እንዴት ከረማችሁልኝ ውዶቼ? የዚህች ሰላምታ መልስ በተለየያ ሁኔታ ውስጥ ቆይታችሁ እንኳን “ደህና” እያላችሁ መመለሳችሁ የተለመደ ነው። አዎን ሰላም ከርማችሁ፤ አሊያ ደግሞ በተለየ መጥፎ ገጠመኝ ሰንብታችሁ ደህና የምትሉበት ምክንያት ደህና ለመሆን መመኘታችሁና ደህና የመሆን ብርቱ ፍላጎት የፈጠረው ደህና ስሜት ነው። ያ ነው ደህና ሳትሆኑ እንኳን “ደህና ነኝ” ያሰኛችሁ። ሰላም መሆን ከሁሉ የሚቀድም፤ ደህና መሆን ከሁሉ የተሻለ ነውና ደህንነት ውደዱ!
በተለያየ ጥሩም መጥፎም ገጠመኝ ሰንብታችሁ “ደህና ነኝ” ማለታችሁ ደግ ነው። እንጂማ አዋዋልና አከራረማችንን እናውራ ካልን ደግና ክፉ ዘርዝረን አንጨርሰውም። ፍፁም ንፁህና ታማኝ፤ የማንዋሽና ውሸትን የምንጠላ እንኳን ብንሆን በሰላምታ ልውውጣችን ወቅት ለተጠየቅነው ጥያቄ የምንሰጠው ምላሸ ትክክለኛ አይደለም።
ትክክለኛ ያልሆነው መልሳችን ግን ትክክልና ተገቢ ነው። አዳራችን ጥሩነት የራቀው፤ የተመሰቃቀለ ሆኖ እንኳን “ለእንዴት አደርክ” ወይም “እንዴት አደርሽ” ጥያቄ የምንሰጠው ምላሽ “ደህና” የሚል ነው። ሰላምታ ውስጥ ትክክል ያሆነ ምላሽ ትክክል ይሆናል፤ መልካም ነገር ውስጥ ስህተት ታርሞ ይታያል ወይም የተዛባ ነገር ይቃናል። የበጎ እሳቤ ምላሽ በሁሉም ሁነት ውስጥ የቀና መልስ ያገኛል። “ደህና ነን” የምንለው የደህንነትን ክብደት ጠንቅቀን ተረድተን እንኳን ላይሆን ይችላል። ነገር ግን ደህንነት ሳያስተውሉትም አሊያም ሳያጤኑትም ደህና ነውና ለ“እንዴት ነህ?” ምላሻችን ሁሌም “ደህና” የሚል ሆኗል።
ከምንም ነገር አስቀድመን የምናቀርበው ሰላምታ “ሰላም ነው?” የሚለው መግቢያችን “ሰላም ሁን” ወይም “ሰላም ሁኚ” ብለን ለመደምደማችን መነሻው የሰላም ትልቅነት ገብቶን የሰላም መሆን ፋይዳው ተረድተን ነው። ሰላምታችን ሲለዝብ በሰላም ነው? መባላችን የተለመደ ነው። ወዳጅ ዘመዳችን ሰላምታችን በትክክል ባይመልስ ወይም መልሱ ላይ ደህና ነኝ ብሎን እንኳን አመላለሱ ባያጠግበን መጨነቃችን አይቀርም። በድምፁ ቅላፄ ወይም በመልሱ ብቻ ደህና ነኝ ማለቱ ብቻ ደህና እንዳልሆነ ያስረዳናል። ሰላም ማጣት ከሁሉ የከበደ ነውና ሰላሙን አጥብቀን እንጠይቃለን። በቻልነው አቅም አጥብቀን እንጠይቃለን፤ ያጣውን ሰላም እንዲያገኝ እንመክራለን፣ እንረዳለን።
