ቃል ተከበረ ? ብዬ ጥያቄ ነገር አነሳሁ ። የምን ቃል ብላችሁ ከጠየቃችሁኝም መልስ አለኝ። መቼም ብዙ አይነት ቃል መኖሩ እሙን ነው። ነሸጥ ሲያደርገን የምንገባው፤ ሞቅ ባለ ጨዋታ ሆነን። በተለይ ደግሞ ምሽት ላይ በመዝናናት ወቅት የሚገባ ቃል፤ ጊዜው ሲደርስ ቃላችንን ወደ ተግባር ለመለወጥ የሚከብደን አይነት ማለት ነው። ይህ ብቻ አይደለም። ሌላም ቃል አለ። በቁም ነገር የሚገባ። የእውነት ለመፈፀም የምንጥረው
ዘመኑ የይቅርታም አይደል? በዳይ ተበዳይን ይቅርታ የሚጠይቅበት፤ ያስከፋም የተከፋም… ሁሉንም የኋላ ነገር የሚተውበት። መቼም ካልዘነጋነው በቀር በይቅርታ እንተላለፍ ብለን ባለፈው ዓመት በሀገር ደረጃ ቃል ስንገባባ ነበር። እኔ በበኩሌ አረሳሁትም፤ እናንተም እንደማትዘነጉት አምናለሁ። ምክንያቱም ቃል ነዋ ። ቃል እኮ ከምንም በላይ ይከበራል። በተለይ በቁምነገር ሲገባ።
ለዚህም አይደል እንዴ “የተናገሩት ከሚጠፋ የወለዱት ይጥፋ “ እያልን የምንተርት። ለቃላችን ታማኝ ለተግባራችን ፈጣን እንድንሆን ደግሞ አባት እናቶቻችን፤ አያት ቅድመ አያቶቻችን ሲመክሩን ሲዘክሩን ኖረዋል። በአፋቸው ብቻ ሳይሆን በተግባርም አሳይተውናል። ይሄማ እንዴት ይዘነጋል፤
አሁን ጥያቄው የሚሆነው ከፅኑዎቹ ባለታሪኮች የወረስነው ቃል የማክበር እሴት እንዴት እየፈፀምነው ይሆን የሚለው ነው? ለቃላችን ታማኝ ተገዥ ሆነን ይሆን? ነው ወይስ ቃላችንን እምንበላ ብኩኖች? እስቲ በቀላል ምሳሌ እራሳችንን እንታዘብ። በመግቢያዬ ላይ ለማንሳት እንደሞከርኩት ይቅር ለመባባል የገባነው ቃል ነበር። በደንብ ግልፅ ለማድረግ እንደ ማህበረሰብ ‹‹ያለንን ግንኙነት ከሚያጠለሽ ቂም በቀል ይልቅ ፍቅር እና ይቅርታ ይሻለናል ይሄን እናከብራለን›› ብለን ቃል ገብተን ነበር። ለመሆኑ እንደገባነው ቃል ነገሮቹን ሁሉ በይቅርታ አልፈናቸው ይሆን? መልሱን ቃል ስንገባባ ለነበርን ሁሉ ትቸዋለሁ፤
ብዙ ነገር ማንሳት ባያስፈልግም በዚሁ ባሳለፍነው አንድ ዓመት ብቻ ‹‹እንፈፅመዋለን›› ብለን የገባነውን ቃል የተገበርን እንዳለን የማይካድ ነው። በዛው ልክ ግን ለቃላችን ተገዢ ያልነበርን ደግሞ አንጠፋም። ለገባው ቃል ሁሉ የማይታመን አለ ብሎ አፍን ሞልቶ መደምደም ባይቻልም ሙሉ ለሙሉ ቃሉን የሚፈፅምም በዛው ልክ ማግኘት ከባድ የሚሆንበት አጋጣሚ አለ። መቼም ጥቂትም ቢሆን በቃል መገኘት ምንም ካለመፈፀም ይሻላል።
