ሀገር ምድሩን የሚያተራምሰው ማሕበራዊ ሚዲያ የሚዳኘው ሕግ የለውም። አንዱ አካሉ የሆነው ፌስ ቡክ ደግሞ የተነገሩም ያልተነገሩ ወሬዎች ማምረቻ ሆኖ ሲያምሰን ሲያወራጭን ሲያተራምሰን ይውላል፤ ያድራልም። የወሬ ጥሩንባ ማለት ነው አሉ አቶ ዘነበ። ልጆች ፌስ ቡክ የሚሉት ላይ ተጥደው ይውላሉ። ትምህርት ማጥናት እንደ ድሮ ተማሪ ለእውቀት ብሎ ማንበብ የለም። ተው ቢባሉም አይሰሙም። ምን አይነት የእብደት ዘመን ላይ ደረስን ሲሉ በዓመት በዓሉ ድግስ ጥሪ በቤታቸው የተሰበሰበው ጎረቤት ሁሉ አሁን ገና ቁስላችንን ነኩት አቶ ዘነበ አሉ።
አባወራዎች እማወራዎች የጎረቤት ልጆችም ተገኝተዋል። የዘንድሮ ልጅ ደፋር ነው ይላሉ አዛውንቶች። አንዱ ልጅ ሀሳባቸውን አድምጦ ሲያበቃ አባባ ዘነበ ፌስ ቡክ እኮ የሰለጠነው ዘመን መገናኛ ሀሳብ መለዋወጫ ነው አላቸው። ቀበል አደረጉና አቶ ዘነበ አይ ልጄ የሰይጣን ዘመን ሰው ከሰው የሚያባላ፤ አብሮነትን የሚያፈርስ፤ የሌለ ነገር ፈጥሮ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያናጭ መሆኑን ትላልቆቹ ሰዎች ነገረውኛል።
እና አንተ ከዚህ፤ እሱ እሱዋ ከዛ፤ ሳንባባል በፍቅር ተዋደን ተጋብተን ተዋልደን ብዙ ደግና ክፉ አሳልፈን የኖርን ነን። አሁን የባሰ ነገር የመጣው የእናንተ ሰይጣን ፌስ ቡክ ከመጣ በኋላ ነው አሉ አባባ ዘነበ። ወጣቶቹ ሳቃቸውን ጎላ አድርገው ሳቁ።
ትላልቆቹ ሰብሰብ ብለን በሰርጉም በለቅሶ ቤቱም ስንጫወት ይሄ ሁሉ ሀገር የሚያምሰው የቆጥ የባጡ የወሬ መአት ከየት ነው የሚመጣው ስንባባል ከፌስ ቡክ ነው ይሉናል። ስለማናውቀው ፌስ ቡክ ሰው መስሎንም ነበር። ምኑ ቀዳዳ ተርታራ፤ ጡሩንባ፤ ፊሽካ የሆነ ሰው ነው እያልን።
ኋላ ላይ ብዙ ሰዎች ፌስ ቡክ ሰው እንዳልሆነ ነገሩን። ይሄው ወጣቱ በያዘው ስልክ ሁሉ እንደሚገኝ ነገሩን አወቅን። የሽብርና ከፋፋይ ወሬው የሚመ ጣው በገንዘብ ተከፍሎ ነው። ወዲያው ወዲያው ብር ካላገኘ አይሰራም ወሬ አይሰጥም ብለው ነገሩን ሲሉ ለዓመት በዓሉ ድግስ የተሰበሰቡት አባቶች እናቶች ወጣቶች ጭምር ድክም እስኪሉ ሳቁ። አይ አባባ ዘነበ እያሉ።
ሰው እንዴት ለወሬ ለማይረባ ወሬ ይሄን ሁሉ ገንዘብ ያባክናል፤ ምነው ሌላ ቁም ነገር አትሰሩበትም ልጆቼ ገንዘብ መጫወቻ ነው? አሉ እማማ ደብሬ። ልክ ነሽ ወ/ሮ ደብሬ ግን እኮ ልጆቹ መች ይሰማሉ ብለሽ ተለክፈዋል። እሱን ካልያዙ ሌላ ሕይወት ያለ አይመስላቸውም። ጉድ ያለው ዘመን እኮ ነው አሉ አባ ቁና።
