መስከረም ሊጠባ ነው፡፡ የእንቁጣጣሹ በአል አስገምግሞ መጥቷል፡፡ “ቡሄን አልፎ ጨለማው ክረምት አብቅቶ እዮሀ አበባዬ የሚባልበት መስከረም ደረሰ እኮ” አሉ አዛውንቱ አቶ አቻምየለህ፡፡ “አዬ ጉድ፤ አዬ ጉድ ታዲያ እንዲህ ኑሮው ጨሶ፤ ነዶ፤ አቀብ አቀብ የሚያስተነፍስ በሆነበት ምኑን ከምን አድርገን ልንቀበለው ነው ጫልቱ” ሲሉ ሚስታቸውን ጠየቁ፡፡
ወይዘሮ ጫልቱ አሽኮመኮሙና “ዓመት በአል እምዬ እንቁጣጣሽ ድሮ ቀረች፤ ዛሬማ ምን ዓመት በአል አለ ? እስቲ አሁን ምን ይደረግ ነው የሚሉት” ሲሉ ረዥም ዘመን አብረው የኖሩትን የልጆቻቸውን አባት አዛውንቱን አቶ አቻምየለህን መልሰው ጠየቁ፡፡ የዛሬን አያድርገውና አቻምየለህ የከባድ መኪና ሾፌር ነበሩ፡፡
ዓመት በአል ሲደርስ እንኳን ለራሳቸው ቤት ለጎረቤቱም ጭምር ዶሮውን፣ በጉንና ከሰሉን ጭነው ከተፍ ይሉ የነበሩ የተወደዱ ሰው ናቸው፡፡ አቻምየለህ የባለቤታቸውን የጫልቱን ንግግር እንደሰሙ በተቀመጡበት ጋቢያቸውን ወደ ትከሻቸው ከፍ ከፍ እያደረጉ “እኔማ ምን እላለሁ የሚገርመኝ ነገር እነዚያ የድሮ ሰዎች ሲያልፉ እንደው ዓመት በአሉን፤ ድግሱን፤ የሰፈርና የመንደር የቤተሰብ ፍቅሩን፤ አብረን እንብላ እንጠጣ እንጨዋወት የሚባለውን ነገር ሁሉ ይዘውት ሄዱ ልበል? ግራገባኝ፡፡
የማየውንና የምሰማውን ለማመን ተቸገርኩ” ብለው በረዥሙ ተነፈሱ፡፡ ቀጠል አድርገው “ጊዜው ተዘባርቆብኛል፤ ተምታቶብኛል እንደው የባሰ አታምጣ ማለት ነው የሚበጀው ጫልቱ” አሉ ጎላ ባለ ድምጽ፡፡ ድሮ ድሮ እንቁጣጣሽ ሲመጣ በዋዜማው በጉ ደጃፍ ላይ ታስሮ እየጮኸ ግቢውን ያሞቃል፡፡
ዶሮውም ያስካካል፡፡ በየመንደሩ በምጣድ ተጥዶ በኮባ ተሸፍኖ የሚጋገረው ዳቦ ጭስ ዓመት በአል መሆኑን ነጋሪ ሳያስፈልግ ያወራል፡፡ በቡድን ለቅርጫ እርድ የተገዙት በሬዎች በየቦታው እምቧ ሲሉ ሰፈር መንደሩ ዓመት በአል ዓመት በአል ይሸታል፡፡ ጠረኑ በሩቅ ያውዳል፤ ይጣራል። ኑሮው ተወደደ እንጂ ባሕሉስ ዛሬም አልቀረ፡፡ የኢትዮጵያዊነት መአዛና ሽቶው ለየት ይላል፡፡
