የአፋር ሴቶች በማህበር ተደራጅተው በጋራ መስራት መቻላቸው ውጤታማ እያደረጋቸው እንደሚገኝ በክልሉ በብድርና ቁጠባ ተደራጅተው የሚሰሩ ሴቶች ይናገራሉ፡፡ ያላቸውን ጥቂት ጥሪት አሰባስበው፣ ጉልበታቸውን እና ዕውቀታቸውን ደምረው የተሻለ ነገር ለመፍጠር መቻላቸውን ይመሰክራሉ፡፡ ችግሮቻቸውን የሚፈቱበት ብልሃት ለመዘየድ አስችሏቸዋል፡፡
የሚድራ ብድርና ቁጠባ ማህበር ሊቀመንበር ወይዘሮ መዲና ከዳፎ፤ ማህበሩ በ2004 ዓ.ም በሰመራ ከተማ እንደተቋቋመ ያስታውሳሉ፡፡ የማህበሩ አባላት ቁጠባ የጀመሩት በወር 10 ብር በማዋጣት ነበር። በየጊዜው የመዋጮ መጠኑን በማሳደግ በአሁኑ ወቅት ወርሀዊ ክፍያው ወደ 110 ብር ማሳደግ መቻላቸውን ይናገራሉ፡፡
ማህበሩ ሥራ ሲጀምር ለአባላቱ ያበድር የነበረው አራት ሺ ብር ነበር፡፡ ይህንን የገንዘብ መጠን ተበድረው ተጠቅመውበት የሚመልሱ አባላት ድጋሚ ብድር ሲፈልጉ መጠኑን በእጥፍ በማሳደግ ስምንት ሺ ብር እያሻሻለም አሁን 10ሺ ብር የማበደር አቅም ላይ መድረሱን ይገልጻሉ፡፡ አብዛኞቹ የማህበሩ አባላት ብድሮቻቸውን በየጊዜው ገቢ በማድረግ ነጻ ሆነዋል የሚሉት ሊቀመንበሯ፤ አንዳንድ ተበዳሪዎች የተወሰነ ዕዳ ስላለባቸው ይሄንንም በአጭር ጊዜ እንደሚከፍሉ ይናገራሉ፡፡
ወይዘሮ መዲና እንደሚሉት፤ ብድር የሚወስዱ የማህበሩ አባላት ገንዘቡን ለቁም ነገር እንዲያውሉት ማህበሩ የግንዛቤ ስራ ይሰራል፡፡ ብድር የወሰዱ አባላቶችም ፍየል በማርባት ይሸጣሉ፣ ማቀዝቀዣ ገዝተው ለስላሳ መጠጥና ውሃ በመሸጥ ገቢ ማግኘት የቻሉ፣ ሱቅ የከፈቱም አሉ፡፡ ጋሪ ገዝተው በማሰራትም የገቢ ምንጭ ፈጥረዋል፡፡ የክልሉ የማህበራት ማደራጃ ማህበር ሲቋቋም እገዛ እንዳደረጉላቸው የሚናገሩት ወይዘሮ መዲና፤ አደራጅተዋቸው ከአራት መቶ ሺ ብር በላይ ብድር እንደሰጧቸውም ያስታውሳሉ፡፡
የአፋር ሴቶች ቀደም ሲል የነበሩባቸው ችግሮች በአብዛኛው ተቃሏል፡፡ ሆኖም አሁንም ብዙ ቦታዎች ላይ የተለያዩ ችግሮች ይታያሉ፡፡ በተለይ ገጠር የሚኖሩ የአፋር ሴቶች ውሃ በቅርበት ስለማያገኙ ውሃ ለመቅዳት ረጅም ርቀት ይጓዛሉ፡፡ የእህል ወፍጮ በቅርበት ባለመተከሉም እህል በባህላዊ መንገድ በእጃቸው ፈጭተው ቤተሰቡን የመመገብ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ርቀት ተጉዘው የቀዱት ውሃም ንጹህ ባለመሆኑ ልጆቻቸው ለጉዳት እንደሚዳረጉም ይገልጻሉ፡፡ ከብት የማገድና ማለብ፣ ልጅ የማሳደግ ኃላፊነቱ የተጣለው በሴቶቹ ላይ ነው፡፡
ውሃ የማያገኙ የአፋር አካባቢዎች በቅርበት እንዲያገኙ፣ ወፍጮ ቤት ያልተተከለባቸው አካባቢዎች እንዲተከልላቸው ማድረግ ይገባል፡፡ የበቆሎ መፈልፈያ እንዲያገኙ በማመቻቸት የስራ ጫናቸው እንዲቀንስ መሰራት አለበት፡፡ አፋሮች አሁን ሴት ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ገበታ ልከው እያስተማሩ ናቸው፡፡ ብዙ ቦታዎች ትምህርት ቤቶች ተከፍተዋል፡፡ ይሄ ጥሩ ነው። በቀጣይ ዛሬ ችግር የሆኑትን የማስተካከሉ ስራ በትኩረት መሥራት ይገባል ባይ ናቸው ወይዘሮ መዲና፡፡
