በአሁኑ ሰዓት ከመፋቂያ ባልተናነሰ ሁኔታ ከከንፈራችን ላይ ከማይጠፉትና በምላሳችን ከምናሯሩጣቸው ውድና በቅርዬ ቃላት ወይም ፅንሰ ሀሳቦች መካከል “ሎጂክ” እና “ሎጂካል” ቀዳሚዎቹ ሳይሆኑ አይቀሩም። እጅግ ቀላልና በሁሉም ዘንድ በሚገባ የታወቁ፤ ታውቀውም ጥቅም ላይ የዋሉ እስኪመስል ድርስ ከሰዎች (በተለይ ከእኛ ከከተሜዎች) ከንፈር ሲወርዱ አይታዩም። “ሎጂካል ሁን/ሁኚ እንጂ”፣ “ሎጂካሊ…” ወዘተ ሁላችንም በየደቂቃው የምንዘርፋቸው ቅኔዎች ናቸው።
የምክንያት አሰጣጥ ጥናት የሆነው ሥነ- አምክንዩ (ሎጂክ) በሁሉም ዘርፍ አስፈላጊ ይሁን እንጂ በፍልስፍና፣ በሒሳብ እና በኮምፒዩውተር ሳይንስ የዕውቀት ዘርፎች ተዝወታሪ፤ እጅግ አስፈላጊ የእውቀት ዘርፍ ነው ይሉናል ባለሙያዎቹ። እንዲሁም ተወዳጅ።
በፍልስፍናው ዘርፍ የኢፒስቲሞሎጂ ጥናት ክፍል ስር የሚገኘው አምክንዮ/ሎጂክ በርካታ ፈላስፎች በፍቅር የወደቁለት እውቀት እንደ መሆኑ መጠን በርካታ ብያኔዎችንም አግኝቷል። “የምክንያት አሰጣጥ ጥበብና ሳይንስ” ነው ከሚለው በዘርፉ አባትነት ከሚታወቀው አሪስጣጣሊስ ቀጥሎ በ12ኛው ክፍለ ዘመን ብቅ ካለው ሪቻርድ ዋትሊ እና ተከታዮቹም አንስቶ እስከ “እውነትንና ውሸትን ለይተን ለማወቅ የሚያስችል መሳሪያ” ነው እሚለው ፈላስፋው አቮሮዝ ድረስ ስለ አምክንዮ ብዙ ተብሏል።
አሪስጣጣሊስ የሥነ አምክዮ ክፍሎችን “መፍታት/ Analysis” እና “ቋጠሮ/Synthesis” በማለት ለሁለት ከፍሎ የሚያቀርብልን ሲሆን፤ የሲሎጅስቲክ አምክንዩ፣ የፕሮፖዚሽናል አምክንዮ፣ ፕሪዲኬት አምክንዮ፣ ሞዳል አምክንዮ፣ የለት-ተለት አምክንዮ፣ ሒሳባዊ አምክንዮ፣ ፍልስፍናዊ አምክንዮ፣ እና አምክንዮና መንሰላስል ዋና ዋና የ“ሎጂክ” ርእሰ ጉዳዮች መሆናቸውም በእሱው አማካኝነት ተብራርቷል።
“እውንነት ምንድን ነው?”፣ “እውቀታችንን እንዴት ልናውቅ ቻልን?” “ህይወት ምንድ ነው?” “ከየት መጣን?” ለሚሉና ለመሳሰሉ ጥያቄዎች መልስ ለመስጠት ሌት ተቀን የሚጥረው በሁለት ዋና ዋና ምክንያታዊ አስተሳሰብ ዘርፎች ማለትም ከተቆራረጡ ምሳሌዎች ተነስተን አጠቃላይ ድምዳሜ ላይ የምንደርስበት “ትንቢት አምክንዮ/Inductive reasoning” እና ከትርጉምና ጥርጥር ውስጥ መግባት ከማይችሉ እውነታዎች ተነስቶ ውሱን ምክንያታዊ ድምዳሜ ላይ የሚያስደርሰን “መንስኤ አመክንዮ/ deductive reasoning” በአጠቃላይ የሰው ልጅ፤ በተለይም በዚህ በ21ኛ ክፍለ ዘመን አጋማሽ፣ እጅግ አስፈላጊና ከተጋረጡ ችግሮች መውጫ መንገድ እንደሚሆን ይታመናል።
ካልሆነ በዘመኑ ገጣሚያን ልዩ ትኩረተን ካገኙ፣ በስነፅሁፍ ስራዎች ውስጥ ሁነኛ ስፍራ ከተሰጣቸው “መንጋ”ን የመሳሰሉ ቃላት ተፈላጊነታቸውና አገልግሎታቸው እየጨመረ ከመሄድ አይድንም።
