በጣም ተቻኩላ ወደ መኪና እየገባች ነው፤ የጠዋቱ ሰዓት እንዴት እንደሚሄድ፤ ከመኝታ ተነስተን ትንሽ እንኳን የቆየን ሳይመስለን ወደ ስራ የምንወጣበት ሰዓት ይደርስና ጥድፊያ ይሆናል። ደጋግሞ መጠራራት “እከሌ …እከሊት” መራሯጥ … ብቻ የሚነሳ የሚወድቀው ነገርም ይበዛል። በተለይ ደግሞ በበጋ ወቅት ያለው ጥድፊያ አይነሳ ። ተማሪዎች በአንድ በኩል፤ ዋናው አካል በሌላ በኩል፤ የራስ እሩጫ እንደዛው፤ በተለይ ለእኛ ለሴቶች መጥኔ አይባልም እንጂ መጥኔ ብል ምንኛ ደስ ባለኝ።
ይህ እንደምንም ተጠናቅቆ ከቤት ከተወጣ በኋላ ደግሞ የቢሮው ተረኛ ሆኖ ይጠብቃል። የፊርማ ሰዓት ደረሰ አልደረሰ ፤ አሻራ አሳበቀ አላሳበቀ ብቻ ጣጣው ብዙ ነው። በነገራችን ላይ ያቺ አሻራ የሰዓት መቆጣጣሪያን የፈጠራት ማን ነው? እኔ ብቻ በጣም አድርጌ እወዳታለሁ፤ ፈጣሪዋንም አመስግኛለሁ። ለጓደኛ፣ ለዘር ማንዘር ምናምን ብሎ ነገር የለም እሷ ካለች፤ ሁሉም የእጁን በእጁ ያገኛል።
ያልተፈረመበትን ሰዓት አይመዘግብ፤ ሌላ ጓደኛ አይፈርም ብቻ ለቁጥጥርና ለክትትሉ እንዴት ጥሩ መንገድ እንደሆነች። ሁሉም ነገር ሀቅ በሀቅ… አድሎ ደህና ሰነብች ። ምናልባት እኔ ያልተረዳሁት በተግባር ግን የሚታወቅ ክፍተት አለባት ከተባለ እታረማለሁ። ምክንያቱም በተግባር የማውቀው ያወቅኩትን ያህል ስለሆነ።
እንዳው የሴቶች ጉዳይ ሲነሳ ብዙ ራሳቸውን የሚያማቸው እንዳሉ አትዘንጉ። ምንም አይደለም፤ የነበርንበት ባህል ልበለው ልምድ ሴትን ሴት ናት ብሎ ከማሰብ የዘለለ ስላልነበር የሴቶች ነገር ሲነሳ ያው ከዛኛው አስተሳሰብ የዘለለ የማያስቡ አይጠፉም። ይሄንንም ስል የማናት ደፋር የሚል አይጠፋም ማለቴ ከወንዱም ከሴቱም፤ ግን እውነታ ነው። ሴቶች ሀላፊ ነታቸውን ይወጣሉ ፤ የቤቱም፣ የውጪውንም፣ ማህ በራዊ ጉዳዩ፣ በስራ ላይ ያለውም … ብቻ ሁሉም ተዳምሮ ጥንካሬያቸው ያስደስታል ።
ብራቮ ! ሴቶች ብል ደስታዬ ነው። አሁንም ደግሜ እላለሁ ብራቮ ሴቶች። ቅር የሚለው አይኖርም እንጂ ይህን በማለቴ ቅር የተሰኘብኝ ካለ አንገቴን ዘንበል አድርጌ አሁን ይሄ ኪስ የማይገባ ለሴቶች በዝቶባቸው ነው? እለው/ እላት ነበር ።
ብራቮ ካልናቸው ግን ይበልጥ ይጠነክራሉ። ይበልጥ ራሳቸውን ያሳድጋሉ። ብቁ ሆነው ለመገኘት ይሰራሉ። ቃላቶች ደግሞ ለድካማ ብርታት ናቸው። ስለዚህ እንበላቸው – ብራቮ። ታዲያ ሴቶችን ለማሸማቀቅ፣ አንገት ለማስደፋት፣ ሞራል ለመንካት እያሉ የሚያስቡ አይኖሩም ብዬ ግን አላስብም፤ ብዙ አሉ፤ ያጋጥሙናል። እንደሚታለፈው እያለፍናቸው መሆኑ ይያዝልን። አዎ! ታላቅ ውጤት ከፍ ወዳለ ደረጃ የሚደረሰው ብዙ በጣም ብዙ አሳዛኝና ፈታኝ ነገሮች ታልፈው፣ ተችለው፣ ተጋፍጠው፣ ታግለው ነው። አንዳንዴም ጦር ሲሰበቅ ጎንበስ ብሎ በማሳለፍ ጭምር መሆኑ አይዘንጋ።