ቀደም ሲል በአፋር ሴቶች ላይ ከሚደርሱ ጎጂ ድርጊቶች መካከል ግርዛት አንዱ እንደነበር ያስታውሳሉ፤ ይሄ እንዳይፈጸም የሸሪያ ህግ ይከለክላል፤ መንግሥትም ቁጥጥር ያደርጋል፡፡
ሌላው ያለአቻ ጋብቻም በክልሉ ሲፈጸም የነበረ ጎጂ ድርጊት እንደነበር የሚያስታውሱት ወይዘሮ መዲና፤ አሁን መቆሙን ይጠቁማሉ፡፡ ልጃገረዶቹም ሆኑ ቤተሰቦቻቸው እንደማይፈቅዱም ይገልጻሉ፡፡ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች እንዲቀሩ በመንግሥት የተሰራው ሥራ ውጤታማ ሆኗል፡፡ ያለአቻ ጋብቻ እና አብሱማ (የዝምድና ጋብቻ) አብዛኛው ቦታ ላይ እየቀረ ሲሆን በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ የሚፈጸመውም በልጃገረዷ ፍላጎት ላይ መሰረት ተደርጎ መሆኑን ይጠቅሳሉ።
እንደእርሳቸው ማብራሪያ፤ በማህበር መደራጀቱ የአፋር ሴቶች ተጨማሪ ገቢ እንዲኖራቸው አስችሏል፡፡ ሆኖም ከማደራጀት ባለፈ መንግሥት ለየማህበሩ ድጋፍ ሊያደርግ ይገባል፡፡ ‹‹ማህበራችን በቂ የመሥሪያ ቦታ የለውም፡፡ ቢኖረን ከዚህም በላይ መሥራት እንችል ነበር፡፡ ሆኖም ጉዳዩ ለሚመለከተው አካል ጥያቄ አቅርበን ምላሽ አላገኘንም›› ብለዋል፡፡ አሁን እየሰሩበት ያለው ከክልሉ ፋይናንስ ያገኙት ቢሮ ከሁለት ሰው በላይ አያስቀምጥም፡፡ ይሄ ችግራቸው ቢፈታላቸው ብዙ መስራት እንደሚችሉ ይናገራሉ፡፡
«የአፋር ሴቶች ሰላም ፈላጊዎች ነን፡፡ ልጆቻችን በአማን ወጥተው በአማን እንዲመለሱ (በሰላም ወጥተው በሰላም እንዲመለሱ) እንፈልጋለን፡፡ በመሆኑም የሰላም አስከባሪዎችም ነን፡፡ አሁን ብዙ ለውጦች እየመጡ ናቸው፡፡ ሴቶች በፖለቲካ ተሳታፊ እየሆኑ ነው፡፡ ተምረው በተለያዩ የኃላፊነት መደቦች ላይም እየተሰማሩ ይገኛሉ፡፡ በማህበራት በመደራጀት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ መሆን ችለናል። ወደፊትም ከዚህ በላይ ማደግ እንደምንችል ተስፋ አለኝ»ይላሉ፡፡
የማህበሩ መሥራችና አባል ወይዘሮ ሞሚና አሊም፤ የአፋር ሴቶች ከማጀት ወጥተን ገቢ በሚያስገኝ ስራ ላይ መሰማራት አለብን በሚል ተነሳሽነት ማህበሩን ማቋቋም እንደቻሉ ይናገራሉ፡፡ አዋሽ አርባ ላይ በአንድ ወቅት የወሰዱት ስልጠና ስራ ፈጠራን የሚያበረታታ በመሆኑና ከሌሎችም ልምድ ቀስመው መመለሳቸው የሚድራ ብድርና ቁጠባ ማህበርን ለመመስረት በር እንደከፈተላቸው ይጠቅሳሉ፡፡
ማህበሩን ለመጀመር ፈተና እንደነበረው የሚያስታውሱት ወይዘሮ ሞሚና፤ ሴት ልጅ ከማጀት ወጥታ ለመስራት ተጽእኖ ይደርስባት ነበር። አሁን ግን ችግሩ መቀረፉን ይገልጻሉ፡፡ ማህበሩ ከተመሰረተ በኋላ በቁጠባና ብድር የተገኘውን ጥቅም በመመልከት ብዙዎች መቀላቀላቸውን ይናገራሉ፡፡ ማህበሩ የተቋቋመው በ19 ሴቶች ከእያንዳንዳቸው አባላት ከነመመዝገቢያው 70 ብር በተዋጣ ካፒታል ነው።
የማህበራት ማደራጃ ለመነሻ በሰጠው ብድር ስራ የጀመረው ማህበር አሁን ግማሹን ዕዳ መልሶ ወደ 200 ሺ ብር ካፒታል አስቀምጠዋል፡፡ በአሁኑ ወቅትም የማህበሩ አባላት ቁጥር ከ40 በላይ ደርሷል፤ ሁሉም አባላት ብድር ወስደው ተጠቃሚ መሆን ችለዋል፡፡