የሰላም ዋጋ ትልቅ ነውና፤ ደህንነት ከፍ ያለ ፀጋ ነውና ደህና የመሆን ልባዊ ምኞት በደህንነት ማረጋገጥ ይጀመራል። በምኖርበት አካባቢ አንድ የአዕምሮ ህመምተኛ አለ። ለ’ሰላም’ ትልቅ ቦታ ያለው፤ ሌላ ንግግር የለውም ። ‘ሰላም ነው?’ የዘወትር ጥያቄው ከሰው ጋር መቃረቢያ፤ አንደበቱ የተገራበት ብቸኛ ቃል እስኪመስል የእሱነቱ መለያ ሆኗል። እንደ ቢጤዎቹ ሰውን መተናኮል የማያውቅ፣ ካፉ ደጋግሞ የሚያወጣውን ቃል ያህል ሰላሙ የበዛ፣ እንደአዕምሮ ህመምተኛ ሰውን ሲቀርብ ስጋት የማይፈጥር ሰላማዊ ህመምተኛ ነው። በአብሮነት ቆይታው “ዋናው ሰላም መሆን ነው። ” በማለት የሰላም ታላቅነት ከኛ በላይ የገባው፤ ስለሰላም ያለው ምልከታ እጅግ የተለየ ለመሆኑ ማሳያ ነው።
ይሄ ህመምተኛ እንደቀረበው ሁሉ ሲለይም ቃሉ ጣዕም ያለው ሰላምን ያዘለ ነው። “ሰላም ሁን” ወይም “ሰላም ሁኚ” የስንብት ቃሉ ነው። ይሄ ሰው ስለሰላም ማን አሳወቀው የሁልገዜ ጥያቄዬ ነው። ምንአልባት በውስጡ የተፈጠረው ሰላም ማጣት ጉዳቱ ገብቶትና ሰላም ከምንም በላይ መሆኑን ተገንዝቦ፣ አሊያም የኛ ሰላም አለመሆን ሰላሙን እንዳይነሳው ስጋት ገብቶትም ሊሆን ይችላል። ብቻ የሰላም ዋጋ ገብቶት አሊያም በአጋጣሚ ሰላም ማለትን ያበዛል፤ በጎ ምኞት ይደራርባል።
እናንተዬ የሰላምታ ልውውጣችን ግን ጥያቄ ባይሆን መልካም አይመስላችሁም። “እንዴት ዋላችሁ?” ስንባል የዋልንበት እንቅጩን ከመንገር ይልቅ እየዋሸን እኮ ነው። በበጎም በመጥፎም አጋጣሚ ቆይተን ደህና ማለት የምናዘወትር ብዙዎች ነን። እርግጥ ደህንነት እንዲሰማን በምንም ሁኔታ ውስጥ ደህና ነኝ ማለቱ ይሻል ይሆናል። ግን ደግሞ እቤቱ በምስቅልቅል ሁኔታ ያደረን ሰው “እንዴት አደርክ?” ከማለት ይልቅ “ሰላምህ ይብዛ” ብንለው አይሻልም። እኔ ይመስለኛል፤ ሰላምህ ይበዛ መሰኘት የበለጠ ደህና የመሆን ስሜት ይፈጥራል። ግን የምናወራው ስለ ሰላምታ ስለሆነ ሰላም በምንም መመዘኛ ውስጡ ሰላም ነውና አያወዛግብም። የተሻለ ብዬ ሀሳብ ሳነሳ ያኛው ያልተሻለ ነው ለማለት አይደለም። በሰላም ውስጥ ሁሉም መልካም ሁሉም የተሻለ ነው።
በመጥፎም እንክረም በበጎ “ሰላም?” ስንባል ምላሻችን የሰመረ መሆኑ ለዚህ ነው። በነገራችን ላይ፤ ስለ ሰላም ተብሎ ሁሉ ነገር ቢተው፤ ከሰላም ጋር ሁሉም ቢታረቅ የዓለም ገነት መሆን፤ የምድር እረፍት አይታያችሁም። ስለምን ተብሎ ይሆን ለሰላም ተብሎ ሰላም የምናጣው? እርግጥ ሰላምን ማብዛት፤ ሰላምን ማስፈን፤ የፈለገ ሰላምን መከተሉ ግድ ይላል። አልናፈቃችሁም ሰላም ሆነን፤ ወጥተን መግባት፤ ሰላም ሆነን ወደ ፈለግነው የሀገራችን ጥግ ደርሰን መመለስ፤ ሰላም ሰፍኖ ፍቅር ፀንቶ ማየት!
