን እናንሳለን ይገዛ” የሌሎች ጓደኞቼ አቋም ነበር ።“አዎ በእርግጥ በደመወዝ እንጂ በምንም አንዱ ልማታዊ ድርጅት ነው ብሎ ይደራርቡበታል ሌላው ጥፋታዊ ይመስል ደሞዙ የተሰበረ እግር ያላት ኤሊ ይመስል የተንቀራፈፈ በሁለት ዓመት 200 መቶ ብር ይጨምሩለታል ።እኛ ብር ባይኖረን ወኔ አለን ።ይገዛ” የጃኬቱ መገዛት እርግጥ እንዲሆን ሌላኛው በፉከራ መልክ አሰማው።
በዚህ እልህ ሁሉም ያለውን አዋጥቶ ገበያ ተወጥቶ የተገዛውን ጃኬት ቀድሞ ለመልበስ እጣ ወጣ ።በሳምንት እየቀያየርን ልንለብሰው ተስማምተን እጣ ወጣ። ለገረመው ደረሰው፤ የመጀመሪያ ሳምንት የሱ ማጌጫ ሊሆን በቃ ። ድምጽ የሚከበርበት ቤት ነውና ጸደቀለት። አይናችንን እያቁለጨለጭን ፈቀድንለት።
የኛ ቤት ልዩ ነገር የሁላችንም ስምና ባህሪ መመሳሰሉ ነው። ካንዱ በቀር፤ ከየሺጥላ በቀር። የቤታችን አባላት ስምና እና ልዩ መለያ ባህሪያችን የአንዱ ጓደኛዬ ስም ዜና ይባላል። አቤት እድሜ ለዜና እኛ ቤት የመረጃ ችግር የለም። ዜና ባይኖር ከመረጃ ርቀን ቀርተን ነበር ።ሬዲዮ የለን፣ ኢቲቪ የለን ። እሱስ እንኳን አልኖረን በውሸቱ ተቃጥለን ቁጥራችን ከ4 በቀነሰ ነበር፡፡
ጃኬቱንስ አራት ባንሆን መች እንገዛው ነበር ።እናም ዜና መረጃዎችን እንደ ጉድ ያዘንብብናል። ችግሩ ዜና ዜናዎቹ አብዛኛውን ጊዜ ሲግናላቸው በተበላሸ ሳተላይት ቲቪዎች እና ኮልታቸው ባልተሰላሰለ ሬዲዮኖች እየሰማ ነው መሰለኝ የተሟላ መረጃ አይነግረንም ።ኧረ እኛም አሟላ ብለን አናስጨንቀውም፤ ባልተሟላ ኑሮ የተሟላ መረጃ ምን ያደርጋል። እና በዜና የመረጃ ችግራችን ተቀርፏል፡፡
ሁለተኛው ጓደኛችን ገረመው ይባላል። ታምረኛውና ተገራሚው ገረመው መገረም ስራው ነው። በቢል ጌት ሃብታም መሆን፣ በኤሊ መንቀርፈፍና በዩዜን ቦልት ፍጥነት፣ በጨርቆስና በቦሌ ልጆች የኑሮና የባህሪ ልዩነት ሁሌም ይገረማል፡፡
የገረመው መገረም በራሱ ሲያስቡት ያስገርማል። እንዲሁ ለመገረም የተፈጠረ ሁሉ ይመስለኛል፤ ተገራሚው ገረመው። የዋህና ቅን ነው። ከመገረሙ በላይ የሚያስርመው ገረመው፤ የሚገረምበት ሲያጣ የሚገርም ነገር እንኳን ይጥፋ ብሎ ሲናደድ ያስቀኛል ።ወይ ገረመው ገራሚ ሆኖ ቀረብን።
ሶስተኛው ጓደኛችን የሺጥላ ይባላል ።ምስኪን የሺጥላ እራሱን ላይችል ነገር የሺ ሰው ጥላ አሉት። እኔ የሺጥላን እንደገረመው በጣም እገረምበታለሁ። አንድ ነገር ብቻውን ማድረግ አይችልም ፤ አይወድምም። የግድ አጋዥ ያስፈልገዋል። አራት ዓመት አንድ ክፍል ቤት ውስጥ ስንኖር አንድ ቀን ምግብ የማብሰል ተግባር ብቻውን ተወጥቶ አያውቅም።
ስራዎችን ሁሉ ገረመው እስኪገርመው ድረስ አልችልም ብሎ ያልፋቸዋል። ለነገሩ እሱ ምን ያድርግ ቤተሰቦቹ ናቸው የማይችለውን ያሸከሙት። እሱ ለሺ አይደለም ለራሱም ጥላ መሆን ላይችል ነገር። ገረመው በየሺጥላ ሁኔታ ሲገረም ብቻ ነው ሌሎቻችን ሳንገረም ትክክል መሆኑ የሚገባን ።
የእኔ ስም ደግሞ በሰኔ ይባላል። በቃ እኔና ሰኔ እንዲህ ነን። የተቆራኘን ።የተወለድኩት ሰኔ ላይ ነው ።ትምህርት ጨርሼ የተመረቅሁትም እንዲሁ በሰኔ ነው። የመጀመሪያ ሴት ጓደኛዬን የተዋወኳት በሰኔ ነው፤ የዛሬ ዓመት ሰኔ ላይ ተለያየን እንጂ። ስራ የተቀጠርኩትም በዚህ ዓመት በሰኔ ወር ነው። ብቻ ሰኔ ላይ ብዙ ገጠመኝ አለኝ። እኔም ጥሎብኝ ገጠመኜ ሰኔ ላይ ካልሆነ መንገር ስለማልወድ ይበቃኛል፡፡