እውነት ነዋ! በእኔ ምልከታ ቃል ከምንም ይበልጣል፤ በተለያየ መንገድ ስለሰዎች ባህሪ ሲነሳ አጋጥሟችሁ ከሆነ እሷ/እሱ በቃሉ/በቃሏ ነው የሚገኙት ይባላል። አዎ! ቃል ያስከብራል፤ ቃሉን የሚያከብርም ታማኝ፣ በቃሉ የሚገኝ፣ ቃሉን የሚፈጽም፣ … እንለዋለን። ለቃሉ ያልታመነውን ዋሾ፣ ቃላባይ … ማለታችን ደግሞ የተለመደ ነው። እንዲህ ከመባል ይሰውረን፤ እኛም በቃላችን እንገኝ።
የቃል ትንሽም ትልቅም የለውም። ቃል በፖለቲካ፣ በሃይማኖት…አይከፋፈልም። ቃል ቃል ነው። ማይኪያቶ እጋብዛለሁ ያለ ቃሉን መፈጸም አለበት። ቁም ነገሩ የግብዣው ትልቅ ትንሽ መሆን ማይኪያቶ፣ ሻይ፣ ቡና… መባሉ ሳይሆን ግብዣው በግብዣነቱ አሊያም በቃልነቱ መከበሩ ነው። እጋብዛለሁ ያለም ለመጋበዝ ቃል የገባም በቃላቸው ልክ ሊገኙ ይገባል፤
‹‹ቃል ይከበር፤ የገባነው ቃል እንፈፅም›› እያልኩ ስነታረክ አንድ ነገር ከፊቴ ድቅን አለ። ያው ሁሌ የምናነሳው ቀጠሮ የማክበርና ያለማክበር ጉዳይ ነው። ‹‹ቀጠሮም ከምንም በላይ መከበር አለበት። ቀጠሮ ማክበር ትልቅነት ነው›› የሚሉ እንዳሉ ሁሉ ‹‹የሀበሻ ›› ቀጠሮ በሚል ራስን ማሳነሻ የሚያደርጉም አይጠፉም። ኧረ ሞልተናል! በንግግር መሀል ‹‹ የሀበሻ ቀጠሮ አይደል እንዴ ምንም ቢሆን አንድ ሰላሳ ደቂቃ መዘግየቱ አይቀርም›› ይባላል። በዚህ አመለካከታችን የተነሳም ቃላችንን እንበላለን። ዘና ብለን አንድ ሁለት ሰዓት አርፍደን የቀጠሮ ቦታችን እንደርሳለን። ይሄ የሚሳካው እንዲያውም በጣም ፈጣን ቀጠሮ አክባሪ የሆንን እንደሆን ነው። ካልሆነስ? ካላችሁ መልሴ የሚሆነው ሁለትና ሶስት ሰዓት ከቀጠሮ መዘግየትና ማዘግየት እየተለመደ የመጣ ደዌ ነው።
ይሄን ከቀጠሮ ጋር ተያይዞ በቃላችን የማንገኘውን ጉዳይ ሳነሳ አንድ ወቅት የገጠመኝን ጉዳይ አስታወስኩ። በጊዜው ለስራ ጉዳይ የተያዘ ቀጠሮ ላይ ለመድረስ አስራ አምስት ደቂቃ ዘግይቼ ተገኘሁ። በእርግጠኝነት የመጀመሪያ እንደምሆን አስቤ ነበር፤ ነገር ግን አይደለም ጥቂትም ቢሆኑ የቀደሙኝ ሰዎች ነበሩ። ለዘገየሁበት አስራ አምስት ደቂቃ ራሴን ረገምኩ፤ በሰዓቱ መድረስ ስችል ማን በሰዓቱ ሊገኝ ብዬ በራሴ ላይ የአርፋጅነት መመሪያ አውጥቼ መቆየቴ ተገቢ አይደለም እያልኩ ራሴን ደጋግሜ ወቀስኩ። በእኔ ምክንያት የተንገላቱ ስራ የፈቱ እንዳሉ በማሰብ።