አባ ቁና የወንድ መስፈሪያው ቁናው እኔ ነኝ ባይ ነበሩ። ሀገር ያውቃቸዋል። እርጅና ሳይመጣ ከዘራ ሳይያዝ በፊት። ግርግር ያለ እንደሁ ዘራፍ አባ ቁና ብለው ከመሀሉ ጥልቅ ነው እንዳናቀዠቀዠው ሰው። ጠቡን ለሁለት ከፍለው የሚረዱትን ለይተው በወይራ ክትክታ ያበራዩት ነበር። ጉልበታም እምቢ ባይ አመጸኛ እንደነበሩ የሚያውቁአቸው ይናገራሉ። አባ ቁና ያንን የብርታታቸውን ዘመን ሲያስታውሱ የሚሉት ግጥም አለቻቸው ።
ልጁስ ልጅ ነበረ ለሀገር የሚበጅ
እርጅና በአቋራጭ ደረሰበት እንጂ ይላሉ። ለማለት ያህል እንጂ እድሜውንስ ጠግበውታል። ምናባቱንስና።
ወ/ሮ ደብሬ ፌስ ቡክ ነው እያሉ ልጆቻቸው በሚነግሩአቸው ሁሉ አብዝተው ይጨነቃሉ። ምን መአት ሊመጣብን ነው አምላኬ እያሉ። ወ/ሮ ደብሬ፤ አቶ ዘነበ ፤አባ ቁናም ይሄ ነገር ከመጣ ወዲህ ሀገራችን ሰላም አላገኘችም። ፌስ ቡክ የምትሉት ይጥፋ፡፤ ሰላማችንን አብሮነታችንን ፍቅራችንን እንፈልጋለን። ወሬኛ፤ አዋሻኪ፤ ቆርጦ ቀጥል፤ አሸባሪ ስለሆነ እዛው ወደመጣበት ሀገር ወደ አማሪካ ይመለስ አሉ። ምን ይመለሳል መሀላችን ገብቶ ያምሰናል እንጂ መላቀቂያ ነው እኮ ያጣነው። የሕዝብ ሰላም የሚያውክ ዋናው አጋንንት ነው አሉ አባ ቁና።
የዘንድሮው ዓመት በዓል ወሬ የኑሮ ውድነቱና ፌስ ቡክ ነው። የሚገርመው አዛውንቶቹ ራሳቸው ለምደውት እስቲ ደሞ ያ ፌስ ቡካችሁ አባ ቀዳዴ ምን አለ እያሉ ይጠይቃሉ። ቤተሰቡ ጎረቤቱ እያውካካ አዛውንቶቹም ሁሉም ይሄን ጠላ ይቀረድዱታል። እኛና ጠላ ተገናኝተን መትረፊያም የለው አሉ ሰዎቹ። ማለፊያ ጠላ ነው ይድገሙን ይባል የለ። በዛን ዘመን ማሕበራዊ ሚዲያ ፌስ ቡክ ምናምን የሚባል አልነበረም። ለክፉውም ሆነ ለደጉ ነገር እነሱው ነበሩ ማሕበራዊ ሚዲያዎቹ። ያው ምንም አያመልጣቸውም። እነ አባ ዘነበ፣ እነ አባ ቁና፣ እነ ወ/ሮ ደብሬ።
እናቶችም እንዲሁ ናቸው:: በቡና ረከቦታቸው ዙሪያ ለወትሮውም ይሁን ለዓመት በዓሉ ሰብሰብ ብለው የተገኘውን እየቀማመሱ የነበረውን እያስታወሱ አምና አብረው የነበሩትን ለዘንድሮ ለመድረስ ያልታደሉትን ዘመዶች የሰፈር ሰው እያነሱ እያዘኑም ጨዋታቸውን ይቀጥላሉ። በይነ መረቡ (ኔት ወርኩ) ብዙ ነው።
አውደ ዓመት በኢትዮጵያውያን ዘንድ ትልቅ ከበሬታና ውዴታ አለው። የፍቅር የሰላም የአብሮነት የተጠፋፋ ዘመድ አዝማድ መገናኛ፤ በስራም ይሁን በቦታ ርቀት ተራርቆ የኖረ ቤተሰብ የሚጠያየቅበት የሚሰባሰብበት ናፍቆቱን የሚወጣበት ታላቁ የኢትዮጵያውያን መገናኛ ማሕበራዊ መድረክ ነው።
