ቀደም ሲል ስለጋዜጠኝነት ሙያ ሥልጠና ለመውሰድ ወደ ቻይና ሄጀ በነበረበት ወቅት የጠላት መከላከያ ምሽግ የሆነውን ታላቁን የቻይና ግንብ ለመጎብኘት እኔና ጓደኞቼ እድል አግኝተን ነበር። ቦታውን ስንጎበኝ የአፍሪካ ቱሪስቶች መሪና አስተርጓሚ ሆና ትሠራ የነበረችው ሆው ሉዊስ (ኢትዮጵያውያን ጓደኞቼ ጫልቱ የሚል ስም የሰጡዋት ) ወጣት ከቻይና ሥነቃል ተነሥታ ስለ ታማኝቱ አፍቃሪ ስለ ሚንግ ጂያንግ፤ ስለ ባለቤቷና በታላቁ የቻይና ግንብ ሥራ ስለነበረው ተሳትፎ አጫውታን ነበር።
ሉዊስ እንደተረከችልን ቆንጆይቱ ሚንግ ጂያንግ በቻይና ስለ ታላቁ ግንብ ከሚነገሩ ታሪኮች ውስጥ አራተኛው ሥነ ተረት ተደርጎ ይታያል። ይህ ከ2200 ዓመት በላይ እድሜ ያለው፤ በኲዊን ሥርዎ መንግሥት ዘመን የታወቀና በአፈ ታሪክ ላይ የተመሠረተ ሥነ ተረት ነው።
ሥነ ተረቱ የተገኘው በብራና ላይ (ማኑስክሪፕት) በእጅ ተጽፎ ነው። ወይዘሪት ሉዊስ እንዳለችው ሚንግ በመልካም እንክብካቤ ያደገች፤ እጅግ በጣም ቆንጆ፤ ሙዚቃ የመድረስና ግጥም የመግጠም ችሎታን የታደለችና የፈላስፋው የኮንፊሺየስ ዓይነት አስተሳሰብ የነበራት ወጣት ናት። ከዕለታት በአንዱ ቀን ከሰዓት በኋላ ሚንግ ጂያንግ በቤተሰቦቿ ግቢ ውስጥ በሚገኝ የአጸድና አትክልት ቦታ ውስጥ አበቦችን ተመስጣ በማየት ላይ እንዳለች በአጸዱ አጥር በኩል ያያት በነበረ አንድ ወጣት ስሜቷ ተሰረቀ።
ወጣቱ ዋን ጂሊያንግ እንደሚባልና ታላቁን ግንብ ይገነባ ከነበረው የመጀመሪያው ንጉሥ አምልጦ የመጣ ሠራተኛ እንደሆነ ነገራት። በረሀብና በችግር በጣም እንደተሠቃየም ገለጸላት። ቆንጆይቱ ሚንግና ቤተሰቦቿ ወጣቱ እንግዳ ዋን ጂሊያንግ አብሯቸው እንዲቆይ ፈቀዱለት። በእውነትም ወጣቱ የተማረና መልካም ሥነ ምግባር ያለው ሰው ነበር። ቆይቶ እጅግ በጣም ቆንጆ የሆነችው ሚንግና ወጣቱ ዋን ጂሊያንግ በፍቅር ወደቁ። የሚንግ ቤተሰቦች ተወዳጇ ልጃቸው ትዳር ለመመሥረት እጮኛ ስላገኘች በእጅጉ ተደሰቱ።
ወዲያውም ጋብቻ መሠረቱ። ነገር ግን በሰፈሯ በውበቷ የተነደፈ ሌላ ሰው ጋብቻዋን በምቀኝነት ተነሣሥቶ ለማደናቀፍ ስለፈለገ በአካባቢው ወደሚገኙ ባለሥልጣኖች ዘንድ ሄዶ አቤቱታ አቀረበ። በሠርጋቸው ቀንም የወደፊት ባለቤቷ ዋን ጂሊያንግ ተይዞ በሰሜን ቻይና የታላቁ ግንብ ወደሚገነባበት ቦታ ተላከ። ወጣቷ ሚንግ ጂያንግ ያገባችው አዲሱ ባለቤቷ ወደእርሷ እንዲመለስላት ቀንም፤ ሌትም ትጠብቀው ጀመር።
የበጋው ወቅት ገብቶ እስኪያልፍ ድረስ በጉጉት ስሜት ሆና ስለእርሱ ብታስብና ብትጨነቅም ምንም ዓይነት ቃል፤ አንዳችም መልእክት ከዋን ጂሊያንግ ሊመጣላት አልቻለም። ለብዙ ቀናት በሐሳብ ስትሰቃይ ከቆየች በኋላ በመጨረሻ ክረምቱ ሲገባ ለባለቤቷ የሚበረከቱ የክረምት ልብሶችን አዘጋጅታ እስካለበት የታላቁ ግንብ ፕሮጀክት ድረስ ሄዳ ዓይኑን ለማየት ወሰነች።
