አንድ ሥራ አጥቶ ረጅም ጊዜ የቆየ ሰው ነው አሉ። ሁልጊዜ በራሱ ይማረራል፤ ተምሬ ሥራ አጣሁ።ደህና ነጥብ ኖሮኝ ለሥራ አልታደልኩም ብሎ ብቻ ይማረራልቨ መፈጠሩንና ፈጣሪውን እንዲሁ እያነሳ ይበሳጫል፤ ይበሰጫጫል። አንድ ቀን አሁንም ሥራ ፍለጋ ዘወርወር ሲል በአንድ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት በእሱ የትምህርት መስክ አረጋውያንን ለመንከባከብ የሚል ማስታወቂያ ወጥቶ ይመለከታል።
ሄዶም ይመዘገብና ለፈተና ቀነ ቀጠሮ ተቆርጦለት ይመለሳል። ፈተናው በሚሰጥበት ማለዳ ላይ አንድ አዛውንት ወደ ቢሮው መሻገሪያ አካባቢ ቆም ብለው ሰዎች እንዲያሻግሯቸው ይጠይቃሉ። ብዙም አላስተዋላቸውም። በዕለቱ ታዲያ በጠዋት ሮጥ ሮጥ እያለ መንገድ ሊያቋርጥ ሲል አዛውንቱ ያገኙት እና ልጄ እባክህ አሻግረኝ ይሉታል፤ እሱ ግን እሳቸውን ሳሻግር (ፈጠን ብለው ስለማይራመዱ) ሰዓት ያልፍብኛል ብሎ ስላሰበ መልስ ሳይሰጥ ያልፋቸዋል። እሳቸውም አዝነው በቆሙበት ሆነው የሌላ ሰው መምጣት ይጠባበቁ ጀመር።
ሌላው ወጣትም እንዲሁ ፈጠን ፈጠን ብሎ ይራመዳል ደግሞ የእጅ ሰዓቱን መለስ አድርጎ ይመለከታል ከሩቅ አስተዋሉት። እኔን ለመጎተት ሰዓትም የለውም መሰለኝ ብለው እያሰቡ ደግሞ ተስፋ ባለመቁረጥ አጠገባቸው ሲደርስ “እባክህ ልጄ” ሲሉት ባልሰማ አለፋቸው። አሁንም አዝነው ሦስተኛውን መጪ መጠባበቅ ቀጠሉ ሦስተኛው ሰውም በተመሳሳይ እየተራመደ ነው፤ አጠገባቸው ደርሶ “ልጄ” ሲሉት እርምጃውን ገታ አድርጎ “አቤት” ብሎ ማድመጡን ቀጠለ።
“እባክህን አሻግረኝ” አሉት “እሺ አባቴ ብሎ እጃቸውን ይዞ አሻገራቸው”። የፈተናው ሰዓት ደርሶ ለተፈታኞች የተሰጣቸው ፈተና የነበረው እኛን አዛውንት ማሻገር ነበር እናም የመጀመሪያዎቹ ሁለቱ ወድቀው ሦስተኛው ሰው ማለፉ ተነገራቸው። ምክንያቱም የሚቀጠሩት አዛውንት ሊንከባከቡ ነው፤ ለእነሱ ክብር መስጠትና መንከባከብ የሚችል ፍላጎቱም ያለው ነው የሚያስፈልገው።
ይሄንን በየትኛውም ቦታ ላይ ያልተወጣ ሰው እዛም ተቀጥሮ ቢገባ ያለው የውስጥ ባህሪ የታዛዥነት፣ የተንከባካቢነት እና የአዛኝነት ካልሆነ የሚሰው ሥራ ለደመወዝ እንጂ በፍላጎት አይሆንም። ይሄ ደግሞ በሥራ ላይ የሥራ ሰዓት ከመቁጠር ያለፈ ውጤት አያመጣም። ለአዳዲስ ነገርም አያነሳሳም። ሥራን መስራት ከራሥም ኃላፊነት በተጨማሪ ቅንነትን፣ ተነሳሽነትን … ይጠይቃል። ቅን ሰው ከሥራው በላይ ይሰራል። የእኔ ሥራ ይሄ አይደለም ያ ነው እያለ የሚኮፈስ ከሆነ ደግሞ እንኳን የተሻለ ያልተጠበቀ ሥራ ቀርቶ የራሱንም አድምቶ ሊወጣ አይችልም።