የውስጥ ስሜትን ይኮረኩራል፡፡ በትዝታም ይንጣል፡፡ የቀደሙ ዓመታትን ያለፉ ቤተሰቦችን የነበረውን አብሮነትና ፍቅር እየቆሰቆሰ እንዲያ እንዲያ እያለ በአይን ሕሊና እየተጓዘ ሆድ ያባባል፡፡ አንጀት ያላውሳል፡፡ አረ በእን ባም ያጥባል፡፡ አይ ዓመት በአል! አይ መስከረም! ሁሉን አስረስቶ ነገም እኖራለሁ የሚል የተስፋ ቀስት ያስወነጭፋል፡፡ ይሄ ሁሉ ትዝታ አዛውንቶቹ ዘንድ አለ፡፡ እነሱ ይህን የቤተሰብ ወግ እየተጫወቱ እያሉ ጎረቤታቸው ወይዘሮ ባፈና “ቤቶች እንዴት አረፈዳችሁ” ብለው ሞንደል ሞንደል እያሉ ገቡ ። ወይዘሮ ባፈና ወትሮም ሞንዳላ እመቤት ናቸው።
ብዙ ወልደው የከበዱ፡፡ በመንደሩ በሰፈሩ የተከበሩ እናት፡፡ “ቁጭ ይበሉ ወይዘሮ ባፈና” አሉ ጫልቱ። “ምኑን እቀመጠዋለሁ” አሉ ባፈና፡፡ “ምነው?” አሏቸው ባልና ሚስት:: ባፈና ቀጠሉና “ኑሮው ጨሰ አሳበደን ወዴት እንድረስ ይኸው ዓመት በአል ደግሞ መጣ ይቅር አይባል መቼም ዓመት በአል ይኸው ሲንቀዠቀዥ ደረሰ፡፡
ወይዘሮ ጫልቱ ገበያ አንሄድም ?” አሏቸው፡፡ ጫልቱም “እሱኑ እኮ ነው የምናወራው ከአቶ አቻምየለህ ጋር፡፡ በጡረታ ደመወዝ ምኑ ከምን ይደረጋል እንደው ለደምቡ ማታ ችቦውን አብርቶ፤ ሲነጋ የተጋገረውን ዳቦ ቆርሶ፤ ቆሎ ቆልቶ፤ ቡና አፍልቶ፤ ቄጠማውን ጎዝጉዞ ተመስገን እንኳን ለአዲሱ ዓመት አደረስከን ብሎ ለፈጣሪ ምስጋና አቅርቦ መዋል ይሻላል እንጂ ከጣሪያ በላይ በወጣ የኑሮ ውድነት ዓመት በአል የለም።
በግና ዶሮ መግዛት ድሮ ቀረ ባፈና አይሞከርም” አሉ ጫልቱ ከመቀመጫቸው እየተንጠራሩ፡፡ “እኔ የምለው አሉ ወይዘሮ ባፈና ሀገራችን የምናውቃት፤ የተወለድንባት፤ ያደግንባት፤ የወለድንባት ክፉና ደጉን አልፈን እዚህ የደረስንባት ያቺው የድሮዋ ኢትዮጵያ ነች ወይንስ ተቀይራ ሌላ ሀገር ሆነች ? እኔ እኮ ግራ ገባኝ” ሲሉ ባፈና ብስጭት፣ ብሶትና ምሬት የቀላቀለውን ሀሳባቸውን በረዥሙ ተነፈሱ። አቶ አቻምየለህ ቀጠሉና “ምነው ጃል ዓመት በአል ድሮ ቀረ አሉ ? ነጋዴውም እንደዛሬው ሰው ቆርጥሜ ልብላ አላለም፡፡ ምን ያድርግ ተጫወተብን እንጂ፡፡
የድሮው ዘመን ኑሮ ቢመኙትስ ከወዴት ይመጣል። ይብላኝ አሁን ለተወለዱት” አሉ፡፡ “ድሮ ሁሉ ነገር ርካሽ ነበር፡፡ ዶሮ 25 ሳንቲም፤ በግ 6 ብር፤ ቤት ኪራይ 2 ብር፤ እንቁላል በስሙኒ አስር፤ በሬ 50 ብር፤ 50 ኪሎ ጤፍ 7 ብር” እያሉ ሲደረድሩት የያኔው ትዝ ብሎአቸው ወይዘሮ ባፈናና ወይዘሮ ጫልቱ “አረ ምነው ምነው እሱን አያንሱት ተው ተው አቶ አቻምየለህ” አሏቸው፡፡ “ያኔም እናማርር ነበር። የባሰ መጣ፡፡ የባሰ አታምጣ ይሻላል” አሉ ሁለቱም ድሮን ዘንድሮ በላው በሚል ትዝብት፡፡
