አከራዬ “ጤፍ ጨመረ፤ ኑሮ ተወደደ” ብለው የቤት ኪራይ ጨመሩብኝ።እኔ የተወደደውን ጤፍ የምበላ አይመስላቸውም መሰለኝ።አዎን! ከስቼ ሲያዩኝ ምግብ የተውኩ መስሉዋቸው ይሆናል።ኮስምኜ ሲመለከቱኝ የኑሮ ክብደት መለከያ ሚዛን መስያቸው ይሆናል።ለሳቸው የከበደው ኑሮ ለኔ የረከሰ ይመስላቸዋል መሰለኝ፤ ብቻ ኑሮ አጠውልጎኝ አንገቴን ሰብሬ ሲያዩኝ የኑሮ መወደድ ምክንያት እኔ መስያቸው ይሆን እንዴ ብዬ አስባለሁ።አከራዬ የኑሮን መወደድ በምን ሊያውቁት ይችላሉ።ምንያም ሱቅ ሄደው የ5 ብር ሻማ 6 ብር ሆነ ሲሏቸው የአራት ሺህ ቤታቸው “ከዛሬ ጀምሮ አምስት ሺህ ሆኗል፡፡” የሚሉት አከራዬ የኑሮ መወደድ ለሳቸው ጭማሪ እንጂ ኪሳራ እንዴት ሊሆን ይችላል።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግልምጫቸው ሲጨምርብኝ አጎንብሼ “ሰላም ዋሉ?” ስል ዝም በማለት ያልፉኝ የነበሩት አከራዬ ማልጎምጎም ሲጀምሩ ጭማሪ አስበው እደሆነ ሊገባኝ ይገባ ነበር።“ጨምሯል” የሚቀላቸው ተጨምሮብዎታል የሚነዳቸው አከራዬ የሚቀላቸውን ነገር ሲተገብሩ እኔም የቀለለ ቤት ፍለጋ በረፍቴ ቀን ማልጄ ወጥቼ አምሽቼ መግባት አዘውትሬያለሁ።ከስራ ወጥቼ ሌላ ኑሮ የሚያቀልል ቤት፤ ለመቆየት የሚበቃ ማረፊያ ለማግኘት ስማስን ረፍት አጥቻለሁ።
ውዶቼ የሰሞኑ ትርፍ ስራዬ ቤት መፈለግ ሆኗል።ይህ አጋጣሚ ብዙ ደላሎች ለማወቅ አጋጣሚ ሆነኝና በአዲስ አበባ የተለያዩ መንደሮች ውስጥ ያሉ ቤት አከራዮች አመልና በተለያየ መልኩ ለኪራይ ያዘጋጁዋቸው ቤታቸው በደላሎች አስጎብኚነት አዳረስኩ።ከውካዋ …..”ምንድ ነው?” ከውስጥ የአከራይ ቤተሰብ፤ “ተከራይ ይዤ መጥቻለሁ ክፈቱ….” ከውጭ እኔን ይዘው ይዞሩ የነበሩት ደላሎች ተደጋጋሚ የቃላት ልውውጥ የመሰንበቻዬ ማጀቢያ ሙዚቃዎች ሆነውኝ ከረሙ።
ቤት ለመከራየት ስዞር ስንቱን አከራይ ታዘብኩ! “ብቻህን ነህ?” “አዎን”፣ “ታመሻለህ?” “አይ” “ትቅማለህ? ታጨሳለህ?” “ኧረ ፈጥሞ”፤ “ብዙ ጓደኛ አለህ?” “አዎን …” የተለያዩ ጥያቄዎች ፤ብዙ አዎን፤ አንዳንዱ ደግሞ አይ የሚያሰኙ ይጠይቃሉ አከራዮች።አዎን እና አይ አስከትላው እኔ።ብቻ ብዙ የማይገባ ጥያቄና አሰልቺ ንግግር ይሰማል።ለመግባባት ስደርስ ሌላ ጥያቄ ያስከትላሉ።ይሄን ጥያቄ መሞገት ያምረኛል።ሰው ሆኖ ከሰው ጋር መኖር ክልክል ነው ባይን እሞግታለሁ።ሰው ሆኖ ሰውን አታቅርብ የሚልን እከሳለሁ።ለዚያውም ራቅ ብዬ።ታዲያ ነግሬያቸው ነው ’ማልፈው።“ሰው ወይም ጓደኞችህ ማምጣት አይቻልም ሲሉኝ” ተቃውሞዬን ማሰማት እጀምራለሁ፡፡
እኔ ምለው ተከራዮች ጓደኛ የሌላቸው ያህል የተከራይ ጓደኛ አጥብቀው የሚጠሉበት ምክንያት ምን ይሆን? ከሰው ጋር መኖር ክልክል ነው ማለት እንዴት ይቀላል? ትዳርን መስርቶ፤ ልጅ ወልዶ በደስታ ለመኖር እየታሰበ ለሌላው አያገባኝም በሚል “ለባለትዳርና ልጅ ላለው ቤት አላከራይም” እንዴት ይባላል? ትዳሩን የሚያስተዳድሩት እነርሱ፤ ልጁን የሚያሳድጉት እነርሱ፤ ቤተሰቡን የሚመግቡት እነርሱ ይመስል።ብቻውን የሚኖር፣ ሰው የማያምረው፣ የማይስቅ የማይጫወት፣ ማህበራዊ ህይወት የራቀና የጠላ ሊያደርጉን ቆርጠዋል አከራዮች፡፡
ውዶቼ አከራዮች ተከራይ በቤት ላይ እንደዜጋ መብት እንዳለው አስበን እናውቃለን።መሬቱ በምንም መለኪያ የሀገር ሀብት ነው።ያ ሀብት ደግሞ በአጋጣሚ ወይም በሆነ መንገድ የአከራዩ ሆኖ ተገኘ።ነገር ግን፤ ተከራዩ በሀገሩ ያለን ማንኛውም ሀብት በእኩል የማግኘት ኢኮኖሚያዊ መብቱ ነውና ቢያንስ በተከራይነት መብቱ ሳይነጠቅ በሰላም የመኖር ህጋዊ መብት ይኖረዋል።የኑሮ ጉዳይ የሰብዓዊ መብት ጉዳይም ነውና አከራይ የተከራይን ሰብዓዊ መብት የማክበር ህጋዊ ግዴታ አለበት።ተከራይም የአከራይ መብት መጠበቅ እንዳለበት ሳይዘነጋ፤ እናም ሰው ሆኖ “ሰው አትቅረብ ሰው አትጥራ” ማለት ተገቢነት የለውም።ያራዳ ልጆች እንዲህ አይነቱ ገጠመኝ ተገቢ ያለመሆኑን መንገር ሲፈልጉ ወይም ሲወርፉ “አይነፋም” ማለት ያዘወትራሉ።እናም ይሄ ተግባር ‘አይነፋም፡፡’
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በቅርቡ ባደረጉት የፓርላማ ንግግራቸው “የቤት ኪራይ ጉዳይ በጥናት እልባት ይበጅለታል፤” ማለታቸውን በሰማሁ ጌዜ ለተግባራዊነቱ ፍጥነት ጸሎት ጀምሬ ነበር።ምን ዋጋ አለው ጸሎቴ አልሰመረም መሰለኝ፤ የአጥኚዎቹን ድምፅ እስካሁን መስማት አልቻልኩም።እንደአከራይ ካልሆነ በቀር ተከራይ ሆኖ ይሄን የማይናፍቅ ይኖራል።የኪራይ ገደብ ተቀምጦ ህጋዊ የሆነ ምቹ ስርዓት ተዘርግቶ ተከራዮች መበዝበዛቸው ቢቆም ምን አለ።
የቤት አከራዮችና ደላሎች የሚስማሙበትን ያህል ተከራዮች ከደላሎች ጋር ቢስማሙ የቤት ኪራይ ዋጋ ከመጨመር ይልቅ በወረደ ነበር።አቤት የደላሎችና የአከራዮች ፍቅር፤ በነገራችን ላይ ውዴታቸው በጥቅም ላይ የተመሰረተ ነው።ደላላው አዳዲስ ተከራዮችን በማቅረብና ዋጋ ከፍ አድርጎ በመንገር የአከራይን ገቢ ማሳደግና አከራይ ደግሞ ተከራይን ቶሎ ቶሎ በመለዋወጥ የደላላውን ገቢ በማሳደግ የንግድ ስምምነት አድርገው እቅድ አውጥተው ተከራይን የመበዝበዝ ስራ በጋራ ለመስራት ቃል ኪዳን አስረዋል።
