ከራሳችን ጋር ሙግት ስንገጥም ከሃሳባችን ጋር መስማማት ሲሳነን የሚጎድልብን ነገር ይበረክታል። ከግጭት ከባዱ እና የገዘፈው ግጭት ከራስ ጋር የሚሞግቱት፤ ከግል ጋር የሚጣረሱበት ነው። በህይወት ሳሉ ከራስ ጋር መጣላትን የመሰለ የከበደና ትልቅ ፈተና ያለ አይመስለኝም። ከህሊና ፍርድ ጋር እየተሟገቱ ከራስ ጋር ያለ ስምምነት መኖር ምንኛ ከባድና የከፋ ስለመሆኑ መገመት ከባድ አይደለም። ሦስተኛ ወገን አስታራቂ የሌለው የማያቆም ግጭት በራስ ውስጥ የሚፈጠር የመሸናነፍ ፉክክር፤ ከልክ በላይ ህመም የሚፈጥር መጣረስ፤ ለሸምጋይ የሚቸግር ተቃርኖ፤
ከራሱ ጋር የሰመረ ስምምነት ያለው አካባቢያዊ ሁኔታውን በመልካም ነገር መለወጡ አይቀሬ ነው። ከእርስ በእርስ ግንኙነትና ጉድኝት ስምረት ቀድሞ ከራሳችን ጋር የምንፈፅመው የስምምነት ቃል ኪዳን ያህል ትልቅ ሚና አለው። የማህበረሰባችን ሁለንተናዊ አተያይና በጎ የሚባሉ እሴቶች ዛሬ ላይ “የት ገቡ?” የሚያሰኘን አጋጣሚ የሚፈጠረው እኮ ከእርስ በርስ መተዛዘንና መግባባት በፊት ለራስ ክብር መስጠትና ከራስ ጋር በመልካም ሁኔታ ላይ መግባባት ስላልቀደመ ነው።
ሰሞኑን ከራስ መጣላታችን ከግላችን ጋር እርቅ መፍጠር ያቃተን መሆናችንን በብዙ ማስረጃ ፍንትው ብሎ በመታየት ላይ ነው። እውነት ግን ሰው ከራሱ ጋር ሳይታረቅ በምን መልኩ ነው ከሌላው ጋር እርቅ መፍጠር አሊያም ደግሞ መግባባት የሚችለው። ፈፅሞ ከራስ ጋር ያለን መግባባት ከራስ ጋር ያለን የረጋ ስሜት ከራስ ጋር ያለን መስከን ነው ሰላማዊ የሚያደርግ ያ ደግሞ ከራስ ከፍ ብሎ ለሌላም ይተርፋል።
በጎ እሳቤ የሚፈጥር አዎንታዊ አስተሳሰብ የሚመነጨው ከራስ ጋር ባለ ሰላም ውስጥ ነው። በተናወጠ ማንነት ውስጥ መስከንን መጠበቅ እንዴት ይቻላል? ያልሰከነ ግለሰብ በረጋ ማህበረሰብ መሀል ላይ ተገኝቶ መፍትሄ የሚወልድ በጎ ሀሳብ እንዴት ሊፈጥር ይችላል? ይሄን መጠበቅ ያልዘሩትን የማጨድ ያህል የማይጨበጥ ህልም ማለምን ይስተካከላል።
ከስህተት ለመተራረም መመካከር ወሳኙ ነጥብ አይደል? አንዱ ካንዱ ጋር የመመካከር ዙፋን ላይ ለመቀመጥ ከራሱ ጋር መክሮ መጨረስ፤ ከራሱ ጋር መስማማት ማስቀደም ደግሞ ግድ ይለዋል። ከራስ ጋር የመጋጨት ትልቁ መንስዔ ደግሞ ተግባርን በትክክል አለመወጣት ወይም ስህተት በምንለው ተግባር ውስጥ መዘፈቃችን ይመስለኛል። የሰራነው በጎ ያልሆነ ተግባር ከራሳችን ጋር ለመጣረስ ትልቅ መነሻ ይሆነናል።
