አንዳንድ ወቅት ብቅ እያለ የሚያስጨንቀን፤ ትዕግስታችንን የሚፈትነን ‹‹የጭለማ›› ጎን እንዳለን አምናለሁ። ታዲያ በአስተሳሰብ ልእልና ሰልጠን ያሉቱ ጥቁር ክፍላችን አሊያም ‹‹dark side›› እያሉ የሚጠሩት ደርሶ ድብታና ድብርት ውስጥ የሚዶለን፤ አለፍ ሲልም ትዕግስት እያሳጣ የማይሆን ውሳኔ ላይ የሚጥለንን ነው። በተለይ ችኩልና ለውሳኔ የፈጠንን በውጤት ያልታጀብን ያደርገናል።
በአንድ ነገር አምናለሁ። ግራ በገባው ዓለም ላይ አብዛኞቻችን የጎደለን ‹‹ትዕግስት›› ነው። ይሄ እኔ የማምንበት ሀቅ ነው። ትእግስት በቀጥታ ከእምነታችን ጋር እንደሚያያዝም አውቃለሁ። ይህ ጉዳይ አንድ ነገር ያስታውሰኛል። አሁን በህይወት የሌለው አያቴን። ምድር ላይ ያሉ እንቅፋቶችንና መሰናክሎችን በሙሉ አይኔ ማየት እንዲችል አይኔን የገለጠልኝ መሪዬ።
የህይወት መመሪያ ቁልፉን ያቀበለኝ ይህ ታላቅ ሰው በአንድ የተባረከ ቀን የእምነት እና የትግስት ሃያል ቁርኝትን ሊያሳየኝ ቻለ። እምነት ‹‹የማይታየውን ማየት መቻል ሲሆን›› ትእግስት ደግሞ ‹‹በልቦና ያዩትን እውነት እስኪገለጥ የመጠበቅ ሃይል›› እንደሆነ ገለጠልኝ።
የበጋው ወር ሲገባደድ ሰማይ የመሬት ንቃቃትን ለመድፈን ‹‹በህይወት ውሀ›› ምድርን ሲያረሰርስ፤ በእናቴ ግፊት ሁሌም አያቴን ለመጠየቅ ወደ ገጠሩ ክፍል የመሄድ ልምድ አለኝ። ከመኪና ጥሩንባ ጩኸት፤ ከአርማታ ጫካ ተላቅቄ ትክክለኛው የህይወት ኡደት ከሚከወንባት ውብ የተፈጥሮ ክፍል ጋር የምገናኘው ያን ጊዜ ነበር። ይህ ስሜት ውስጤ እንደቀረ የማስታውሰው አሁን ላይ መለስ ብዬ ለማስተዋል ስሞክር ትዝታው ሲጎሻሽመኝ ነው።
ታዲያ ማስተዋል በጎደለው የልጅነት ጊዜዬ ላይ ለአያቴ ቀለል ያሉ ለእኔ ግን ፈታኝ የሆኑ ጥያቄዎችን አከታትልበት ነበር። በአንዱ የክረምት ወቅት እንዲህ ሆነ። አያቴ በጠዋቱ ከመኝታዬ አስነስቶ እርስቱ ወደሆነው ወደ አንድ ሰፊ ሜዳማ ስፍራ ይዞኝ ሄደ። ብቻችንን አልነበርንም። ነገ ዋርካ የሚሆኑ፤ ዛሬ ግን ፍሬ የሚሆኑ በርካታ የዘር ፍሬዎችን ይዞ ነበር።
ሁሌም ይህን የማድረግ ልምድ ቢኖረኝ ከእኔ ጋር ግን በዚህ መልክ ፍሬን ከአፈር አዋህደን አናውቅም ነበር። እንዲያው ዘርን ለመበተን ብቻም ወደ ስፍራው እንዳልወሰደኝ ቆየት ብሎ ነበር የገባኝ። በእኔ ለጋና በእርሱ የሰከነ እእምሮ ውስጥ በርካታ ጉዳዮች እየተብሰለሰሉ ፍሬውን ከአፈሩ ጋር አቀላቀልን።