የቃላቸውን ያህል ታምነው የማይገኙት ደላሎችም ምግባርና ቃላቸው የተነጣጠለ፤ ተግባርና እውነታቸው የተራራቀ ሆኗል።ደላሎቹ ቤት ተጠይቀው ሲያወሩ ሲያስተዋውቁ ለጉድ ነው።የቤቱን ሁኔታ በአንደበታቸው ባለ ምርጥ ቃል ሁሉ አጣፍጠው ይናገራሉ።ቤቱ የተሰራው ከምርግ ጭቃ ሆኖ አስሩ ቦታ ተነድሎ እየታየ ሳለ በእምነበረድ ተገጥግጦ የተሰራ ነው።የተነደለው ደግሞ በባህሪው ቤቱ ስለሚሞቅ ለንፋስ መውጫ ሆን ተብሎ የተሰራ ነው፤ በአፈር የተደመደመ ወለል ልስልስ በሆነ ሲሚንቶ ተሰርቶ ነው እያሉ ሲተረተሩ የሚተረትሩትን እየሰሙ ከመታዘብ ውጪ ምን ሊባል ይችላል።እኔ ’ምለው ደላላና ውሸት እስከ መቼ ነው አብረው ተከባብረው ወዳጅ ሆነው የሚዘልቁት?
በነገራችን ላይ ውዶቼ፤ አሁን ላይ ያለው የኑሮ መወደድና የዋጋ ንረት ምክንያት ሸማቹን ከተጠቃሚ ጋር የሚያገናኙት ደላሎች ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ብዙ ማሳያዎችን መጥቀስ ይቻላል።የቤት ኪራይ ጉዳይ አይደል መነሻዬ? እሱን መሰረት አድርጌ አንድ ገጠመኜን ላንሳ። እዚሁ አዲስ አበባ ከተማ አራት ኪሎ አካባቢ የሚገኝ አንዱ ኮንዶሚኒየም ግቢ ቤት ጥየቃ ገብቼ ከደላሎቹ የተሰጠኝ ምላሽ ላስከትል።የሚከራይ ቤት መኖሩን የጠየኩት ደላላ መኖሩ ነገረኝ።የዋጋ ጥያቄ ሲያቀርብልኝ የምችለውን ነገርኩት።
ባልኩት ዋጋ አሁን ላይ የተያዘ ቤት መኖሩንና እኔ የተሻለ ዋጋ የምከፍል ከሆነ አሁን ያለው ተከራይ ከቤቱ ባለቤት ጋር በመነጋጋር ማስወጣት እንደሚችል ነገረኝ።የኔን የነገ እጣ አሰብኩት።እሺ ብዬ ተደራድሬው ብገባ ሌላ ከፍ ያለ ተከራይ ሲመጣ ልቀቅ የማልባልበት ምንም ምክንያት የሌለኝ ተገፍታሪ ነኝና መገፍተርን ጠላሁ።
ምቾት ፈልጎ የሰውን ሰላም መንፈግ፤ መደላደልን ተመኝቶ ድሎትን ከሰው ማራቅ አይከብድም!? የደላሎች ስራ ተጠቃሚን ከአገልግሎት ሰጪ ጋር አገናኝቶ ተገቢ በሆነ መልኩ ገቢ ማግኘት፤ በሰጡት ልክ መገልገል መሆን ሲገባው ተገቢ ያልሆነ ጥቅም መቃረም አግባብ አይደለም።አገልግሎት ሰጪው ከአገልግሎት ፈላጊው ጋር የሚያገናኝ መላ ሲፈጠር ደላላው ምን ይል ይሆን? አከራዩስ “ሰው አይረባህም፤ ብቻህን ከሆንክ፣ እየሳቅህ የማታወራ ከሆነ፤ ከሰው ጋር የማትኖር ከሆነ ግባ” ማለቱን ሰው ሲያስፈልገው ሰው ከየት ያስገኝለት ይሆን እንጃ? ምድር ለሁላችንም የኪራይ ቤት ናትና እርስ በርስ ሳንበዳደል እንለፍባት።ኪራያችን እስኪያበቃ ብንፋቀርባት ትሰፋናለች። አበቃሁ ቸር ያሰማን!
አዲስ ዘመን ነሀሴ 17/2011
ተገኝ ብሩ