አሁን ላይ ያለው የኑሮ ውድነት በጣም መሮናል! እንደው በብዙ ነገር የመማረሩ ልምድ ስላለን እንጂ በንዴት አልቀን ነበር። የተከራየንበት ቤት ብዙ የሚከራዩ ቤቶች ያሉበት ግቢ ስለሆነ ስብሰባ ይበዛበታል ።አከራያችን በረባ ባረባ መሰብሰብ ይወዳሉ። ትናንት እኛ ግቢ ስብሰባ ነበር፤ ባንፈልግም ተገኘን። አዎ እኛ ግቢ ስልክ ሳይለንት ሳያደርጉ መግባት የተከራይነት ሙሉ መብት ማስነጠቅ ነው፡፡
ተከራይ ሳይለንት ሳያደርግ ቀርቶ ስልኩ ቢጠራ (ቢጮህ) ተረበሽኩ፥ ተደፈርኩ አበዛችሁት ብለው ይሰበስቡናል- አከራያችን። የግቢው በር ኳኳታ ከቤት ሰራተኛቸው አልፎ እሳቸው ጆሮ ከደረሰ በቃ ምንም ቢደክመን ክፍላችን ገብተን ማረፍ ብያምረንም እያማረችሁ ይቅር! አልጋው የእናንተ ይሁን እንጂ ቤቱ የኔ ነው ብለው አንኳኩተው ይጠሩናል፤ ለስብሰባ አከራያችን ።ስብሰባ ላይ ያልተገኘ ተከራይ ስብሰባው ሳያልቅ “ቤቱን ለዕቃ ማስቀመጫነት ስለምንፈልገው ቤት ፈልግ” ይባላል፡፡
ግን ያ ሰው ሲለቅ አንድም ቀን ዕቃ ገብቶበት
አያውቅም፤ ሌላ ተከራይ እንጂ። ለነገሩ አከራያችን ዕቃ እያሉ የሚጠሩት እኛን መሆኑ ዘግይቶም ቢሆን ገብቶኛል። ዕቃ ብለው መጥራታቸው፤ እንደ ፈለጉ ልክ እንደ ዕቃ ግባ ውጣ ማለትን ጊዜው ያጎናፀፋቸው ልዩ መብት ነው፤ ላለው ብቻ ይታከልለት ፖሊሲ። ታዲያ ለኛስ ለምን? እንዳትሉኝ። ጭንቅላት ሳይሆን ብር ነው ያልኩት ፈራካ ላለው ብቻ ። ሰብአዊነት የነተበበት ቁሳቁስ የነገሰበት፤ አልላቀቅ ያለንን ደህንነታችንን ረተንበት የነበረው እሴታችን የመደጋገፍ ልማዳችን የተነጠቅንበት ክፋ ዘመን! ወይ ነዶ! የትኛው ትውልድ ያለበትን ዕዳ ይከፍለን ይሆን ጓደኞቼ? እናም ማታ ተሰበሰብን … ፤ምን ተሰብስበን እላለሁ፤ለካ ለነሱ ዕቃ ነን፤ ተጠራቅመን፡፡
ባለፈው ሳምንት የገዛነው ጃኬታችን ከነገ ወዲያ ጀምሮ የእኔ ተራ ስለሆነ ቀን አጥቤ ውጪ አስጥቼው አስሬ እያገላበጥኩ ሳደርቀው ነው የዋልኩት። የምሽቱ ንፋስ ይምታው ብዬ እደጅ ትቼው ስብሰባ እስክንገባ ድረስ ባይኔ እከታተለው ነበር። ስብሰባ ሲሉን ብር ሊጨምሩ ይሆን በሚል ፍርሀት ጃኬቱን ረሳሁት።
ስነጠራ ተያይዘን ወደ አከራያችን ቤት ገባን ። አከራያችን ባለቤታቸውን ጨምሮ ከ8 ልጆቻቸው ጋር በፍሰሐ የተከራዮችን እድሜ ያርዝምልን፤ ቤት ሰሪዎችን ያጥፋልን እያሉ ምርቃት ከእርግማን አቀላቅለው ለፈጣሪያቸው በማቅረብ በስጋት ስጋን እስኪተው ቀዩን ከጮማው አማርጠው በድሎት ኑሮን በርቀት እንቁልልጭ ይሉናል፡፡
አከራያችን ሁሉም የግቢው ተከራይ መሰብሰቡን ሲመለከቱ ኑሮ ተወዷል ብለው በእያንዳንዱ ክፍል ላይ 200 ብር መጨመራቸውን አረዱን ።ደነገጥን፤ መከራከር አይቻልም፤ እሺ ብለን ወጣን፤ የሰማነውን መርዶ እያብላላን።
ውጪ ስወጣ ስገባ ያየሁት ጃኬቴ የለም ።ጓደኞቼ ያስገቡት መሰለኝና ጠየኳቸው። አለየንም አሉኝ ።የሺጥላ አንድ መርዶ አረዳኝ። ሰሞኑን ልብስ በግቢው ውስጥ ከተሰጣበት እየጠፋ መሆኑን እንደሰማ ነገረን፤ ሌባ እየገባ እየዘረፈ መሆኑን ገለጸልን ።የአከራያችን ስብሰባ ጃኬታችንንም 200 ብራችንም አስበላን ።ተፈፀመ ።
አዲስ ዘመን ህዳር 25 ቀን 2013 ዓ.ም