የተነሳሁበትን ጉዳይ ትቼ ወደ ሌላው ስምጥ አልኩ አይደል? የእኔ ነገር እስኪ ወደተነሳሁበት ልመለስ። እና ያቺ የተጣደፈች ሴት በራፏ ላይ የቆመው መኪና ውስጥ ከገባች በኋላ ማታ ለቅሶ እሄዳለሁ ብላ ያዘጋጀችውን ጥቁር ሻርፕ አለመያዟን ስታረጋግጥ በር እየዘጋች ያለችውን የቤት ሰራተኛ ፈጠን ብላ ስሟን በመጥራት” እባክሽ የረሳሁትን ጥቁር ሻርፕ አቀብይኝ ” ብላ በማዘዝ የሚመጣውን ሻርፕ መጠበቅ ጀመረች።
ረፈደብኝ ብላ በምን አይነት ጥድፊያ ላይ እንዳለች አትርሱት። የተላከለችው ልጅ የቁራ መልዕክተኛ እንደሚባለው በዛው ቀረች እንዳልላችሁ ከች ብላ እትዬ “የአባዬን ነው?” ብላ መጠየቅ ። ማሽላም ሲያር ይስቃል ይባል የለ። ከት ብላ ስቃ “አባዬ ጥቁር ሻርፕ አለው? ኧረ የእኔን ወንበር ላይ ያደረኩትን ነው” ስትላት ሮጥ ብላ ይዛ መጣች።
ይቺ ሴት ያችን ልጅ ምን የምትላት ይመስላችሁል? ብዙዎቻችሁ ስድብ፣ ቁጣ ወይም ሌላ ነገር ልትሉ ትችላላችሁ ግን አይደለም። “አመሰግናለሁ! እግዚአብሄር ይባርክሽ!” ነው ያለቻት። ልጅትም ፈገግ ብላ ምስጋናዋን አፍሳ ወደ ግቢ ገባች፤ እኛም ወደ መንገዳችን። ገጠመኙ ግን መኪናው ውስጥ ለነበርነው ሁሉ የሀሳብ መለዋወጫ ምክንያት ሆነን።” አባዬ ጥቁ ሩን ሻርፕ መቼ መቼ ነው የሚለብሱት አንዷ ፌዘኛ ያነ ሳችው የሽርደዳ ቃል ነበር። ሁላችንም እሳቸው ለለ ቅሶ ሳይሆን ጥቁር ሻርፕ ለሰርግ ነው የሚለብሱት። ከረባት መስሏት ይሆናል? … ብቻ ጨዋታው በዛው ደራ።
እኔን ያስደሰተኝ ምስጋናው ነበርና ቃላት የታመመን ያክማል ፤ ጤነኛን ያሳምማል ማለቴ ጨጓራ አስያዘችኝ ፤ አስያዘኝ የሚባሉ ሰዎች እኮ ሞልተዋል ። በቃላት ውርጅብኝ ምክንያት። ይህቺ ሴት ጨጓራውን የታመመ ብታገኝ እንኳን ታድናለች። አልወጣትም እንጂ “አንቺ ደደብ፣ ደነዝ፣ ….እሱ ሻርፕ ይለብሳል ሰዓቴን አቃጠልሽው፣ አቃጠልሽኝ፣ ያቃጥልሽ…” ብትላት ኖሮ ያቺ ልጅ ሙሉ ቀኗን ስድቡ በአእምሮዋ በነጻ ሲመላለስ፣ እሷም ስትብሰከሰክ ደግሞ ሌላ ጥፋት ስትጠነስስ ትውላለች።
