የልጆች ጤናማ ዕድገት በሚደረግላቸው ሁለንተናዊ እንክብካቤ ላይ ይወሰናል፡፡ እንክብካቤው የጤና አጠባበቅን፣ ተገቢ የአመጋገብ ስርዓትን፣ የግልና የአካባቢ ንጽህናና ደህንነትን፣ ፍላጎትን መሰረት ያደረገ እንክብካቤ መስጠትን እና ቅድመ መደበኛ ትምህርት ማረጋገጥን ያጠቃልላል፡፡ ከእርግዝና ጀምሮ ልጆች ከተወለዱ አስከ ስምንት ዓመት እድሜ ድረስ የሚደረግ ሁሉን ያማከለ እንክብካቤ ለልጆች አካላዊ፣ አእምሯዊና ስነ ልቦናዊ ዕድገት ወሳኝ ሲሆን ለሀገር ምርታማ ዜጋ ለማፍራትም ትልቅ መሰረት ይጥላል፡፡
በመጀመሪያዎቹ ጥቂት ዓመታት አንጎል ለመጥፎም ይሁን ለጥሩ አካባቢያዊ ተፅእኖ ተጋላጭ መሆኑን የጤና ባለሙያዎች ይገልፃሉ፡፡ በዚህ ጊዜ አንጎል በተለይም ለተመጣጠነ የምግብ እጥረት፣ በመርዛማ ነገሮችና በጭንቀት ምክንያት ለሚከሰት አደጋ በይበልጥ ተጋላጭ ነው ተብሎም ይታሰባል፡፡ ይህም ልጆች ወደፊት በትምህርታቸው ዝቅተኛ አፈፃፀም እንዲኖራቸውና በመጨረሻም ትምህርት እንዲያቋርጡ ሊያድርጋቸው ይችላል፡፡
ችግሩ በረጅም ጊዜ ሂደትም ገቢያቸውን ይቀንሳል፤ የጤና ችግሮችን ያስከትላል፤ ከፍተኛ ወንጀሎች ላይ መሳትፍን ያመጣል፤ በትውልድ መካከልም ቀውስን ያስክትላል፡፡
ኢትዮጵያን ጨምሮ አነስተኛና መካከለኛ ገቢ ባላቸው ሀገራት የሚኖሩ ህፃናት ለዘርፈ ብዙ ችግሮች የተጋለጡ መሆናቸው በጤንነታቸው፣ በደህንነታቸውና በትምህርታቸው ላይ ከፍተኛ ተፅእኖ እንደሚያሳደር መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በነዚሁ ሀገራት ውስጥ ከሚኖሩ ከ 5 ዓመት እድሜ ክልል በታች ከሆኑ ህፃናት መካከል 43 በመቶው በተመጣጠነ የምግብ እጥረትና ድህነት ምክንያት በዕድገትና መዳበር እምቅ አቅማቸው ላይ እንደማይደርሱም በተለያዩ ጊዚያት የተሰሩ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡
በኢትዮጵያም ከ 5 ዓመት የዕድሜ ክልል በታች ካሉ ህፃናት ውስጥ 38 በመቶው በመቀንጨር የጤና ችግር ይሰቃያሉ፡፡በኢትዮጵያ በቀዳማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ላይ የተለያዩ ተግባሮች ቢከናወኑም፣አመርቂ ናቸው ተብሎ እንደማይታመን ይገለጻል፡፡
በተለይ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት በጉዳዩ ዙሪያ በቂ ግንዛቤ አለመያዛቸው፣ ጉዳዩ በሚመለከታቸው የዘርፍ መስሪያ ቤቶች መካከል ቅንጅታዊ አሰራር አለመኖሩና ከዘርፍ መስሪያ ቤቶችና የልማት አጋሮች ጋር በመሆን የህፃናት እንክብካቤን በስፋትና በፍትሃዊንት ማዳረስ አለመቻል አሁንም የዘርፉ ተግዳሮት ሆነው መቀጠላቸውን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ወይዘሮ አበባ ሲሳይ በአማራ ክልል ጤና ቢሮ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ባለሙያ ናቸው፡፡ እርሳቸው እንደሚሉት በክልሉ በቀዳማዊ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ላይ በርካታ ተግባሮች እየተከናወኑ ይገኛሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ በልጆች አእምሯዊ ዕድገት ላይ የሚሰራ ስራ ሲሆን፣ ጨዋታን መሰረት ያደረገ የማስተማር ስነ ዘዴን በቅድመ መደበኛ ትምህርት ፕሮግራም ውስጥ በማካተት ዕድሚያቸው ከ 4 አስከ 6 ዓመት የሆኑ ልጆች እንዲማሩ ሲደረግ ቆይቷል፡፡ መምህራንም የማስተማር ስነ ዘዴውን አውቀው ትምህርቱን ለተማሪዎቻቸው እንዲሰጡ የአሰልጣኞች ስልጠና ተሰጥቷቸዋል፡፡ የመማሪያ መፃህፍቶችም ከክልሉ ነባራዊ ሁኔታ ጋር ጥቅም እንዲሰጡ ተደርጓል፡፡
ባለሙያዋ እንደሚገልፁት በልጆች አእምሯዊና አካላዊ ዕድገት ላይ እየተሰሩ ያሉ ስራዎች ቢኖሩም አብዛኛዎቹ ህፃናት ትምህርታቸውን ስለሚያቋርጡ የትምህርት ስነ ዘዴውን በሚፈለገው መጠን ማስኬድ አልተቻለም፡፡ በክልሉ ካለው ከፍተኛ የህፃናት ቁጥር አንፃር ሲታይም ስራው አጥጋቢ ነው ማለት አይቻልም፡፡ የትምህርት ስነዘዴው ለማህበረሰቡ በሚገባ አለመተዋወቁና በቂ ትኩረት አለማግኘቱ እንዲሁም የትምህርት ባለሙያዎች ለቅድመ መደበኛ ትምህርት የሰጡት ትኩረት አናሳ መሆን ስራው ውጤታማ እንዳይሆን አድርጎታል፡፡
አብዛኛው ወላጅም ከመደበኛ ትምህርት በፊት የቅድመ መደበኛ ትምህርት ለህፃናት አስፈላጊ መሆኑን እንደማይገነዘብ የገለጹት ባለሙያዋ፣ ይህም ለስራው ተጨማሪ እንቅፋት ሆኗል ይላሉ፡፡ በዚህና በመሳሰሉት ምክንያቶች ህፃናቱ አመቺ የመማር ማስተማር አካባቢ ስለማይገጥማቸውና ስልቹ ስለሚሆኑ ከትምህርት ገበታቸው ለመቅረት እንደሚገደዱም ያመለክታሉ፡፡
በቀዳማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ላይ ጉዳዩ ከሚመለከታቸው የዘርፍ መስሪያ ቤቶች ጋር ትስስር በመፍጠር ከመስራት አንፃርም ሰፊ ክፍተት እንደነበር የሚያስታውሱት ባለሙያዋ፤ በጋራ ለመስራት በባለድርሻ አካላት መካከል የመግባቢያ ሰነድ ተፈርሞ እንደነበርም ይጠቅሳሉ፡፡ በመግባቢያ ሰነዱ መሰረት ባለመሰራቱ ውጤት ማምጣት እንዳልተቻለም ይናገራሉ፡፡
እንደ ባለሙያዋ ገለፃ፤ በአሁኑ ወቅት በቀዳማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ላይ ካባለድርሻ አካላት ጋር በማቀድና የቴክኒክ ኮሚቴ በማዋቀር በትስስር ለመስራት ጥረት እየተደረገ ይገኛል፡፡ በተለይም የማስተማር ስነ ዘዴውን ለማህበረሰቡና ለወላጆች በስፋት የማስተዋወቅ ሥራ እየተሰራ ነው፡፡ በቀጣይም ለህፃናት ሳቢና ምቹ የትምህርት አካባቢ እንዲኖርና የመምህራን የማስተማር ስነዘዴም ህፃናትን የማያሰለች እንዲሆን ዓለም አቀፍ የማስተማር ስነ ዘዴ ተሞክሮዎችን በማየት ተግባር ላይ እንዲውሉ ይደረጋል፡፡
በትግራይ ክልል ጤና ቢሮ የእናቶችና ህፃናት ኬዝ ቲም አስተባባሪ አቶ ከበደ አምባዬ እንደሚገልፁት፤ ቀደም ሲል በክልሉ በህፃናት ስርዓተ ምግብ ዙሪያ የቆየ ሲሆን፣ በቀዳማይ የልጅነት ዕድገትና መዳበር ላይ ግን በበቂ ሁኔታ አልተሰራም፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው በቀዳማይ የልጅነት ዕድገትና ማዳበር ላይ በዘርፍ መስሪያ ቤቶች በኩል በቂ ግንዛቤ ባለመኖሩና ፕሮግራሙን በማስፈፀም ረገድ የእያንዳንዱ ዘርፍ ደርሻ ምን እንደሆነ ባለመታወቁ ነው፡፡
የቀዳማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ቀደም ሲል የነበረውን የስርዓተ ምግብ አሰራር እንደሚያጠናክር የሚገልፁት አስተባባሪው፤ፕሮግራሙን በሚፈለገው ልክ ለማስፈፀም ጉዳዩ የሚመለከታቸው የዘርፍ መስሪያ ቤቶች በጋራ በማቀድ የሚጠበቅባቸውን ድርሻ በቅንጅት ሊወጡ ይገባል ይላሉ፡፡ በአሁኑ ወቅትም ከክልል ጤና ቢሮ ማኔጅመንት ኮሚቴ ጋር በመሆን በቀዳማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ላይ ውይይት መደረጉን ጠቅሰው፣ ባለድርሻ አካላትም ከሚመለከታቸው የጤና ቢሮ ኃላፊዎች ጋር ውይይት እንዲያካሂዱ እቅድ መያዙን ይጠቁማሉ፡፡
አስተባባሪው እንዳሉት፤ በቀጣይም በባለድርሻ አካላት ቢሮ ኃላፊዎች፣ በሃይማኖት መሪዎች፣ በወረዳ ጤና ጽ/ቤት ኃላፊዎችና ጤና ተቋም ኃላፊዎች አማካኝነት በቀዳማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጥ መድረኮች ይካሄዳሉ፡፡ በትምህርት ቤቶች ጤናማና ምቹ የመማር ማስተማር ሂደት እንዲኖር ይሰራል፡፡ እናቶች ሲወልዱ በስራ ቦታቸው የህፃናት ማቆያዎች እንዲዘጋጁላቸው ለማድረግ መመሪያ ይዘጋጃል፡፡ እያንዳንዱ የዘርፍ መስሪያ ቤትም ፕሮግራሙን ለማስፈፀም በጀት እንዲይዝ ይደረጋል፡፡
የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ሊያ ታደሰ እንደሚገልፁት፤ የጤና ዘርፍ ትራንስፎርሜሽን እቅድ ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች ውስጥ የእናቶችና የህፃናት ጤና አገልግሎት ይገኝበታል፡፡ ከዚህ አኳያም በተለይ የጨቅላና ዕድሚያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆኑ ህፃናትን ህመምና ሞት ለመቀነስ በማህበረሰብና በጤና ተቋማት በርካታ ስራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ፡፡
ሚኒስትር ዴኤታዋ፤ በዝቅተኛና መካከለኛ ገቢ ባላቸው ሀገራት ከሚኖሩና ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች ከሆኑ ህፃናት ውስጥ 250 ሚሊየን ያህሉ በአግባቡ እንክብካቤ ባለማግኘታቸው በዕድሚያቸው ልክ መድረስ የሚገባቸው የአካልና የአእምሮ ዕድገት ደረጃ ላይ መድረስ እንደማይችሉ ጥናቶችን ጠቅሰው ያብራራሉ፡፡ በኢትዮጵያ አብዛኛዎቹ የጤና ፕሮግራሞች አስከቅርበ ጊዜ ድረስ ትኩረት ያደረጉት ዋና ዋና ገዳይ በሽታዎችን መከላከልና ማከም ላይ ብቻ እንደነበር ጠቅሰው፣በዚህም ምክንያት በቀዳማይ ልጅነት እድገትና መዳበር ፕሮግራም ላይ በሚፈለገው መጠን እንዳልተሰራ ይገልጻሉ፡፡
በዘላቂ የልማት ግቦች ውስጥ ትኩረት ከተደረገባቸው የህፃናት ጤና አጀንዳዎች ውስጥ አንዱ የቀዳማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበርና ፕሮግራም መሆኑን የሚጠቅሱት ሚኒስትር ዴኤታዋ፤ ፕሮግራሙን በ2030 እ.ኤ.አ ለማሳካት እየተሰራበት እንደሚገኝ ይናገራሉ፡፡
እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ማብራሪያ፤ የጤናው ዘርፍ አጀንዳ ትኩረት በዚህ ጉዳይ ላይ ያተኮረ መሆኑ ተገቢ ቢሆንም፣ በህፃናት ጤና ላይ ብዙ መሻሻሎች እየታዩ በመሆኑ በአሁኑ ወቅት ወደ ሁለንተናዊ የህፃናት ዕድገት መሸጋገር አስፈልጓል፡፡ ይህም ተገቢ የጤና አጠባበቅን፣ በቂና ተመጣጣኝ ምግብ ማግኘትን፣ ፍላጎትን መሰረት ያደረገ ምላሽ የሚሰጥ እንክብካቤ ማድረግና የደህንነትና ጥበቃ ዘርፎችን ያካትታል፡፡
እንደ ሚኒስትር ዴኤታዋ ገለፃ፤ በነዚህ ዘርፎች ላይ አተኩሮ መስራት ህፃናት ወደፊት ለሚኖራቸው ስኬታማ ህይወት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ከማድረጉ በተጨማሪ ለሀገር ብልፅግናም ከፍተኛ ሚና ይጫወታል፤ የሰው ኃይል ካፒታል ኢንቨስትመንትን በመመለስ ረገድም ትልቅ አቅም ይኖረዋል፡፡ ሆኖም በቀዳማይ የልጅነት ዕድገትና ማዳበር ላይ መስራት የተለያዩ ዘርፎችን ንቁ ተሳትፎና ቅንጅታዊ አሰራር ይጠይቃል፡፡ በተለይም የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ የሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴና የትምህርት ሚኒስቴርን የመሳሰሉ የመንግሥት ሴክተር መስሪያ ቤቶች በጋራ ሊሰሩ ይገባል፡፡ ከዚህ ውጪ የሆኑ ሴክተር መስሪያ ቤቶችና የግል ተቋማትም በጥምረት መስራት ይጠበቅባቸዋል፡፡
ሚኒስትር ዴኤታዋ እንደሚሉት፤ ከቅድመ ልደት አስከ ሰባት ዓመት የሚሆኑ ህፃናት መብትና ደህንነትን ለማስጠበቅ የሚያስችል ሀገራዊ የፖሊሲ ማዕቀፍ የተዘጋጀ ቢሆንም፣ በሚፈለገው ደረጃ ተግባራዊ እየሆነ ባለመሆኑ ፖሊሲው ከቀዳማይ የልጅነት ዕድገትና መዳበር ፕሮግራም ጋር አብሮ ተግባራዊ እንዲሆን በእቅድ ውስጥ ማካተት ያስፈልጋል፡፡
ይህንን የፖሊሲ ንድፈ ሃሳብ ተግባራዊ ለማድረግ ባለፉት በጀት ዓመታት የተጀመሩ እንቅስቃሴዎች ቢኖሩም፣ የቀደማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ፕሮግራምን አጠናክሮ ለማስቀጠል የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት የሚሰራ ይሆናል፡፡
በቀዳማይ ልጅነት ዕድገትና መዳበር ላይ በቅርቡ ለመጀመሪያ ጊዜ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሴክተር መስሪያ ቤቶችን ያሳተፈ ሀገር አቀፍ አወደ ጥናት መካሄዱ ይታወሳል፡፡ በአውደ ጥናቱ ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ ከሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴርና ከትምህርት ሚኒስቴር የተውጣጡ የስራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ተገኝተው ቅንጅታዊ አሰራር ከፍተኛ ጥራት ላለው ቀዳማይ የልጅነት ዕድገትና መዳበር ስኬት ቁልፍ ሚና አንዳለው በመገንዘብ ለመፈፀም የጋራ አቅጣጫ አስቀምጠዋል፡፡
አዲስ ዘመን ታህሳስ 23/2011
አስናቀ ፀጋዬ