በዚያው ካገኘኋት የስራ አጋሬ ጋር ስንጨዋወት እቀጠሮው ቦታ የደረሰችው ከቀጠሮው ሰዓት አስር ደቂቃ ቀድማ መሆኑን ነገረችኝ። እሷ ይሄንን ያደረገችው ምናልባት እንኳን ታክሲ ባይገኝ ወይም ደግሞ የትራፊከ ፍሰቱ ቢያደነቃቅፈኝ ፈጠን ብዬ ልሂድ ብላ ማልዳ በመነሳቷ ነበር። እንዳሰበችው የመንገድ መደነቃፉ ሳይገጥማት በጥሩ ሰዓት ደርሳለች። እኔ እሷን ሃያ አምስት ደቂቃ ርቄያታለሁ። በሰዓቱ ቀጠሮው ቦታ ብደርሰ ያቆምኳት እሷ የቀደመችውን አስር ደቂቃ ብቻ ይሆን ነበር። ስለዚህ በቃሌ እና በሰዓቱ ባለመገኘቴ ጥፋት እንዳጠፋሁ አስቡት። ከእኔ በኋላ ደግሞ ስንት ሰዎች ይመጡ ይሆን? መቼም ጉዞው የሚጀመረው የተሟላ ባለሙያ ሲኖር አይደል? ስለዚህ ሁሉም እስኪሟሉ በትዕግስት እንጠብቃለን። ሰላሳ ደቂቃ፣ አንድ ሰዓት፣ ቀጠለ ተጨማሪ ሰዓት በተቀመጥንበት መኪና ውስጥ ስንጠባበቅ ሰዓቱ ነጎደ።
በሰዓቱ ከተገኙት ባልደረቦቻችን ውስጥ አንዷ ትዕግስቷ አለቀና ‹‹መቼ ነው የምንሄደው›› ጥያቄ ለአስተባባሪዋ አቀረበች። አሁን የተሰማት የመሰለችው አስተባባሪ ‹‹ይቅርታ ትንሽ ደቂቃ ነው ቀሪዎቹ ደርሰዋል›› የሚል መልስ የማይመስል ስላቅ ወረወረች። ከነሱ ማርፈድ የእርሷ መልስ አስገራሚ ነበር። ማሰብ ያለብን ለቀጠሮው አስር ደቂቃ ቀድማ የመጣችውን ሰው ነው። ከቀጠሮው አንድ ሰዓት ተኩል ዘግይተው የመጡትን ሰዎች አሰብኩና አንድ ነገር ወደ ውስጤ መጣ። እነዚህ ሰዎች መቼም ቢሆን የቀጠሮ ሰዓት ማክበር የሚለው አይገባቸውም። እንዲህ አይነት ሰዎችን አንድም በመምከር ሌላው ደግሞ በመቅጣት ማስተማር ይገባ ነበር። እኛ ግን ይሄንን አላደረግንም። ስልጣኑም አቅሙም ሁኔታውም አይፈቅድልንም። ሁላችንም እያጉተመተምን ጉዞው ቀጠለ። አርፋጆችም ምንም የጥፋተኝነት ስሜት ሳይሰማቸው ትክክል የሰሩ መስሏቸው ወይም ተፈላጊ መሆናቸው እየተሰማቸው ፈገግ ብለው በጨዋታ መንገዱ ያዋዙት ቀጠሉ። ዘመኑ የይቅርታ ቢሆንም እንዲህ ያጠፋም ራሱን ትክክል ነህ እያለ ይቅርታውን እንዲህ ያልፈዋል። በፖለቲካውም፣ በመልካም አስተዳደሩም አካባቢ ይሄው ነው። ስህተትና ጥፋት እንደትክክለኛነት ታይቶ ይታለፋል። የስንቱ አንጀት እርር ድብን እንዳለ ቢያውቁት እንዴት ጥሩ ነበር። ግን መሆን ያለበት እኮ አስራ አምስት ደቂቃ ጠብቆ ያልመጡትን በሙሉ ትቶ መሄድ ነበር። ይሄ ቅጣት ለነገ አስተማሪ በመሆኑ ክፋት እንዳላሰብኩ ይቆጠርልኝ። አንዳንዴ ማስተማር መልመድ አለብን ካልሆነስ ካላችሁ ካልሆነማ ተያይዘን የሀበሻ ቀጠሮ ስንል መክረማችን ነው ። ቃላችንን ቅርጥፍ አድርገን እየበላን!