የጠቅላይ ሚኒስትሩን “እድሳት ከቢሮ እስከ ሀገር” የሚለውን ዶክመንታሪ ፊልም አየሁት። የጠቅላዩን ሀሳበ ሰፊነት እና ትጋት አደነቅሁ። ለወሬ እና ለወሬኛ እንደሳቸው ጆሮውን የደፈነ ብቻ ነው ብዙ አስቦ ብዙ መራመድ የሚችለው። ሌሎችም ይሄንኑ እያደረጉ እንደሆነም አምናለሁ። ይሰራሉ ይተቻሉ። ከተሳሳቱ ይታረማሉ። ከወደፊት ትልማቸው ግን ንቅንቅ አይሉም። እኛም “ትልቅ ነገር እናልማለን፣ ትልቅ ነገር እናስባለን፣ ነገር ግን ከትንሽ እንጀምራለን፤ ያንን በፍጥነት እናሳካለን፣ ወደፈለግንበት እንደርሳለን።” ያሉትን ይዘን መስራት ከጀመርን ከምናስበውም በላይ ውጤት እናመጣለን።
ነገር ግን ሥራ ሲሰራ እንቅፋት እንደማይጠፋ ይታመናል፤ እንቅፋት ያደነቃቅፋል። ነገር ግን እንቅፋቱ የከፋ አደጋ እንዳያደርስ መንገድ መንገዱን እያዩ መራመድ ይጠቅማል። የሥራ ያለህ ብሎ ሥራ የሚያማርጥ፣ ሥራ ለመቀጠር ብቻ የሚያስብ ባሰበው መንገድ መቀጠል እንደማይችል ቆም ብሎ ከሌሎች በመማር መንገዱን ማስተካከል ይኖርበታል። ነገር ግን ለሚሰራ መንገድ የጠረገ፣ ያስተካከለ ሥራ ሰራ ነው የሚባለው። መንገዱን አመቻችቶ በዛው መንገድ መቀጠሉ አይቀርምና።
አንድ ጸሐፊ “አርፈህ ሥራህን ሥራ” የሚል ጽሑፍ ጽፎ አነበብኩት። እኔም እውነት እኮ ነው ለምን አርፈን ሁላችንም በየተሰማራንበት መስክ ሥራችንን አንሰራም? ለምን ራሳችንን በሥራ አናሸንፍም? ለምን ከመስራት ይልቅ በማውራት እንዲጨበጨብልን እንፈልጋለን? ለምንስ ሥራውን የሚሰራውን ሰው ወይም አካል ስንንቅ ስናንቋሽሽ፣ ስንዘነጥል ስንዘነጣጥል፤ ስንተች እንውላለን? ለምን ለሚሰራ ሰው እንቅፋት ሆነን ለማደናቀፍ እንሞክራለን? ግን ለምን…ለምን… ስል ማሰብ ቀጠልኩ። በኋላ መልስም ባይሆንም እንደመልስ ያሰብኩት “ራሳችን ሥራ ስለማንሰራ” የሚል ነበር።
አንሰራም፤ የተሰራ ሥራ ደግሞ እናጣጥላላለን፣ እናሳንሳለን… ለተቀማጭ ሰማይ ቅርቡ ነው እንደሚባለው ማለቴ ነው። ከተሳሳትኩ እንደለመድኩት ጊዜው የይቅርታ ነው በሚለው እሳቤ ይቅር በሉኝ። ግን ለዚህ የሚሆን ብዙ ብዙ ነገር ማንሳት ይቻላል። ሰርቶ ሳይሆን አውርቶ አደሮች መኖራቸውን፤ የሚሰራን አመስግነው ሳይሆን አጥላልተው፤ አጠልሽተው ሕዝብን ለማሳመን የሚጥሩ፤ ሕዝብን ለክፉ ዓላማ ለማነሳሳት ወይ ደግሞ የሰውን ንፁህ ልቦና ለማቆሸሽ የሚሰሩ መኖራቸውን አትዘንጉት። ምን ለማትረፍ ካላችሁ መልሱ ብዙ ነው። ውበት እንደተመልካቹ እንዲሉ።
ሁሉም ከራሱ የግል ጥቅም፣ ፖለቲካ፣ ሃይማኖት፣ ዘር፣… ሊነሳ ይችላል። አንዳንዱ ደግሞ ምንም ነገሩ ሳይገባው ሌላው ስላለ ብቻ ይሆናል ለእንቅፋቱ ተባባሪ ለመሆን የሚነሳው። ለዚህ አባባል ምን ማስረጃ አለ የምትሉ ከሆነ ያው በየድረገጹ የምናየው የሚሰነዘረው ሀሳብ ብቻ አንዱና በቂ ምስክር አይደል!። የሚሰራን፣ የሚለፋን፣ የሚጥርን አካል ስም ለማጉደፍ የሚደረገው ሩጫ ሥራ ሰሪዎቹ ከለፉበት ሥራ በላይ በጥበብ የሚደረግ ነው። ግን እኮ ቀላል ነገር አለ፤ እከሌ እከሌት ከሰሯቸው በላይ የሚበልጥ የሚታይ ነገር ሰርቶ የሁሉንም ክብር ወይም ዝና መሰብሰብ ይቻል የለ እንዴ? ይሄ ካለ ታዲያ የግለሰቦችን የተቋማትን ልፋት ሜዳ በሚያስቀር መልኩ ለመተቸት መነሳቱ ምን ያስፈልጋል?