በጊዜው ከአያቴ ጋር የነበረኝ ቆይታ አስደሳች ነበር። የዘር ፍሬን ከመሬት ማዋሃድ የሚሰጠው ደስታ ልዩ ነበር። እውነት ለመናገር ደግሞ ከሁሉም በላይ ያጓጓኝ የተከልናቸው ፍሬዎች ከምድር ከርስ ውስጥ እየተፈለቀቁ ሲወጡ ማየት ነበር። ተከላውን ጨርሰን ወደ ቤታችን ተመለስን። እኔ ተመለስኩ ከምል ግን በድኔ ተመለሰ ብል ይቀለኛል። ምክንያቱም ሀሳቤ የነበረው የተከልናቸው ፍሬዎች ላይ ነበር። እንዴት እና መቼ ይበቅሉ ይሆን? ያስጨነቀኝ ጥያቄ ነበር።
ከሁለት ሰዓት ቆይታ በኋላ አያቴን ትቼ የተከልናቸው ፍሬዎች ወደሚገኙበት ስፍራ አቀናሁ። ከሜዳው ለመድረስ ልቤ እስኪፈርስ መሮጤን አስታውሳለሁ። በቦታው ስደርስ ግን ከእኔና አያቴ የእግር ጫማ ምልክት፤ ተቆፍረው አፈር ከለበሱ ጉድጓዶች ውጪ ምንም መመልከት አልቻልኩም። ልፋታችን መና የቀረ መሰለኝ። ምንም አረንጓዴ ነገር አልታይህ አለኝ። ተስፋ ቆረጥኩ። ‹‹በቃ የተከልናቸው ፍሬዎቹ አልበቀሉም›› ብዬ ተከዝኩ። ከአንዱ ጉድጓድ ውስጥ አፈር የለበሰውን ፍሬ አውጥቼ ከፀሐይ ትይዩ ካደረኩት በኋላ አንጋጥጬ አየሁት ምንም የበቀለ ነገር አይታየኝም። መልሼ ወደ ጉድጓዱ ተክዬው ወደ ቤት ተመለስኩ።
አያቴ ፊቱን ወደ መግቢያው በር አዙሮ፤ ጀርባውን ለጠዋት ፀሐይ ሰጥቶ፤ ኩታውን ደርቦ ከበረንዳው ላይ መፅሐፉን ይደግማል። ልጅ ሆኜ ‹‹ኢትዮጵያ›› እሱን ትመስለኝ ነበር። እውነትም ተፈጥሮን የተረዳ፣ ወግ ባህሉን የጠበቀ ኩሩ ኢትዮጵያዊ ነበር። እንባ ያቀረሩ አይኖቼን ከፊቱ አቅርቤ ‹‹አባባ የተከልናቸው ዛፎች አልበቀሉም። ደርቀዋል›› አልኩት። ቀና ብሎ ሲያየኝ እንባዬን ዘረገፍኩት። አባባ የልጅነት ጭንቀቴን እና ጉጉቴን በተረዳ አንደበት ፈገግ እያለ፤ እንባዬን ከጉንጬ ላይ በመዳፉ እየጠረገ ‹‹ ልጄ አትቸኩል። ሂደቱን ለተፈጥሮ ተውላት። ችግኞቹ ይበቅላሉ። ከኛ የሚጠበቀውን አድርገናል። አሁን ተራው የተፈጥሮ ነው›› በማለት ጊዜው ገና መሆኑን ነገረኝ። ‹‹በጥረትህ እምነት ይኑርህ የተከልከው ፍሬ እንደሚበቅል እመን›› ሲልም በውብ አንደበቶቹ አስረዳኝ።
ከሳምንት በኋላ አያቴ እንደተለመደው በጠዋት ቀስቅሶ ችግኞቹን ወደተከልንበት ስፍራ ይዞኝ ሄደ። በልጅነት አዕምሮዬ በጊዜው የተመለከትኩት ነገር አስደሳች ነበር። ችግኞቹ አናታቸውን ከቀበረው አፈር ፈልቅቀው አውጥተው ስፍራውን በአረንጓዴ ቀለም ሞልተውታል። ደስ የሚል ትእይንት ነበር። አያቴ ቀጠለ ‹‹አየህ ልጄ ፍሬው ቅጠል ለመሆን የሳምንት ጊዜ ፈጅቶበታል። በህይወት ውስጥ እንዲሁ ጊዜ የሚፈልጉ በርካታ ጉዳዮች አሉ። ያንተ ድርሻ ሂደቱን ማመን እና የድርሻህን መወጣት ነው። ከዚያ ውጤቱ እስኪመጣ በትእግስት መጠበቅ›› በማለት የህይወት ክህሎትን አስተማረኝ። በአያቴ አጭር ቋንቋ ሂደቱን ማመን ‹‹ትእግስት›› ማለት ነው። የዘራነውን እንደምናጭድ በልቦናችን ማወቅ ደግሞ ‹‹እምነት›› ነው።
