አበባ አየሁ ወይ፤ ለምለም… አበባ አየሁ ወይ ለምለም….ባልንጀሮቼ፤ ለምለም ግቡ በተራ …” ጠዋት ቀድሜ የሰማሁት የአዲስ ዓመት መዳረሻ ብስራት መንገሪያ የልጃገረዶች ጨዋታ ነው ። እርግጥ የዘመኑን ያህል በለውጤ ላይ ባላምን ደስ ብሎኛል። አዲስ ዓመት እንደኛ የሚደምቅለት ወይም የሚደምቅበት አለ? ግን አይመስለኝም፤ ተፈጥሮ ሁላ አበባ አፍክታ፤ የሰማዩ ደመና ሁሉ ተገፍፎ፤ ብርሃኑ ሲገልጥ አዲስነት በተፈጥሮም ላይ ሲነግስ እኮ ነው ዘመናችንን የምንለውጠው፡፡
ይህ ከተፈጥሮ ጋር በጋራ የምንለውጠው አዲስነት አያስደስትም? በጣም እንጂ! “አዲስን ዘመን በአዲስ መንፈስ መጀመር ጥሩ ነው፤” ሲሉ ደጋግሜ ሰምቻለሁ ። ደስ ሲል! ያ ለውጥም በአዲስነት ላይ መገኘት ትልቅ ነው ። አዲስነት ተሰማኝ! ለዚያውም በማለዳ ስንት መርዶ በሚነገርበት ሀገር ላይ የአዲስ ዓመት ብስራት፤ አዲስ ዘመን ነጋ ዜማ መስማት መታደል አይደል?
አዲስ አበባ የበዓል ሰሞን ሩጫዋ ሰርገኛ ጠርታ ደጅ ላይ ያስቆመች፤ የምታበላው ያለሰናዳች ሙሽራ ያስመስላታል ። የበዓል ሰሞንማ ባልዋን ለመጀመሪያ ጊዜ ያየች ሙሽራ ያህል ጭንቀቷ ይበረታል ። የበዓል ድባቡ ከትርምስ ጋር የተደበላለቀ ሁነት፤ ደስም ጭንቅም ያሰኛል ። አውዳመት የኛን ያህል የሚደምቅለት አለ ግን? በዓሉን ለማክበር የምናሰናዳው ነገር መብዛቱ የምነከውነው ተግባር ማየሉ አንድ ቀን ብቻ አክብረነው የሚያልፍ እኮ አይመስለም ።
እኔ ምለው? ይሄ ሁሉ የበዛ ክብረ ባዓላችን ድምቅምቅ አድርገን እያከበርን ምግብ በየአይነቱ፤ የሚጠጣ በየወንጪቱ፤ አቅርበን እየላፍን…፤ እያሻመድን የኑሮ መወደድ ሳያነቃንቀን፤ የጊዜ መቀየር ሳይለውጠን፤ የቀጠልነው በምን ይሆን? ኑሮ ተወደደ፤ ረከሰ፤ ተሰቀለ፤ ተዘፈዘፈ፤ ዓመት በዓል ዓመት በዓል ነው። ሁላችንም ዘንድ ከየትም ተጠረቃቅሞ ቤት ይሞላል ። በእኩልነት ሁሉም በጋራ ይስቃል፤ በአብሮነት ጨዋታው ይደራል ።
እንደምናከብራቸው በዓላት ብዛት፤ እንደምንደግሰው ድግስ ስፋት አዘውትረን ችግር የምናወራ፤ ድሎት የራቀን አንመስልም እኮ! ውዶቼ፤ ትናንት ቤታችሁን የዋላችሁበትን አስቡት እስኪ? ከኑሮና አኗኗራችን በላቀ፤ ከምግብና አመጋገባችን በተለየ የአውዳመት ድግሳችን የተለየ ነው ። እንዲያው በበረከቱ ቤታችንን እየሞላው እንጂ ተማርረን የምንገልፀው አጥተን ነጣን የበዓል ቀን ላይ በልተን ወዛን ይለወጣል ።
ሰው ግን ከየት ነው ይሄን ብር የሚመጣው፤ አውዳመት እየጠበቀ የሚረጨው? የሆነ ያልታወቀማ ምንጭ አለ ። ግድ የላችሁም ውዶቼ፤ ሰዎች ከገቢያቸው በላይ ሲያወጡ ካላቸው በላይ ሲነጩ መጠርጠር ጥሩ ነው ። በዓመት በዓል ላይ የሚፈልቅ፤ አውዳመት ላይ የሚፍለቀለቅ አንድ ያለታወቀማ ምንጭ አለ መሰለኝ ።
የሰዎች ብር ማግኛ መንገድ የተለያየ፤ የገቢ ምንጫቸው ለየቅል ቢሆንም ሰሞኑን በአንድ አጋጣሚ ከስራ ባልደረባዬ የሰማሁት የበዓል ሰሞን ስብሰባዎች ገጠመኝ ግን ገርሞኛል ። በዓላት በደረሱ ጊዜ የስብሰባዎችን መብዛት ዋነኛ ምክንያት እንዳጤነው አደረገኝ።