አንድ ፖሊስ በአንድ ምሽት በጥበቃው ስራ ላይ ሳለ በአንድ ሱቅ በር ሲያልፍ ከፍ ያለ የጭቅጭቅ ድምፅ ይሰማል። ፖሊስ ፀጥታን ማስጠበቅ፤ የህብረሰተቡን ደህንነት ማረጋገጥ ዋነኛ ስራው ነውና ይኸኛውም ይህንን ጠንቅቆ የተረዳና ሙያውን የሚያከብር ነበር። ቆም ብሎ የሰማውን ከፍ ያለ ጭቅጭቅ ለማጣራት ይሞክራል። ጭቅጭቁ ከፍ እያለ መሄድን ያስተዋለው ፖሊስ ወደ ሱቁ ጠጋ በማለት ምን እንደተፈጠረ ይጠይቃል። በሱቁ ውስጥ ያለው ግለሰብም ምንም እንዳልተፈጠረ ይገልፅለታል። ፖሊሱም ጭቅጭቅ ሰምቶ እንደመጣና ችግር ካለ እንዲነግረው በማግባባት ይጠይቀዋል።
ባለሱቁም በረጋ መንፈስ “ምንም አልተፈጠረም እየተጨቃጨኩ ያለሁት ከራሴ ጋ ነው ሌላ ሰው የለም።” በማለት ይመልስለታል። በምላሹ ግራ የተጋባው ፖለስ “እንዴት?” በማለት ይጠይቃል። ሰውዬውም እኔ ሁሌ ነው ከራሴ ጋር የምጨቃጨቀው በህይወቴ ውሸታም ሰው አልወድም። በዚያ ነው ከራሴ ጋር የምጨቃጨቀው።” በማለት ከራሱ ጋር የተጣላበትን ምክንያት ያስረዳል።
ፖሊሱ ሰውዬውን ቀርቦ የሚሞግተውን፤ አስገድዶ የሚጨቃጨቀውን የመፍታቱ አቅምም ኃላፊነትም ነበረበት። ነገር ግን ደግሞ ሰውዬው የተጣላው ከራሱ ጋር፣ የሚጨቃጨቀው ከማንነቱ ጋር ነውና መሸምገል ከበደው። ማስታረቅ አልሆንልህ አለው። የራስ ሙግት መፍቻው፣ ከራስ ጋር የሚፈጥሩት መጣረስ መፍትሄው ከውጫዊ አካል አይመጣ ነገር ምን ያድርግ። ብቻ የችግሩን ጥልቀት እያሰበ መፍትሄው ቸግሮት ትቶት ወደ ሌላ ውጫዊ ተቃርኖ ወደተፈጠረበት ማስታረቅ ወደሚቻልበት አቀና። ሰውዬውን በነበረበት ሁኔታ ትቶት፤
ባለሱቁ ከራስ ጋር የመጣላቱ ትልቁ ችግር ራሱ ላይ ያለ ባህሪይ፤ ነገር ግን ሳይወደው ዘወትር የሚደጋግመው ተግባሩ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል። ሁላችንም ዘንድ ያለው ገጠመኝ ከራሳችን ጋር የምንጣረስበት ትልቁ ጉዳይ ከዚህ የተለየ መልክ የለውም። እራሳችን በራሳችን ላይ ሳንፈልግ ወይም ሳንወድ የምንጭነው ሳናምንበት የምንተገብረው አሉታዊ ድርጊት ነው።
ከራሳችን ጋር አለመታረቃችን ማህበራዊ እሴታችንን ይሸረሽራል። ውስጣችን ጥሩ የሆነ ስሜት ሳይሰማው ስለአካባቢያችን ጥሩ መሆን ሊያስጨንቀን አይችልም። ስለግላችን የሚሰማን መጥፎ ስሜት አካባቢያዊ ጉዳዮቻችን ላይ መጥፎ ገፅታ ይፈጥራል። ዛሬ ላይ አብረን በጋራ የምንጋፈጣቸው አስቸጋሪ ሁኔታዎች ሲያሻግሩን የቆዩ እሴቶቻችን መለዘብ የጀመሩትም በዚሁ ሰበብ ነው።