ለካ አያቴ ሁሌም ያለቦታው ፈጠን ፈጠን ሲሉበት የማይወደው እና ‹‹የጅብ ችኩል ቀንድ ይነክሳል›› እያለ የሚተርተው ወዶ አይደለም። ይሄ የገባኝ ከላይ ያጫወትኳችሁ የችግኙ ጉዳይ ዓመት ከሞላው በኋላ ነበር። ከወዲያኛው ማዶ ስልክ አቃጨለ። አያቴ ነበር ለእናቴ የደወለው። ጥቂት ተጨዋውተው መነጋገሪያውን ለኔ አቀበለችኝ። በስልኩ ውስጥ እንዲህ የሚል ድምፅ ሰማሁ ‹‹ልጄ የተከልናቸው ችግኞች አድገው ትልልቆች ሆነዋል። ስታያቸው እንደምትደሰት እርግጠኛ ነኝ››። አያቴ ይህን ሲለኝ ከዓመት በፊት ከጉድጓድ አውጥቼ አንጋጥጬ መብቀል አለመብቀሏን የተመለከትኳትን ፍሬ አስታውሼ ለራሴ ፈገግ አልኩ።
ዛሬስ? ጊዜው አልፎ ዓመታት ቢነጉድም የእኔም ሆነ የማህበረሰባችን መሰረታዊ ችግር የትዕግስት እና የእምነት ማጣት ነው። የተፈጥሮን ኡደት አለመከተል። በመቸኮላችን ከስጋው ይልቅ ቀንድ መንከስ። ማወቅ ያቃተን አንድ ጉዳይ አለ። የምንተክለው መጥፎም ሆነ ጥሩ ፍሬ ጊዜውን ጠብቆ መብቀሉ እንደማይቀር ማመን አልቻልንም። ሂደቱን አልጠበቅንም!
መልካም ፍሬዎች በአንድ ጊዜ አይበቅሉም። የክፋት ፍሬዎችም እንዲሁ። ስኬታማ ሰዎች አይን ባወጣ ሌብነት ካልሆነ በቀር በአንድ ሌሊት ሀብት አያከማቹም። እውቅናም ሆነ እውቀት በአንድ ምሽት አይገኙም። የእኔና የአብዛኛዎቻችን ችግር ይህ ነው። ስኬትም ሆነ ውድቀት በአንድ ቀን ጥረት የሚመጡ ይመስለናል። መች ይሄ ብቻ ሆነ። ዛሬ የስኬት ፍሬ ዘርተን ነገ በቅሎ ማየት እንሻለን። የተፈጥሮን ኡደት መጠበቅ አቅቶን የዘራነውን እየነቀልን በትግስት ማጣት ወጥመድ ውስጥ እንወድቃለን። ጎጠኞች የዘሩት የክፋት መንገድ በአንድ ምሽት እንደ አረም ተነቅሎ ካልተጣለ ብለን በድብርት ማቅ ውስጥ እንወድቃለን። እምነት እናጣለን። ለዘመናት የበቀለው መልካም የአንድነት ፍሬ በዓመታት የአረም ዳዋ የሚለብስና የሚነቀል ይመስለናል። ፍርሃት ውስጥ እንዘፈቃለን። ማስተዋል አቅቶን ለአያቶቻችን ጆሮ ነፍገን።
ሀሳቤን ይህን ጠይቄ ልደምድም። ‹‹ትእግስታችን እስከምን ድረስ ነው?›› በተለይ ደግሞ የማህበራዊ ድረ ገፅ ልክፍት ላይ የወደቅነው ወጣቶች። ዛሬ አስበን ውጤቱ ለነገ የምንጠብቅ። ቀንድ ነካሾች። በአንድ ሌሊት አገር የሚገነባ፤ በንጋታው አገር የሚፈርስ የሚመስለን። በአንድ ወቅት ግርግር በማንነታችን፣ በቤተሰባችን፣ በጓደኛችን፣ በአገራችን፣ በስራችን፣ በጥረታችን እምነት ያጣን። ‹‹የጅብ ችኩሎች፤ ቀንድ ነካሾች›› በተፈጥሮ ሂደት ‹‹ለምን እምነት፤ ለምን ትግስት አጣን?››!! ሰላም
አዲስ ዘመን መስከረም 11/2012
ዳግም ከበደ