እኔ ምለው በዓውዳመት ሰሞን ስብሰባ የሚበዛው ለምን እንደሆነ ጠይቃችሁ ታውቃላችሁ? ጉዳዩ ወዲህ ነው ወገኖች፤ ግርግሩን ተጠቅሞ ኪስ ለመሙላት፤ በዓልን አስታኮ ትርፍ ለመብላት ነው። የበዓልን ግርግርና አውዳመት በመጣ ቁጥር የሚዘጋጁ ስብሰባዎች የዛሬው ትዝብት ማጠንጠኛዬ ሆኗል ። የዓውዳመት ሰሞን፤ በተለይ የመንግስት መስሪያ ቤቶች በስብሰባ ይጨናነቃሉ ። በዓል ሲቃረብ ስልጠና መስጠት፤ ሰበብ ፈጥሮ መሰባሰብ ተለምዷል።
ሰብሳቢውም ተሰብሳቢውም በስብሰባው አላማ ላይ ትኩረት ከማድረግ ይልቅ ከስብሰባው የሚገኘው ብር ወይም አበል ላይ ያተኩራሉ ። በአንድ ጊዜ ሁለት ስብሰባዎች ላይ በመገኘት ከሁለቱም ቱርፋት ለመቋደስ የማይወጡት ዳገት የማይወርዱት ቁልቁለት የለም።
ለወጌ መነሻ የሆነኝ ባልደረባዬ በስራ አጋጣሚ በታደመባቸው ስብሰባዎች የገጠመውን ሲነግረኝ፤ የታዘበውን ሲያወጋኝ የተገረምኩበት ጉዳይ ለዚህ ጽሁፌ መነሻ መሆኑን ነግሬያችሁ የለ ። አግራሞቴ እንዲጋባባችሁ የራሴን ገጠመኝ አክዬ ገጠመኙን ላውጋችሁማ ።
ስበሰባ የሚበዛበት የበዓል ሰሞን ላይ የተከሰተ ነው ጉዳዩ፤ ለበዓል መዋያ ይሆን ዘንድ አበል ተበጅቶ መርሀ ግብር ተነድፎ የሁለት ቀን ስብሰባ አራት ወይም አምስት ቀን ተብሎ የሚከፈልበት ሰሞን፤ አውዳመትን ለመውጣት የሚያስችል ገቢ ማግኛ ይሆን ዘንድ የታሰበ ስብሰባ፤
ከአዲስ አበባ ወጣ ብሎ በሚገኝ መስሪያ ቤቶች በክፍለ ሀገር አበል ለመክፈል ሲያስቡ ስብሰባ አብዝተው የሚያደርጉበት ከተማ ላይ ነው የባልደረባዬ ትዝብት መነሻ ቦታው፤ አንድ ተሰብሳቢ በሁኔታው የባልደረባዬን ትኩረት ይስብና ባልደረባዬ ሰውዬውን መከታተል ይጀምራል። ሰውዬው በተደጋጋሚ ከስብሰባው ወጥቶ ይገባል፤ በመሀል እየጠፋ አመሻሽ ላይ ይመጣል ።
ይሄን የተመለከተው ወዳጄ “የት እየቆየህ ነው ምትመጣው?” ብሎ በገደምዳሜ ይጠይቀዋል ። ያ ወጥቶ ይገባ የነበረው፤ ጠፍቶ አምሽቶ ይከሰት የነበረው ሰው ምላሹ አስገራሚ ነበር ። ሌላ ቦታም ስብሰባ እየተካፈለ መሆኑንና በአንዴ ሁለት ስብሰባ ላይ እየታደመ መሆኑ አበል ሁለቱም ቦታ እንዳያመልጠው ለፊርማ እየተመላለሰ መሆኑን ነገረው ። ጉዳዩ አግራሞትን አጭሮበት ነበርና ከትውስታ ማህደሩ በጫወታችን መሀል አካፈለኝ ።
የሰውዬው ሁሉ አይቅርብኝ ባይነት አያስገርምም? ባልደረባዬ የስብሰባ ገጠመኙ ሌላ ተመሳሳይ ሁለት ስበሰባ ተካፋይ ሰው ጋርም አገናኝቶት አልፏል። ይሄኛው ሰውዬ ግን አትራፊ ሳይሆን አጉዳይም ነበር ። ከአንደኛው ስብሰባ ወደሌላው እየተመላለሰ የትራንስፖርት ወጪ እያወጣ ለቀናት ሁለቱም ቦታ ‘አለው’ ሲል ከርሞ ስብሰባው አበል አልባ መሆኑ ተነግሮት አተርፍ ባይ አጉዳይ አድርጎታል።
ሃላፊዎችስ ቢሆኑ የተቋማቸውን አደራ፤ የህዝብን ተልዕኮ ለመፈፀም ተቀምጠው የዓመት በዓል ኪስ መሙያ፤ የአውዳመት ወጪ መሸፈኛ የሚሆን አበል መፍቀዳቸው ለምን ይሆን? ይህቺ ሀገር ሌላ አሳቢ፤ ሌላ ተቆርቋሪ ያላት ይመስል ክፍተቷን መሙያ ደጅ ደጁን እያየች ከኪስዋ የምናጎድለው ለምንድን ነው? እንደ ዜጋ እንቆርቆር! የራሳችንን ለመሙላት ስንሮጥ ከሀገር ላይ ማጉደላችን ምን የሚሉት በደል ነው?