ይሄ ሶሻል ሚዲያ የምትለው ነገር በቴክኖሎጂ ተደግፎ ዓለምን ከማናወጡ የሀገራት አደጋ ከመሆኑ በፊት በኢትዮጵያ ባሕል ውስጥ ነበረ። ከቤተሰብ መንደርና ሰፈር እስከ ሀገር ይዘልቃል። ኔት ወርኩ (በይነ መረቡ) ጥልቅና ሰፊ ነው። በመንግስትም ሆነ በባለስልጣናት ወይንም የትም ቦታ የተተነፈሰች ሳትሰማ አትውልም። አታድርም። እንደ ዛሬው ፌስ ቡክ ሀገር ሊያጠፋ ሕዝብን ከሕዝብ ሊያባላ ያለመ ግን አልነበረም።
ምልአተ ሕዝቡ በሚገናኝበት ቦታ ሁሉ ይነጋገራል። ይከራከራል። ያሸሙራል። መንቆር ይችልበታል። ፌርማቶሪ ይሉት ነበረ ድሮ ፌርማቶሪ (ሰላይ) አለ ከተባለም ወሬው ጸጥ እረጭ ይላል። ትንፍሽ የለም። ኔትወርኩ ይዘጋል። የመሰለውን ድምዳሜ ይሰጣል። በዚያኛው ጎራ ደግሞ ተው ተው ተሳስተሀል፤ ይሄ ልክ አይደለም፤ እንደዚህ አይሆንም፤ የጠላ ቤት ወሬ ነው፤ እውነቱ ይሄ ነው ይላል። ይሄም አይደል ፌስ ቡክ ማለት ?
የሆነ ያልሆነውን መዘብዘብ፤ ትንሹን ማግዘፍ፤ የሌለውን ፈጥሮ ማውራት፤ ስም አጥፊ ሆኖ መሰለፍ፤ አዋኪ፤ አዋሻኪ፤ ነውረኛ፤ ነገረኛ መሆን ማለትም አይደል እንዴ አሉ አቶ ዘነበ። ሆሆይ ብለው ሳቁና ፌስ ቡክ የምትሉት ልጆቼ እያዩ ሲነግሩኝ ካለመአት በቀር የሚያወራው ነገር የለም። ምን ግዜ ላይ ደረስን እላለሁ። መልካም ነገርም አለው። ቤተሰብ ያገናኛል። እንኳን አደረሳችሁ ይላል። ግን መአቱና ክፋቱ ይበዛል። አጠቃቀሙን የሚያበላሹትና የሚያከፉት ሰዎች ይመስሉኛል አሉ አባባ ዘነበ።
እኔ እንደው ሳስበው ይሄ ፌስ ቡክ የምትሉት የእኛኑ ሰዎች የጠጅና የጠላ ቤት ወሬ ነው የሚመስለኝ፤ እንቶ ፈንቶ ትርኪ ምርኪ ወሬ ያበዛል። የቧልተኞች የስራ ፈቶች መንደር ይመስለኛል። ትንሹም ትልቁም ሲበረብር ይውላል ያድራል። ሕይወትና ኑሮ ትግል ነው። ሰው ስራ ፈቶ እንዴት እንዴት ፌስ ቡክ የሚሉት ላይ ተጥዶ ይውላል ? ነውርም አሳፋሪም ነው። ደሞ ለእሱ ሲባል የሚወጣውስ ወጪ ? አሁን አሁን ቀልቡኝ ነው የሚለው። ብሩ ካለቀ ወሬ የለም። እንዲህ አይነት የወሬ ዘመን ወሬ ፍለጋ ብር እየተሞላ ገንዘብ የሚያልቅበት ላይ ነው የደረስነው ይገርማል እኮ አሉ ወ/ሮ ደብሬ ።
ምናለ ገንዘቡን ሌላ ሌላ ቢሰሩበት አስበውታል በወር ምን ያህል ሊሆን እንደሚችል ጉድ እኮ ነው። ሀገር በስራ እንጂ በወሬ አትለማ። በወሬም አትጠፋ። ልጆቻችን ወደቀልባቸው ቢመለሱ ደግ ነው አሉ አባ ቁና። አቶ ዘነበ ለጠቁና ፌስ ቡክን ፈረንጆቹ ከእኛ ሳይወስዱት እንዳልቀረ እገምታለሁ አሉ አዛውንቱ።