“ዛሬ ግዜው አብዶአል፡፡ ሰው አብዶአል፡፡ ጨርቁን ጥሎአል። ኑሮው ወሬው ሁካታው አሳብዶታል፡፡ እናንተስ የት ናችሁ” ሲሉ አዛውንቱ ጠየቁ፡፡ ዝምታ ሰፈነ፡፡ ሩቅ ዘመንን ከዛሬው ጋር ማወዳደር ውስጥ የገቡ ይመስላሉ፡፡ ባፈና ዝምታውን ሰብረው መናገር ጀመሩ፡፡ “ጽድቁ ቀርቶ በቅጡ በኮነነኝ ነው የሚባለው አይደል፡፡ የሆነው ይሄ ነው፡፡ አሁን አሁን በቀደም ከወራት በፊት አንድ ኪሎ ሽንኩርት 15 ብር ነበር፡፡ ዛሬ 30 ብር ገባ፡፡ አንድ ኪሎ ጤፍ እንደ አይነቱ ከ20 እስከ 24 ብር ድረስ ነበር፡፡ ዛሬ 35 ብር ገባ፡፡ ሽሮ አንድ ኪሎ 15 ብር ነበር ዛሬ 27 ብር ገባ፡፡ አምስት ሊትር ዘይት 400 ብር ገባ፡፡
አንድ ዶሮ ድሮ ከ15 ብር እስከ 25 ድረስ ይገዛ ነበር ዛሬ 350 ብር 400 ብር ገባ፡፡ በግ ድሮ 70 እና 80 ብር ይገዛ ነበር ዛሬ ከ2000 ብር በላይ ሄዶ ጥሪው እንደበጉ አይነት 10 ሺህ ብር ደረሰ። ነጋዴው እየተማከረ ስልክ እየተደዋወለ ሕዝቡ ምን ያመጣል እያለ ተጫወተብን፡፡ ይሄ ሁሉ ከውጭ ሀገር በዶላር የሚመጣ ሸቀጥ ሳይሆን ሞልቶ በተረፈ ሁኔታ በአገራችን መሬት የሚበቅል የሚመረት ምርት ነው፡፡
ነጋዴው ስርአት አጣ፤ ወገኑ አንመስለውም። ዘርፌ ልክበር እኔ ብቻ በልቼ ልሙት አለ፡፡ ሕግና ስርአት የሚያስይዘው ጠፋ፡፡ ንግድ ሚኒስቴር ሸማቾች ምንጥርሴ የሚሉት ሁሉ ከነጋዴው ጋር የተመሳጠረ ይመስላል፡፡ እና ሕዝቡ ምን ይሁን? እውነት ይህች አገር እኛ የምናውቃት ኢትዮጵያ ነች? ወይንስ ተጭበርብራለች?” በማለት ባፈና ማረጋገጫ በመፈለግ ባልና ሚስቶቹን ጠየቁ፡፡ ሳቅ ቤቱን ሞላው፡፡ “ባፈና እርስዎም ደግሞ እነዚህ ልጆች ምርጫው ተጭበርብሮአል ምናምን እንደሚሉት ኢትዮጵያ ተጭበርብራለች የማናውቃት ሀገር ሆነች ነው የሚሉት” ብለው ዳግም ተሳሳቁ፡፡
አዲስ ዘመን ሲመጣ ለኢትዮጵያውያን ታላቅ አውደ ዓመት ነው፡፡ ከባዱ የሁለት ወራት ጨለማ፣ የክረምቱ ዶፍ ዝናብ፣ አስገምጋሚው መብረቅ፣ ጎርፉና የወንዞች ሙላት ግሳት መስከረም ሲገባ ተገግ ይላሉ፡፡ የደመናው መጥቆርና የሰማዩ ልዘንብ ነው የሚል የማስጠንቀቂያ ማጉረምረም ያበቃል፡፡ መስኮች ደንና ሸንተረሩ በአበቦች ፍካትና ሙላት ይታጀባል፡፡ የአእዋፋት ድምጽና ዝማሬ በየቦታው ይስረቀረቃል፡፡ የመስቀል ወፍ ከተደበቀችበት ብቅ ትላለች፡፡