ይሄን ማለቴ ግን ምንም ነገር የሰራም ሆነ ያልሰራ አይተቸም ከሚል ሀሳብ ተነስቼ እንዳልሆነ ይያዝልኝ። ትችት አስፈላጊ ነው። እንዲያውም እኮ በእኛ ባህል “የጎረቤት ምቀኛ አታሳጣኝ” የሚባል አባባል አለ። ይሄ ከክፋት የመነጨ አይደለም። ጎረቤት የዋህ፣ አዛኝና ለጋስ… ከሆነ እኔ እራሴን አልችልም። ዕቃም ለመዋስ ከዚያ ቤት ስል፤ ምግብ እነሱ ሰርተዋል ስል እኔ ቤት አልይዝም። ለማደግና ለመሻሻል አልጣጣርም። ስለዚህ በመንፈሳዊ ቅናት በመነሳሳት ሰርቼ ለመብለጥ ለመለወጥ እንዲህ ያለው ጎረቤት ያስፈልጋል ከሚል እሳቤ ይመስለኛል። ደግሞም ነው እንጂ ሰው በራሱ ላይ ጠላት ስጠኝ የሚል ጸሎት አይጸልይም።
ትችትም ለሚሰራ ሰው እንዲያውም ያልታየውን እንዲያይ ይበልጥ ያበረታታዋል። ይበልጥ እንዲሰራም ያነሳሳዋል። ይሄ ክፋት ሳይሆን ጥቅም ነው። ነገር ግን ችግሩ የሰናፍጭ ቅንጣት ታክል ለሕዝብና ለሀገር ምንም ያላደረገ ሁሉ እየተነሳ የተሰራን ሥራ፤ የተደረገ ጥረትን ፤ የነገውን ዕቅድ እና ተስፋ አፈር ከድሜ ሲደበላልቀው ማየትም ሆነ መስማት ግን ባይቆጭ ያንገበግባል እንደሚባለው ይሆናል። ይህን ሳነሳ አንድ የረሳሁት ነገር መኖሩ ታወሰኝ።
ክፋት አመንጪ የክፋት መርዙን ቢረጭ ብቻውን የትም ሊያደርሰው አይችልም። የክፋትን ሀሳብ ሸማቹ ነው ሌላኛው ክፉ ማለቴ ነው። ጥሬውን ከብስል፣ ደቃቁን ከአንኳር፣ ጣፋጩን ከመራራው መለያ፣ ማገናዘቢያ፣ ማመዛዘኛ የለም እንዴ ብዬ ብጠይቅ ደስ ባለኝ። የሰጪ ብቻ ሳይሆን የተቀባይም ችግር አለ ማለቱ በደፈናው ሳይበቃን አይቀርም። እና የማስተዋል ሚዛን ያስፈልገናል።” አሁን ምን ያደርጋል ድስት ጥዶ ማልቀስ አስቀድሞ ነበር መጥኖ መደቆስ” የሚባለው እንዳይሆን ማለቴ ነው። ሰላም!
አዲስ ዘመን መስከረም 18/2012
አልማዝ አያሌው