የእኛ ሰው ስራ ሲፈታ ወሬ ፈጥሮ ያወራል። ሰማይ ተቀደደ የሚሉ አሉ። ሰማዩን የሚሰፉም አሉ። ኧረ ምን እሱ ብቻ ብለው አባ ቁና መናገር ጀመሩ። ከጥቂት ዓመታት በፊትና ዛሬም የፌስ ቡክ ወረርሽኝ ወጣቱን ለክፎታል። ሱስ ነው። ሱሴ ሱሴ የሚሉትም ዘፈን ሰምቻለሁ። ይሄ ምናምን እንደሚሉት። ተነስተው ተኝተው ፌስቡክ የሚሉትን መበርበር ነው። ሲተኙም ሳይቃዡ አይቀርም።
ፌስ ቡኬ– — ፌስ ቡኬ እያሉ። አጋንንት ነው። ገንዘብ ጨራሽ ዋናው ወናፍ የወሬ አባት ነው አሉና አባ ቁና በረዥሙ ተነፈሱ። ሚስት ባል ልጆች የቤት ሰራተኞች ሁሉ የፌስ ቡክ ልክፍት ውስጥ ወድቀዋል። ቀብራራው አባ ቁና ወላዲተ አምላክን ይሄንን ፌስ ቡክ የምትሉትን አጋንንት ቄስ አስመጥቶ አንድ ሰባት ሁሉም ቢጠመቅ ከየቤቱ እሪ እሪ እሪ እያለ አጋንንቱ ይወጣል።
ፈረንጆቹ አጋንንቱን ፌስ ቡክ አስረው ስልኩ ውስጥ ከተውት ነው ወደ ኢትዮጵያ የላኩት አሉ አባ ቁና። ይሄኔ ቤቱ በሙሉ በሳቅ ተዝረከረከ። ተፍነክንከው ሁሉም እየተወዘወዙ ሀሀሀሀሀሀሀ ብለው የማያባራ ሳቅ ሳቁ። በዚህ አላበቁም እንዴት ነው የምትስቁት? አሉ አባ ቁና እኮ እንዴት ነው በእኔ የሚሳቅ ሲሉ ጠየቁ። በእኔ በአባ ቁና ነው የምትስቁት አንበሳ ሲያረጅ የዝንብ መጫወቻ ይሆናል የሚባለው ተረት እኮ ይሄ ነው አሉ መለሱና። አባ ዘነበ አይ እርስዎ ዘመኑ ተቀይሮአል እኮ አባ ቁና አሏቸው።
ይሄ እኮ የእኛው አጋንንት አይደለም በጸበል አይለቅም የፈረንጆቹ ነው አሉ አባ ዘነበ። ገንዘብ አይበቃው፤ በልቶ አይጠረቃ፤ ብሩን ጨርሶ፤ ሰላም ነስቶ፤ ሰውን እርስ በእርሱ በጥርጣሬ እንዲታይ አድርጎ፤ ሀገር ሊያጠፋ ሕዝብ ሊያባላ ሌት ተቀን የሚተጋው እማ ዋናው አጋንንት ነው አሉ አባ ቁና መለሱና። እናንተ አላወቃችሁትም እኮ ።
ሽብር የሚነዛ፤ ሕዝብ ከሕዝብ ለማናቆር ወሬ የሚረጭ፤ ሀገር ለማፍረስ ሲምስ የሚውል፤ በሬ ወለደ የሚል ከዚህ በላይ አጋንንት ምን አለ እናንተዬ ዋናው ነው እንጂ። ፈረንጆቹ በጦርነት ገጥመውን አልሆን ሲላቸው ደሞ በወሬ ሊያባሉን ሊፈቱን ይምጡ ሆሆይ በሚል ግርምታቸውን አባ ቁና ገለጹ። ይሄን ፌስ ቡካችሁን እኔ ፈስ ቡክ ብየዋለሁ። ለወሬ የለው ፍሬ ነው። በተለይ ወጣቱ ተጥዶ የሚውልበትና ለማይረባ ነገር ወሬ ፍለጋ ግዜና ገንዘቡን የሚፈጅበት የወሬ ቋት ነው። ብርቱ ካህንና ብርቱ ጸበል በማስረጨት አጋንንቱ ከሀገራችን እንዲወጣ እናድርግ አሉ አባ ቁና ተንገሽግሸው። የፌስ ቡኩን አጋንንት ።
አዲስ ዘመን መስከረም 8 / 2012
ወንድወሰን መኮንን