እንዳው ነገርን ነገረ እያነሳው እንጂ ሀሳቤማ ቃል እንዴት ነበር? ተጠበቀ ወይስ ፈረሰ? የሚል መነሻ ያለው ነበር። አዎ! አሁንም ቃል እንዴት ነው የሚለውን ከማንሳት ወደኋላ አልልም። ምክንያቱም አሁን አሮጌው ዓመት ሊጠናቀቅ የቀረው ከአንድ እጅ ጣቶች የሚያንሱ ቀናት ናቸው። እና ቃላችንን ያፈረስን እንደገና እናድስ። ስለዚህ ለአዲሱ ዓመት ቃል ለማስገባት ከወዲሁ መዝገብ መክፈት አለብን። የምንከፍተው መዝገብ ደግሞ ቃላቀባይ የሚያደርገንን ሳይሆን ቃልን በተግባር እንደሚሆን አስባለሁ። እስኪ ስንቶቻችን ነን ሲጋራ፣ ጫት፣ ሺሻ… ለማቆም ቃል የምንገባ፤ ‹‹መጠጥ… እርግፍ አድርጌ ባልተው ከምላሴ ጸጉር ይመዘዝ›› የምንል።
በቀጣዩ ዓመት ቤት ሰርቼ፣ ትዳር መስርቼ፣ ትምህርቴን ቀጥዬ፣ ድሬ ኩዬ፣ ቤቴን በዕቃ አሳምሬ …. ብለን ቃል እንገባለን። ቃል ስንገባ እንደምናደርገው እርግጠኛ መሆን አለብን ለዚህ ሁሉ የሚያስፈልገው ቆራጥነት፣ የአቋም ጥንካሬ፣ ገንዘብ… ሌላም። እናም ይሄንን አስበን ቃል ከገባን ለምን አይሳካም። ቃል ሲባል የግል ብቻ አይደለም። የማህበረሰብ፣ የቤተሰብ፣ የሀገር ብቻ ብዙ አለ። ልክ ችግኝ ስንተክል እንደገባነው ‹‹የተከልኩትን እንከባከባለሁ›› አይነት ጭምር ነው። ይሄም ቃል ነዋ! ቃላችንን በቀጣዩ ዓመት እናየዋለን።
በተለይ ወጣቶች አካባቢ ብዙ የሚገቡ ቃሎች እንደሚኖሩ እጠብቃለሁ። ምክንያቱም ብዙ ጊዜ እንደምንሰማው ኢትዮጵያ የወጣቶች ሀገር ናት። ወጣቶች ደግሞ ታሪክ መስራት ይችላሉ። ጉልበቱ ካለ፣ እውቀቱ ካለ፣ ቅንነቱ ከታከለበት በበጎ ፈቃድ ብቻ የሚሰሩ ሀገርና ታሪክን የሚቀይሩ ስራዎችን ማከናወን ይቻላል። ለዚህ ታዲያ አነሳሽ ተነሳሽ ሳያስፈልግ ለራስ ብቻ ቃል መግባት ይበቃል። ኧረ ግዴታም ጭምር ነው። ከወጣቱ ብዙ እንጠብቃለን በአዲሱ ዓመት። ዓመቱ ሲያልቅም የተገባው ቃል መሬት ነክቶ ተግባር ላይ ሲውል እኛም ያን ጊዜ ብራቮ ለወጣቱ ብለን አድናቆታችንን እንለግሳለን። ያኔ ታዲያ ቃል ተከበረ? ሳይሆን ቃል በተግባር ተገለጠ እንላለን!
አዲስ ዘመን ጳጉሜ 3/2011
አልማዝ አያሌው