ሰላም እኮ ዋጋው ትልቅ ለመሆኑ ከኛ ከኢትዮጵያውያን የተሻለ አስረጂ የለም። ሁሉ ኖሮን ሁሉን ያጣነው ለራሳችን ሰላም ባለን አተያይ አይመስላችሁም። ዛሬ ላይ የምናነሳና የምጥለው ነገር በዝቶ ተቸግረናል። በየሳምንቱ እርስ በርስ የምፋጭባቸው ጉዳዮች እንደ አጀንዳ መቅረፅ አዘውትረናል። ስለሰላም የሚሰብከው ቀንሶ፤ ሰላም የሚለው አንሶ “ዋ ነግሬሀለሁ!” የሚለው በዝቷል። አያችሁ ውዶቼ በ”ነግሬሀለሁ” ውስጥ ብዙ ድምፀት አለ። “ካንተ እኔ እሻላለሁ። ካንተ እኔ እበልጣሁ፣ እኔ ያልኩትን ብቻ ስማ፣ እኔ ነኝ የማዋጣህ፣” የመሳሰሉ ብዙ ትርጓሜዎች፤ ነገር ግን አንዳቸውም ውስጥ ሰላም የማናገኝባቸው ፍቺዎች፤
ውዶቼ! ስንቱ የሰላም ጥቅም አልገባ ብሎት፤ ስለሰላም አልሰማ ብሎ ሰላም ሊያሳጣን በሚሮጥበት ሀገር ሰላም ደጋግሞ መመኘት ሳይኖርብን አይቀርም። እኔ ’ምለው የሀገራችን ፖለቲከኞች ግን አይሰለቻቸውም? በየሳምንቱ አዳዲስ ጉዳይ እያነሱ እርስ በእርስ መነታረካቸው መች ይሁን የሚያበቃው? ስለ ሀገር ደህንነት፤ ስለ ህዝብ ሰላም ብለው መች ይሆን የሚሰሩት? ተቆረቆርኩለት የሚሉትን ህዝባቸውን ሰላሙን ሰጥተው ለምን አይገላግሉትም። ራሴን ልቆርቁርብህ ካልሆነ በቀር ስለ ህዝብ መቆርቆር ለህዝብ ምቾት መስጠት፤ ለወገን ሰላም መስጠት ካልሆነ በምን ይለካል። በሰላም ነው ግን እንዲህ መሆናቸው?
የእውነት የሰላምን ያህል የገዘፈ፤ የደህንነትን ያህል የተወደደ ፈፅሞ የለም። እስኪ ሰላምን ስበኩንና፤ ስለሰላም አውሩንና፤
ወደ ሰላም ጥሩንና ተሰባስበን እንቅረባችሁ። ሰላም ያጣነውን ሁሉ ማግኛ መንገድ ነው። ስለሰላም በጎነት ማውራት የተሰለቸ ግን የማይሰማ
መሆኑን ለማወቅ የአሁኑን የዓለም ሁኔታ ማጤኑ ብቻ ይበቃል። በሰላም እጦት ለተጨነቀችው ምድር ሰላም እንዲወርድ የሰላምን ባንዲራ
ማውብለብ ግድ ይላል። ምን ዋጋ አለው? የሰላምን ባንዲራ ረግጦ ቆሞ ሰላምን ከሌላ ቦታ የሚፈልግ በዝቷልና መፍትሄው ቸገረ። ሰላም
ከምንም የሚልቅ፤ ሲታጣ የሚጨንቅ፤ ሲኖር የሚቀል፤ እራሳችን የምንጠብቅው፤ የምናስቀጥለው ውድ በረከት ነው። ሰላማችሁ እንዲበዛ
ተመኝቼ፤ ውሏችሁ እንዲቀና በጎ አስቤ ልሰናበታችሁ።
አዲስ ዘመን ነሀሴ 24/2011
ተገኝ ብሩ