ሰሞኑን በአንድ ትልቅ የፖለቲካ መድረክ ላይ የቀረበውን የህሊና ደሳለኝ ሃያሲ ግጥም ካስማና ማገር ሆነው ካቆሙት ቃላት መካከል አንዱና በተደጋጋሚ ስንሰማው የነበረው “መንጋ” የሚነግረን ቁብ ቢኖር በአገራችን “ሎጂክ”ም ሆነ “ሎጂካል” ተብዬ ነገሮች ከአገራችን እብስ ሊሉ አንድ እሩብ የቀራቸው መሆኑን ነው።
ፍልስፍናው እንደሚያስረዳው በስነ-አመክንዮ/ ሎጂክ “መንጋ”ነት የለም። ያለው የሰብእና፣ የአመለካከት፣ አሰራር፣ አስተሳሰብና ባህርይ ያለመጣረስ፣ ርግጠኝነት፣ ታእማኝነት፣ ሙሉነት ናቸው። እነዚህ ደግሞ ለአንድ ለተሟላ ሰብእናም ሆነ ማህበረሰብ መሰረታዊ የግንባታ መሳሪያዎች ናቸው። ከዶ/ር አቢይ ወደ ማማው መምጣት ወዲህ አንዱ የታየው ለውጥ እነዚህን የሰብእና መሰረቶች መሰረት ያደረገ ማህበረሰብ ለመፍጠር እየተደረገ ያለው ጥረት ሲሆን “ብርቱ ወግ”ም የዚሁ አካልና ምሳሌ ነው።
ይህን የፍልስፍናና የዘርፉን የሥነ አምክንዮ (Logic) ጉዳይ ከኢትዮጵያ አውድ አንፃር መረዳት ካስፈለገ የዘርአ የቆብን “ሀተታ ዘርአ ያቆብ” ማንበብና መደመም ይቻላል። (የዛሬን አያድርገውና እኛ እንዲያ ነበርን አሉ። ዛሬ “ትልቅ ነበርን …” ሆነ እንጂ ነገሩ ሁሉ።)
በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ “አውቃለሁ” ከሚለው መካከል “መንጋ”ነት ከበዛ በስሜቱ የሚመራው ቁጥር በልቡናው ከሚመራው ቁጥሩ የናረ ነው ማለት ነው። “አመክንዮ/ሎጂክ፤ ወይም በአመክንዮ ይመራል/ ሎጂካል” የሚባለውም ሆነ ትርጓሜው ደብዛው ጠፍቷል ማለት ነው።
“ሎጂክ” ወይም “ሎጂካል” ህይወትን በትክክለኛው አቅጣጫ እንድንመራ ሚናው ዘርፈ ብዙ ነው ይላሉ ባለቤቶቹ። “መንጋ”ን ለመከላከል ዋንኛው መፍትሄም እሱ መሆኑን ነው ደጋግመው የሚነግሩን። ተገቢ የሆነውን የክርክር ቅርፅ ተገቢ ካልሆነው የክርክር ቅርፅ የመለየት አቅምና ብቃት ምንጩ “ሎጂክ” ሲሆን፤ “ሎጂካል” ለሆኑ ሰዎች መፍለቅም የላቀውን ድርሻ ይጫወታል ባይ ናቸው።
ግድ የለም እያንዳንዳችን እንዴት እንደምንኖር፤ ለምን እንደ ምንኖር ወዘተ በምክንያት ላይ ተመስርተን እንድንወስን እድል ይሰጠናልና ጠበቅ አድርግን እንያዘው የሚሉት ሁል ጊዜ ነው። መጠቀም ማለት ምን ማለት እንደሆነ፤ መስጠትም ሆነ መቀበል ስልምን ሲባል መሆኑን ሁሉ ለመወሰን “ሎጂክ” ሁነኛ ትጥቅ ነው ባይ ናቸው አለምን ሁሉ ሲመክሩ።