አስቸጋሪ ጉዳዮችን የጋራ ከማድረግ ይልቅ “ምን አገባኝ” መለያችን ሆኗል። በመዲናችን አዲስ አበባ ጎዳናዎች ላይ በሚፈጠሩ አስቸጋሪ ገጠመኞች ይህን በደንብ መገንዘብ ይቻላል። ሰዎች እርስ በርስ ሲጣሉ፤ ከፍ ብሎም ሲደባደቡ እያጨበጨቡ ማጀብ፣ የተዘረፈ “እባካችሁ ተዘረፍኩኝ” የሚሉ የጣር ድምፆች ቁብ አለመስጠት፣ “ተቸገርኩኝ እርዱኝ” በማለት የተዘረጉ እጆች ገላ ምጦ ማለፍ ተላምደናል።
በነገራችን ላይ፤ ሿሿ አዲስ ላይ መልኩን እየቀያየረ ተጠናክሮ ቀጥሏል። የማህበራዊ ትስስራችንን መላላት፣ የእርስ በርስ ትብብራችን ልል መሆኑን የተገነዘቡ ቀማኞች በአደባባይና ህዝብ በሚመላለስብት አውራ ጎዳና ላይ እየታዩ በድፍረት ለመድፈር የሚከብድ ዝርፊያ በጠራራ ፀሀይ ተለምዷል። ሰው አይቶ እንዳላየ በማለፍ የዘራፊዎችን ተግባር መግታት ተስኖታል። ሰሞኑን ካሳለፍኩት የግል ገጠመኜ ልነሳና ተነጥቄ እንደ ነጣቂ፤ ተሰርቄ እንደ ዘራፊ የታየሁበትን አጋጣሚ ላውጋችሁ።
የምሽቱ ብርድ እጅ ቢቆረጣጥም ውስጤ ባለው ሃሳብ ተጠምጄ ብዙም አልበረደኝም። ከራሴ ጋር ሙግት ውስጥ ገብቼ ከፒያሳ በተክለ ሃይማኖት በኩል ወደ ጦር ሀይሎች ላዳ ታክሲ ይዤ እየተጓዝኩ ነው። ከሃሳብ እና ሙግቴ የላዳ ታክሲው ሹፌር አባነነኝ። በሚያቀርባቸው የተለያዩ ሃሳቦች ይበልጥ ተግባባንና በጓደኝነት ስሜት ማውራት ጀምረናል። የተክለ ሃይማኖትን አደባባይ ተሻግረን ትንሽ እንደተጓዝን ስልኬ እሪሪ ስትል ምላሽ ሰጠኋት።
ከደወለልኝ ወራትን ካስቆጠረው አንድ ወዳጄ ጋር የሞቀ ወሬ ይዘናል። በመኪናው ውስጥ ያለው የታፈነ አየር መልኩን ቢቀይር ብዬ የመስኮቱን መስታወት ዝቅ አድርጌ ወሬዬን ቀጠልኩ። የትራፊክ መጨናነቅ ድንገት ጉዟችንን ገታ አደረገው። ከስራ መውጫ ሰዓት ጀምሮ እስከሁለት ሰዓት ድረስ የአዲስ አበባ ጎዳናዎች መገለጫ ሆኗል፤ የትራፊክ መጨናነቁ በጊዜ መግባትን የሚያስናፍቀው የየዕለት ገጠመኛችን ሆኖ አርፎታል።
የላዳውን መቆም ሳላስተውል ወሬን ቀጥያለሁ፤ ከናፈቀኝ ወዳጄ ጋር፤ በዚህ ሰዓት በአካባቢው ላይ ያነዣበቡ ጭልፊቶች የሚሞጨልፉት ነገር ላይ አይናቸው ሲንቀዋለል እኔ ጆሮ ላይ ባለው ስልክ ላይ አይናቸው አርፎ ነበርና ከበቡን ። በሹፌሩ በኩል ያለው በር በሀይለኛው ሲደበደብ (የሹፌሩ ትኩረት ለማስቀየር መሆኑ ነው) ሰምሮላቸው አይንና ትኩረታችን ወደተደበደበው ሆነ።