ያውም ሴቲት ከስራ ልክ እግሯ እንደገባ “ዘመድ ሞቷል ተብሎ ተደወለልኝ” ካላለቻት ማለቴ ነው። እሷም ብቻ አይደለችም፤ የተሳደበችውም ቢሆን አእምሮዋ እረፍት ያጣል። በመሳደቧ ትጸጸታለች ወይም ደግሞ ያንኑ ተሳዳቢነቷን ስትደግመው ስታላምጠው ትውላለች። ቀኑ ምንም ባላጠፋው የቀን ጎዶሎ ትለውም ነበር። ይሄ ታዲያ ለማንም ለምንም በማይጠቅም መንገድ መመላለስ መሆኑ ይያዝ ።
አንድ ጊዜ ደግሞ መቀሌ ላይ ነው፤ የማያውቁኝ ግን መልዕክት ላደርስላቸው የሄዱኳቸው እናት ናቸው። ” ወዲ” እያሉ ይጠሯቸዋል። ትልቅ ሰው ናቸው። እኚህን ሴት ከደቂቃዎች ቆይታ በኋላ ስለያቸው በጭራሽ መንገድ ሳላሳይሽ፣ ሳላሳፍርሽ ብለው እንዲሁ እየመረቁ ከአፋቸው እንደ ማር ጠብ በሚለው ንግግራቸው እያወሩና እያመሰገኑ ሸኙኝ። አሁን በቃ ተመለሱ ሲባሉ እንኳን ከፊታቸው እስክንጠፋ ድረስ መንገዱን ቆመው የሸኙን እናት ከአንደበታቸው የሚወጣውን ንግግር በውስጤ ቀርቷል ። አዎ መልካም ቃላት መድሀኒት ናቸው። ለታመመ ብቻ ሳይሆን ላልታመመ ብርታት ጥንካሬ ናቸው። ትዝታ በውስጥ ያስቀራሉ፤ ይናፍቃሉ። አንዳንዱ ደግሞ የሚያወጣው ቃላት ገና ከመነሻው ተናካሽ እንደሚባለው ይሆናል።
ከአንደበቱ የሚወጡት ቃላት፣ የሚናገርበትን ቦታ እንኳን የማይመርጥ፣ ከእነማን ጋር እየተነጋገረ እንደሆነ የማይረዳ፣ተምሬያለሁ ቢልም ያልተማረ ፤ አውቃለሁ ቢልም ማወቁን የሚገልጽበት ቃላት ከእውቀቱ ሰዎች እንዲጠቀሙ፣ እንዲያደምጡ የማያደረግ ይልቁንም አሰልቺ ይሆናል። አላዋቂነቱ ይበዛል። ለመስማት ብቻ ሳይሆን ለማየትም ተጠያፊው ይበዛል። እውነትም መልካም ቃላት ጣዕም አላቸው። ምነው በተናገረ/ በተናገረች የሚያስብሉ በቁም ነገርም በጨዋታም አዋዝተው የሚያስተምሩና የሚያዝናኑ አሉ።
ምነው ዛሬ ከእሱ / ከእርሷ ጋር በዋልኩ፤ አብሬ በሰራሁ የሚያስብሉ፤ የስራ ኃላፊ ሆነው እንኳን የኃላፊነት ስሜት እንዳይሰማ የሚያደርጉ ሰርተው የሚያሰሩ ብዙ ናቸው። እነዚህ ሰዎች እንግዲህ ይህንን የወረሱት ከቤተሰብ፣ ከአስተዳደግ፣ ከጓደኛ ሊሆን ይችላል። ጓደኛ እኮ ብዙ ነገሮችን ይቀይራል፤ ከነአባባሉስ ” ጓደኛህን ንገረኝና ማንነትህን እነግርሀለሁ” አይደል የሚባለው። ግን እኮ “መጥፎ ” ሰዎች መልካም ጓደኛ ይኖራቸዋል እንዴ? እስኪ ልጠይቅ ።
ስለዚህ እላለሁ በተቻለ መጠን ጥሩ ቃላቶችን እንለዋወጥ፤ መጥፎ ቃላት የሚያወጡትንም ኧረ አይባልም እያልን እንመልሳቸው። ሁላችንም በስራ ቦታ፣ በትምህርት ቤት፣ በትራንስፖርት ላይ፣ በሆስፒታል፣ በቤተ እምነቶች … ጥሩ ጥሩ የሰውን ሰብዕና የሚገነቡ መልካም ቃላትን እናውጣ።
አዲስ ዘመን ነሐሴ 19 / 2011
አልማዝ አያሌው