በምክንያት ማመን፣ በምክንያት መስራት፣ በምክንያት መከራከር፤ ባጠቃላይ በምክንያትና ለምክንያት መስራት ሁሉ መነሻው ሎጂክ ነው እያለ ነበር አሉ ሶቅራጥስ በየመንገዱ እንደ እብድ ሲለፈልፍ የነበረው (ማን ሰምቶት የሚሉም አሉ)። “ለምን?” ብሎ ለመጠየቅም ሆነ ለ“ለምን?” ጥያቄ መልስ ለመስጥት “ሎጂክ” የግድ ነው የሚለው የፍልስፍና አስተምህሮት ሲሆን፤ “ለምን?” ብለን ስንጠይቅም “ለምን?”ን የፍልስፍና የበኩር ልጅ ሊሆን የቻለው የ“ምክንያታዊነት”ን ፀጋ፣ አቅምና ብቃት፤ የማሰብ፣ ማሰላሰልና ማብላላትን ጥልቅ ችሎታ ካባ በመደረቡና የጥያቄዎች ሁሉ አውራ በመሆኑ ነው።
“ለምን” ከጥያቄዎች ሁሉ የሚዘወተር፣ ግን ደግሞ ከጥያቄዎች ሁሉ የማይመለስ ወይም የሚድበሰበስ፣ ጠያቄና ተጠያቂን የሚያስተዛዝብ፣ የአድማጭ/ አንባቢብን ልብ የሚሰቅል ሆኖ እስከዛሬ ለመዝለቁ ቁልፉ ምክንያት ይሄው “ሎጂክ” የሚሉት ጣጣ መሆኑና ምክንያታዊነቱ (ምክንያትን ይግድ ማለቱ፣ በእከክልኝ ልከክልህ አለመሸወዱ፣ ነቢብን ከገቢር አጣምሮ መያዙ) ነው። ይህ እውን ይሆን ዘንድ ደግሞ “ሎጂካል” ሰው ሆኖ መገኘትን የግድ ይፈልጋል። ይህ ደግሞ ለብዙዎቻችን ከባድ ነው። በመሆኑም ነው ብዙውን ጊዜ ዳገት ላይ ሰው የሚጠፋው።
“ሎጂክ” ጥልቅ ነው፤ “ሎጂካል”ም ግልብ አይደለም። (ይህ አይነቱን አስተሳሰብ የበለጠ ማወቅ የሚፈልግ ካለ የቴዲ አፍሮን “ሂድ ሂድ . . . ምክንያቱን ለማወቅ . . .” ዜማን እየተዝናና መስማት ይችላል።)
ዘመኑ “መንጋ” በዝቷል፤ ኢምክንያታዊነት ነግሷል እየተባለ የሚነገርበት ዘመነ እንትን ነው። “ሎጂካል” ሰው ማህበራዊነት የገባው፣ ለማህበራዊነት የሚያስብና አብዝቶም የሚጨነቅ፤ ከ”መንጋ”ነት የተነጠለ ማህበራዊ እንስሳ ነው። ሚዛናዊነት፣ አስተዋይነት፣ የማመዛዘን ችሎታ፣ ተንባይነት … ሁሉ የሎጂክ ንጥረ ነገሮች ናቸው። “ሎጂካል” የጊዜ፣ ቦታና ሁኔታን ምንነት፤ ጥምረታቸውን ከነፋይዳቸው ያወቀ ነው።
ይህን ስንል የፍልስፍናውን አባት አሪስጣጣሊስ (384 BC – 322 BC)ን መሆን ወይም ማከል አለብን ማለት አይደለም። ከ“መንጋ”ነት መላቀቅ ይቻል ዘንድ ግን የሱ ደቀ መዝሙር መሆን ባይጠቅምም አይጎዳም።
በአንድ ዘመን እነ “መንጋ”ን የመሳሰሉ ቃላት ላደባባይ የሚበቁበትና በስነፅሁፋዊ ስራዎች የሚያገኙት ትኩረት ከፍ የሚልበት ዋናው ምክንያት የዚሁ የ“ሎጂክ” ድርቅ መንሰራፋትና “ሎጂካል” መሆን ያለመቻል ዝቅጠት ንፁሁን አየር ሲበክሉት ነው። የበሳል ገጣሚያ ስሜት ሲገነፍል መጀመሪያ የሚገሸልጣቸው ወገኖች ቢኖሩ እነዚህኑ “ሎጂካል” መሆን ያልቻሉ “መንጋ”ዎችን፤ ወይም ኢ-ምክንያታዊያንን ሲሆን ለዚህም ዮሀንስ፣ ጎሞራው፣ ፀጋዬና ሌሎች ተጠቃሽ ገሽላጮች ናቸው። “መንጋ” ውጣ፤ “ሎጂክ” ግባ!!!
አዲስ ዘመን መስከረም 12/2012
ግርማ መንግሥቴ