ከመቅፅበት በኔ በኩል ተዘጋጅቶ የነበረው ቀማኛ ወዳጄን እያናገርኩበት ከነበረው ጆሮዬ ላይ ስልኬን ሞጭልፎኝ በሩጫ ወደ ውስጥ የሚያስገባው መንገድ ካጃቢዎቹ ጋር መሮጥ ጀመረ። ከታክሲው ወርጄ እልህና ድንጋጤ በቀላቀለው ስሜት “አለቅህም ዛሬ ቁም ብዬሀለሁ” እያልኩ በገባበት ሁሉ እየተከተልኩ ሲታጠፍ እያሳደድኩ የስልኬን ቀማኛ ከኋላ በቻልኩት አቅሜ መከተል ጀመርኩ።
መንደሩ ጨላልሞ ስለነበር እንደ ቀኑ ሰዎች አይርመሰመሱበትም። ቢሆንም ግን፤ አልፎ አልፎ የሌባውንና የተነጣቂውን መሯሯጥ ቆመው የሚታዘቡ ምን ገዶኝ ባዮች በመንገዱ ላይ ነበሩ። የመንገደኛውን ግዴለሽ መሆን በዚያ ሩጫዬ ውስጥ ሆኜ እንኳን ስታዘበው ሳዝንም ነበር። እዚህ ደርሰናል ማለት ነው። “ወይ ሀገሬ” አስባለኝ። የሌባን ሩጫ ቆሞ ልክ እንደ ውድድር የሚከታተል “እኔ ካልተነካሁ ማንም ይነጠቅ፤ ይቀማ” ባዩ በርክቶ ሳይ መድረሻችን አሰጋኝ።
ከዋናው አስፓልት ወደ ውስጥ በሚያስገባው መንገድ ኋላና ፊት ሆነን እየተሯሯጥን ነጣቂውን ከተነጣቂ አዳኝና ታዳኝ አድርጎ እንደ ትርዒት በሚመለከት ማህበረሰብ በር ላይ እንሯሯጥ ጀመር። ምን ዋጋ አለው ደርሼ ስይዘው ከኋላ ግብረ አበሮቹ ደርሰው የድንጋይ ናዳ ያወርዱብኝ ጀመር። ያኔ ሞባይሌን ሳይሆን ራሴን ማዳን እንዳለብኝ ተሰማኝና እኔ ከፊት እራሴን ለማዳን እነሱ ደግሞ እንዴት ብትንቀን ነው የምትከተለን በሚል መረን የለቀቀ ሽፍታነት ከኋላ ሆነው ያሯሩጡኝ ጀመር።
ሮጬ እራሴን አዳንኩ፤ አንድ ሁለት ድንጋይ ቀምሼ የሞት ሞቴን ወደ አስፓልት ወጣሁ። ስለኔ እዚያ ቦታ ላይ እንደዚያ መሆን ቁብ የሰጠው አልነበረም። በተደጋጋሚ የማልፍበትና የማውቀው ሰፈር የተለየ ስሜት ፈጠረብኝ። በቃ የማላውቀው ማህበረሰብ፣ ለሰው ግድ የሌለው ሰፈርተኛ፣ በላቡ የማያድር ቀማኛ የበረከተበት ልዩ መንደር፤
ለዚህ ሁሉ ምክንያት እርስ በርሳችን መደጋገፉ ርቆናል፤ አብሮ መቆሙን ትተናል። ምክንያቱም እያንዳንዳችን ዘንድ ትልቅ ጉድለት ስላለ፤ ከራሳችን ጋር የተጋጨን፣ ከራሳችን ጋር ያልተግባባን ስለሆነ፣ ከራሱ ጋር እርቅ ፈጥሮ መስከን ላይ የደረሰ ማህበረሰብ በውጫዊ ማንነቱ ላይ በጎነት ይላበሳል። ቀድመን ከራሳችን ጋር ታርቀን አካባቢና ማህበረሰባችንን እናርቅ አበቃሁ። ቸር ይግጠመን።
አዲስ ዘመን መስከረም 16/2012
ተገኝ ብሩ