ክረምቱ አበቃ የምትል መልእክተኛ ናት፡፡ አገር ምድሩ ውብ ሆኖ የመስከረምን ሽታ ይዞ ንፋስ የሚነፍስበት አልባብ አልባብ የሚሸትበት ጊዜን ታስተዋውቃለች፡፡ በበአሉ ቤተሰብ ጎረቤት በያለበት በጋራ ያለውን ደግሶ አብሮ በልቶና ጠጥቶ ለዕለቱ ያደረሰውን አምላክ አመስግኖ የከርሞ ሰው በለን ብሎ የሚመራረቅበት ደግ ደጉን የሚመኝበት ወር ነው፤ ገምሻራው መስከረም፡፡ ሴቶች ልጃገረዶች እንቁጣጣሽ ብለው በየቤቱ እየዞሩ እንኳን አደረሳችሁ የሚሉበት በዓመት አንድ ቀን ብቻ የሚከበር የዓመቱ መግቢያ አሀዱ ነው፡፡ መስከረም በተስፋ በብርሃን በልምላሜ በአዲስ ትልምና እሳቤ ሕይወት የሚጀመርበት የወራቶች በኩርና አውራም ነው፡፡
በኖረውና በቆየው የአገራችን ባሕል መሰረት ሁሉም ዜጋ በአቅሙ ያለውን ደግሶ አዘጋጅቶ በደስታ በሰላም በፍቅር ይቀበለዋል፡፡ ዶሮው፤ በጉ፤ ቅርጫ ስጋው የዘመድ አዝማዱ መሰባሰብ የጎረቤቱ ድግስና አብሮ መብላት መጠጣት፤ አክፋይ ይዞ ወደ ዘመድ መሄድ የድሮው ብርቅዬ ባሕላችን ነበር። አክፋይ በዚህ ዘመን ይኑር አይኑር እንጃለቱ። ድፎ ዳቦ፤ ኡዞ አረቄ ወይንም ቪኖ በወረቅት ተጠቅልሎ አባወራውና እማወራዎቹ የሀገር ባሕል ልብስ ለብሰው ልጆች ደግሞ ስጦታውን ተሸክመው እናት አባት አክስት ታላቅ እህት ወንድም ቤት ይኬድ ነበር ድሮ፤ የዛሬን አያድርገውና፡፡
እንዴት አይነት የሚያኮራ የደመቀ ያልተበረዘ ባሕል ነበረን በል፡፡ የጠበቀው ካለ እሰየው፡፡ ኢትዮጵያዊነትን የሸረሸረው አንዱ ከራስ ማንነት መፋታት ነው። እንደ ኃላ ቀርነት እየቆጠረው የነበረውን ትልቅ ባሕል በባእዳን ባሕል እየተለወጠ እንዳይሄድ አደራችን ይጥበቅ፡፡ እነ አቶ አቻምየለህ ወይዘሮ ጫልቱና ወይዘሮ ባፈና የዚያ ወርቅ ዘመንና ባህል ሰዎች ናቸው፡፡ ጎረቤታቸው አቶ እንዳሻው የቀን ስራ እየሰራ ከጎናቸው ባለች ትንሽ ክፍል ውስጥ የሚኖር ረዥም ዘመን አብሮአቸው ክፉውንና ደጉን ያሳለፈ ሰው ነው፡፡ ሁሉም እንደቤተሰብ ያየዋል፡፡ ብዙዎቹን ልጆች ያሳደገ በፍቅር የሚወደድ ተጫዋች ነው፡፡ እሱ በሚናገረው እንባቸውን እስኪረጩ መሳቅ እንጂ የሚቀየመው ማንም የለም፡፡ መንደሩ በሃዘንም በደስታም ጊዜ የሚጠራው እሱኑ ነው፡፡