በክልሉ አዲስ አመራር ተደራጅቶ ወደ ተግባር መግባቱ ሴቶችን ተጠቃሚ በማድረግ በኩል የነበሩ ችግሮች እንደሚቀረፍ ተስፋ አድርገዋል፡፡
አዲሶቹ አመራሮቹ የተማሩ መሆናቸውና ሴቶች ወደ አመራርነት መምጣታቸው እንዳስደሰታቸውና ለውጥ ይመጣል የሚል ተስፋ እንዲሰንቁ እንዳደረጋቸውም ይናገራሉ፡፡
ወደፊት የመሥሪያ ቦታና የቢሮ ችግሮቻችን እንደሚቀረፉ ተስፋ አለኝ የሚሉት ወይዘሮ ሞሚና፤ የማህበሩ ስራ እንዲስፋፋ፣ ሌሎች የአፋር ሴቶች ተደራጅተው ተጠቃሚ እንዲሆኑ ፍላጎት መኖሩን ይጠቁማሉ፡፡ የአፋር ሴቶች በስራ ፈጠራ ሊሰማሩና ገቢ ሊፈጥሩ እንደሚገባም ወይዘሮ ሞሚና ይመክራሉ፡፡
የአፋር ክልል የህብረት ስራ ማህበራት ማደራጃና ማስፋፊያ ጽህፈት ቤት በተለያዩ የስራ አይነቶች የህብረት ስራ ማህበራትን የማደራጀት ስራ እንደሚሰራ በጽህፈት ቤቱ የህብረት ስራ ማህበራት ማደራጃና ማስፋፊያ ዳይሬክተር አቶ አሚን ሰይድ ይናገራሉ፡፡ የክልሉ ሴቶች በገንዘብ ብድርና ቁጠባ የህብረት ስራ ማህበራት፣ በሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት፣ በእንስሳት ግብይት፣ በመኖ ልማት፣ በእደ ጥበባትና መሰል የሙያ ዘርፎች የህብረት ስራ ማህበራት ተደራጅተው ውጤታማ እየሆኑ እንደሚገኙም ያመለክታሉ፡፡
እስካሁን በክልሉ 1ሺ 500 ህብረት ስራ ማህበራት ተደራጅተዋል፡፡ እነዚህ ከ46 ሺ በላይ አባላት አፍርተዋል፡፡ አብዛኛው ሴቶች የቁጠባ ባህልን ለማዳበር ተደራጅተው የራሳቸው ቁጠባ መልሰው ለአባላት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ አባላትም አዋጭ መስክ ላይ በመሰማራት ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን እየለወጡ ናቸው፡፡ የማበደር አቅማቸውን ለማሳደግ የድጋፍ ገንዘብ እየወሰዱ ራሳቸው ተለውጠው ለማህበሩ የሚመልሱበት ሁኔታ ይመቻችላቸዋል፡፡ የራሳቸውን ውስን ሃብት እየቆጠቡ ህይወታቸውን መቀየር ችለዋል ይላሉ አቶ አሚን ፡፡
ተደራጅተው ገንዘባቸውን፣ ጉልበታቸውንና ዕውቀታቸውን አስተባብረው የተሻለ ነገር ለመፍጠር፣ ችግሮቻቸውንም ለመፍታት የሚችሉበት ተቋም ሆኗል፡፡ ችግሮቻቸውንም በጋራ ይቀርፋሉ፡፡ በመደራጀታቸው ህጋዊ እውቅና፣ የሙያ ድጋፍ፣ አገልግሎት ያገኛሉ፡፡ ከመንግሥት የመስሪያ ካፒታል ተጠቃሚ ናቸው ሲሉም ይናገራሉ፡፡
የአፋር ሴቶች ቀደም ሲል ይደርስባቸው ከነበረው ተጽእኖ ተላቅቀው በመደራጀት ከማጀት በመውጣት ተጠቃሚ መሆናቸው ይበል የሚያሰኝ ተግባር ነው፡፡ ወደፊትም የበለጠ ውጤታማ ለማድረግ ድጋፍና ክትትል ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ በተለይም የሚመለከተው አካል በቂ የመስሪያ እና ለቢሮ የሚገለገሉበትን ስፍራ በማመቻቸት ችግሮቻቸው ማስወገድ የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ ሊያደርግ ይገባል፡፡ ጅምሩን በማስፋፋትም በርካቶችን በማደራጀት ተጠቃሚ ማድረግ ላይ መተኮር ይኖርበታል፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 11/2011
ዘላለም ግዛው