አዲስ ዘመን ጀምረናል ። እኛ አዲስ ባንሆን እንኳን በተዘጋጀልን አዲስነት ውስጥ የምናልፍ፤ ባናቅድ እንኳን ለአዲሱ ዘመን በታቀደ የምንምቧች፤ ንቁዎች መሆን ግድ ይለናል ። ለሀገር ማሰብ፤ ለወገን መቆርቆር የተጣለብንን አደራ ለመወጣት የምንጥር አዲስ ሰው መሆን ያሻናል ። ተገቢ ያልሆነ አሮጌነትን ከውስጣችን አውጥተን የሚገባንን መልካምነት ወደኛ ማስረጫ አዲስ ጅማሮ፤ አዲስ ሀሳብ፤ አዲስ ዘመን!
ውዶቼ፤ አዲስ ለመሆን ተዘጋጅታችሁ፤ አዳዲስ ውጥን ወጥናችሁ በአዲስ መንፈስ አዲሱን ዓመት ከጀመርን ይሄው ሁለተኛ ቀን ላይ ተገኝተናል ። አዲሱ ዓመት ለማንም አይገባም ለኛ ማድረግ በአዲስነቱ የምንታደስበት ሊሆን ይገባል ። ዘመኑን የኛ ለማድረግ ዘመኑ ላይ የሚመጥን መልካም ነገር ማቅረብ ተገቢ ነው ።
በነገራችን ላይ፤ የዘመኑ ሳይሆን የኛ መቀየር የኛ መለወጥ ነው ለሀገርም ለኛም የሚጠቅመው ። ወቅቱማ ዑደት ነው። ዝነፍ ሳይል የሚለዋወጥ፤ በሁሉም ስብዕናቸው ውስጥ ለውጥ ሳይኖርም የሚሄድ የሚያልፍ ። የኛ ለውጥ ነው ወሳኝ፤ በውስጣችን የምንፈጥረው፤ በልካችን የምንሰፋው አዲስ ልብስ አዲስ የሆነ መልካም ነገርን የሚያለብሰን፤
በታደሰው ዘመን እኛ አሮጌ ሆነን ከተገኘን አዲስነታችን ግን ምኑ ላይ ነው? አዲስ መሆናችን ግን የቱ ጋር ነው? ዘመኑ ሲቀየር የኛን ለውጥ በዘመኑ ካልተለካ፤ ጊዜው ሲለወጥ የኛን ለውጥ ካላሳየ የወቅት መቀያየር የጊዜ መለዋወጥ ምንም እኮ ነው ።
የዘመኑ በጎዎች፤ የወቅቱ
ጀግኖች፤ የጊዜው ሰላማዊ ተጓዦች ሆነን ያረጀውን ሃሳብ ወዲያ ጥለን አዲስ ዘመንን የሚመጥን አዲስነት ተላብሰን እንጀምረው፤ ዛሬ
ላይ የተገኘን የዘመኑ መታደስም ሆነ ማርጀት ምክንያት እኛው ነንና ነገ በሚታየው የታሪክ ማህደር ውስጥ ዘመን አዳሾች ሆነን እንጠቀስ
ዘንድ የዘመኑን ያህል በአዲስ እና ጠቃሚ ለሀገር ገንቢ በሆነ ሀሳብ እራሳችንን እናድስ ። አበቃሁ፤ ቸር ይግጠመን!
አዲስ ዘመን መስከረም 2/2011
ተገኝ ብሩ