ትዳር ልጅ የለውም፡፡ የመንደሩ ልጆች ሁሉ ልጆቹ ናቸው፡፡ ሰርቶ ከሚያገኛት ገንዘብ ወደ ቤቱ ሲመለስ ከረሜላ ዳቦ ገዛቶ አምጥቶ ለልጆቹ ያከፋፍላል፤ ያስቃቸዋል። ተጫዋች ነው፤ እንዳሻውን ማን ይጠላል፡፡ የእሱ ዓመት በአል ጎረቤቶቹ ናቸው፡፡ ሚስት የለው ድስት። እሱም ይህ የኑሮ ውድነት ወሬ በእጅጉ አሳስቦታል። እዛ የሚመገብበት ቤት ባዶ ሽሮ ወጥ በእንጀራ 20 ብር ብለውት ሲጨነቅ ከርሟል፡፡ ከዓመታት በፊት 3 ብር የነበረው ሽሮ በኃላ ዋጋ ጨምሮ 8 ብር እየከፈለ ነበር የሚመገበው፡፡ አዛውንቶቹ ስለኑሮው ጉዳይ ሲጨዋወቱ ድንገት እንዳሻው ደረሰና ዝቅ ብሎ ሰላምታ አቀረበ፡፡
ተቀመጥ ተብሎ ተቀመጠ፡፡ “እትዬ አርቦኝ ነው የመጣሁት ትርፍራፊ እንጀራ አለ ?” አላቸው ወይዘሮ ጫልቱን፡፡ ወይዘሮ ጫልቱ እንስፍስፍ እናት ናቸው፡፡ እንዲህ ነበሩ የኢትዮጵያ እናቶች፡፡ “አለ ልጄ እንዳሻው” ብለው ያለውን ሊያቀርቡለት ወደ ጓዳ ገቡ፡፡ አመጡለት። የቀረበለትን እየጠራረገ እየበላ በየቦታው በሄደበት የሰማውን የኑሮ ውድነት ብሶት ነገራቸው፡፡ ሕዝቡ የትም ቦታ ስለነጋዴው አረመኔነትና ክፋት ስለኑሮ ውድነቱ ነው የሚያወራው፡፡ “ምንድነው የሚሻለው” አለና ጠየቀ፡፡
“እኔን እኮ ስራ ያላገኘሁ ቀን የሚያበላኝ የሚያጠጣኝ ሕዝቡ ነው፡፡ ሕዝቡ ካጣ ከሌለው እኔስ ምን እሆናለሁ?” አለ ውስጡ በሃዘን ተሞልቶ። አቶ አቻምየለህ “ሰማህ እንዳሻው እንግዲህ ምን እናደርጋለን ፈጣሪ ያውቃል፤ እሱ አንድዬ ያውቃል” አሉ፡፡ በእኛ ጊዜ ኑሮው ርካሽ ሰውም ትንሽ ነበር። ዛሬ ከመብዛቱ የተነሳ መላወሻ መተናፈሻ ጠፋ፡፡ ብዙ ተባዙ የተባለው ቃል በኢትዮጵያ ምድር ሞልቶ ተረፈ፡፡ ሕዝቡ እንደ ቻይናና ሕንድ በሕዝብ ብዛት አለምን ያስጨንቃል፡፡
የኑሮው ውድነት እንዴት ይገፋ ይሆን በማለት ሁሉም አቀረቀረው ተከዙ፡፡ “እንግዲህ ልጆቹ ገንዘብ ከላኩ ወጥተህ ትንሽ ጠቦት ትገዛለህ፤ ካላኩም በቂጣና በቆሎ እንውላለን ሌላ ምን ይደረጋል ?” አሉ አቶ አቻምየለህ፡፡ እንዳሻው ሁሉም እየሰሙት ድምጹን ከፍ አድርጎ “ሕዝቡ በኑሮ ውድነቱ ስለተጨነቀ ዓመት በአሉ ይቀየር” አለ፡፡ አዛውንቶቹ በሳቅ ቤቱን ሞሉት፡፡ እውነት ነው ዓመት በአሉ ይቀየር !
አዲስ ዘመን ነሐሴ 30/2011
ወንድወሰን መኮንን