ቤተሰቦቿ ግን እንዳትሄድ ቢቃወሟትም የእነርሱ ተቃውሞ ምንም ዓይነት ቁብ ሳይሰጣት ተራራዎችንና ወንዞችን እያቆራረጠች የታላቁ ግንብ እስካለበት ቦታ ድረስ ተጓዘች። እዚያም ስትደርስ ወፈ ሰማያት የሆነ የቀን ሠራተኛ በበዛበት መሃል ዋን ጂሊያንግን ፈልጋ ለማግኘት በማትችልበት ሁኔታ ውስጥ ሆና ላይ ታች ትባዝን ጀመር።
በመጨረሻ ስታጠያይቅ ባለቤቷ ዋን ሒሊያንግ በታላቁ ግንብ ሥራ ብዙ ሥቃይና እንግልት ከደረሰበት በኋላ በዚሁ የሥራ ጫና ምክንያት እንደሞተ መርዶ ተነገራት። እሪ ብላና ራስዋን ስታ ወደ መሬት ወደቀች። ራሷን ስታውቅ ኀዘኑ ልቧን ይበላው ጀመር። ዕንባዋም እንደ ጎርፍ እየወረደ ትጮህ ጀመር። የት እንደተቀበረና ዐፅሙ የት እንዳረፈ ለማወቅ ተቸገረች።
በዚህ ዓይነት ለሦስት ቀናት ያህል ስታለቅስ ቆይታ እስከታላቁ ግንብ ጫፍ ድረስ በእግርዋ ወጣች። በድንገትም ተአምራዊ ነገር ይፈጠራል። ይኸውም የግንቡ 800 ማይል የሆነው ክፍል በታላቅ ፍንዳታ ተሰባብሮ ይወድቃል። በወደቀበት ሰዓትም የእርሷን ባለቤት ጨምሮ የበርካታ ሰዎች ነጫጭ ዐፅሞች ከድንጋይ ስብርባሪና ከአቧራ ጋር በላይና በውስጥ እየሆኑ መታየት ጀመሩ።
ዐፅሞችን ስትመለከት በበለጠ ከጭንቀት ላይ ወደቀች። ወዲያው ጣቶቿን አደማችና «ይህ የምመለከተው ባለቤቴ ከሆነ ደሜ ወደ መሬት ሰርጎና የባለቤቴን ዐፅም ሰርስሮ እንዲገባ ምኞቴ ጥልቅ ነው » ብላ ጸለየች። የሙታን ራስ ቅሎችንም ተመልክታ ወደየቤተሰቦቻቸው መልእክት ለማድረስ ትችል ዘንድ ጠየቀቻቸው። የራስ ቅሎችም ለጥያቄዋ በግጥም እንዲህ ሲሉ መለሱላት።
በፀደይ በክረምት እንዲሁም በበጋ፤
በቢጫማው ዐፈር በአሽዋው መሬት ላይ ተኝተናል ባልጋ።
በይ ቃል አድርሽልን ጽንዓት ቢሆናቸው፤
ለየሚስቶቻችን ለተለየናቸው።
መዝሙር አሰሚልን ለየነፍሶቻቸው ፤
የእኛ መሥዋዕትነት መድኅን ቢሆናቸው።
ዋን ጂሊያንግ ሲሞት ሰውነቱ ከታላቁ ግንብ ጋር ተጣብቆ የግንቡ አካል ሆኗል። ነፍሱ በአየር ላይ እየተቅበዘበዘች ባለቤቱን ሚንግን እንዲህ ትላለች። « ከመሬት ውስጥ የምገኘው እኔ አንድ ድሃ ወታደር ለምን ጊዜም አልረሳሽም ከድንጋይ ክምር ጋር ስዋደቅ ነው የወደቅሁት»። ባለቤቱም ይህንን ስትሰማ «አሁን አባትና ምንም ዓይነት ዘመድ የለኝም፤ ባል ልጅ የለኝም፤ የምሄድበት ቦታም የለኝም የምፈልገው እንዳንተ እዚሁ መሞት ብቻ ነው»።
ይህ ስለታላቁ የቻይና ግንብ የሚነገረው ሥነ ተረት በይዘትም በቅርጽም እየተሻሻለና በጥናትና ምርምር እየዳበረ ከመምጣቱ ባሻገር በብዙ የዓለም ቋንቋዎች ተተርጉሟል። በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ግን ገና የተተረጎመ አይመስልም። የቻይና የኪነ ጥበብ ሰዎች የሚንግንና የዋን ጂሊያንግን ፍቅር መነሻ አድርገው «የወጣቷ ሚንግ ያንግ የ12 ወራት አበባዎች» በሚል ሳቢና ማራኪ በሆነ መንገድ ኅብረ ዝማሬ ሠርተውላቸዋል።
የመጀመሪያው ውቅት የአበባ፤ ሁለተኛው የፍቅርና የተስፋ ፤ ሦስተኛው የድንጋጤና የጥርጣሬ… እያለ አስከ አሥራ ሁለተኛው ወር ይደርሳል። ይህ ወር ለሚንግ የመከራና የጭንቀት ጊዜ ሆኖ ተሥሏል። ሚንግ ለብቻዋ ሆና «ሁሉም ቤተሰብ ከደስታ ብዛት የተነሣ በየቤቱ ቀይ መብራት እያበራ ነው፤የጎረቤቶቼ ባለቤቶች ወደቤታቸው በሰላም ተመልሰው ከፍቅረኞቻቸው ጋር ተገናኝተዋል፤የእኔ ባለቤት ብቻ ታላቁን የቻይና ግንብ እገነባለሁ ብሎ እንደወጣ ቀረብኝ፤ ዐፅሙ ከግንቡ ጋር ተላትሞ ግድግዳ ሆነ፤ ደሙ አሸዋና ሲሚንቶ ሆኖ ግንቡን አጸናው፤» እያለች ስታለቅስ፤ ስታዝንና ስትተክዝ ትታያለች። ነፍሱ ከቦታ ቦታ እየተዘዋወረች በደሏን በመናገር« ውድ ባለቤቴ ሆይ እኔ ድሃው ባለቤትሽ ሞቼና ተቀብሬ ከመሬት በታች ብሆንም ለምን ጊዜም አልረሳሽም» ስትል ትሰማታለች።
ወጣቷን ለከፍተኛ ኀዘንና ሰቆቃቀው የዳረጋት በኵይን ሥርዎ መንግሥት የመጀመሪያ የነበረው ጨካኙና አምባገነኑ ንጉሥ ነው። የመሠረተውን አዲስ መንግሥት ከጠላት ለመከላከል ሲል በርካታ የቻይና ወጣቶችን እያስገደደና እያዘዘ ታላቁን ግንብ እንዲገነቡ፤ ለሕይወታቸው ሳይጨነቅ እንደባሪያ ሌትም ቀንም ያለዕረፍት እንዲሠሩ ያደርጋቸው ነበር። ከዚህም ተነሣ በርካታ ወጣቶች በናዳ፤ በመሬት ነውጥና በእሳት ቃጠሎ፤ በተስቦ በሽታ አልቀዋል። ጭካኔ በተሞላበት የግንባታ ሥራ ልጆቻቸውን፤ ዘመዶቻቸውን፣ ባለቤቶቻቸውንና ልጆቻቸውን ካጡና እድለቢስ ከሆኑ ወጣት ሴቶች ውስጥ አንዷ ሚንግ ሆነች። ቻይናውያን ለሚንግ ማስታወሻ እንዲሆን በኪንግሁዋንግ የደሴት ከተማ ቤተመቅደስ ሠርተውላታል።
ቻይናዊው ንጉሠ ነገሥት የሞተ ባለቤቷን እያስታወሰች እንደምትጨነቅ ስለሚያንግ ሁኔታ በሰማ ጊዜ ወደእርሱ ዘንድ እንዲያመጧት አዘዘ። ወደ እርሱ ዘንድ መጥታ ባያት ጊዜ በውበቷ ተማረከና ሊያገባት ወሰነ። ሚንግም ንጉሡ ሦስት መሠረታዊ ነገሮችን ካሟላላት ልታገባው እንደምትችል ተስማማች።
የጠየቀቻቸው ሦስት ነገሮች አንደኛ ለሟች ባለቤቷ ክብር ሲባል ለ49 ቀናት የመታሰቢያ በዓል እንዲደረግለት፤ ሁለተኛ ንጉሠ ነገሥቱና ባለሥልጣኖቹ በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ላይ እንዲገኙ እንዲደረግላት፤ ሦስተኛ ለሞተው ባለቤቷ መሥዋእት ለማቅረብ እንድትችል በወንዙ ዳር 49 ሜትር ርዝመት ያለው ሰገነት ( ማማ) እንዲሠራላት የሚል ነው።
ንጉሠ ነገሥቱን ኲይን ሺ ሁዋንግዱም ወጣቷ የጠየቀቻቸው ሦስት መሠረታዊ ነገሮች በአንድ ጊዜ እንደሚፈጸሙላት ማለላት። በመሐላው መሠረትም የጠየቀችውን ሁሉ ፈጸመላት። ሁሉ ነገር ከተዘጋጀ በኋላ ከሰገነቱ ላይ ወጥታ ደካማነቱንና ጨካኝነቱን እያነሣች ንጉሠ ነገሥቱን ኲይንን በኃይለ ቃል ትዘልፈውና ታወግዘው ጀመር። ይህንን ከተናገረች በኋላ ከማማው ላይ ዘልላ ወደ ባሕሩ ራስዋን በመጣል ጠልቃና ሰምጣ ሞታለች።
አዲስ ዘመን ነሐሴ 26/ 2011
ታደለ ገድሌ ጸጋየ ዶ/ር