የሰው የሕይወት ገጠመኞች እጅግ ብዙ ናቸው:: ከጥንት እስከ ዛሬ:: በየዘመኑ አስገራሚ አሳዛኝ ታሪኮች ይከሰታሉ:: ዳርቻ የላቸውም:: እንደገናም ሰው ይወለዳል:: ያድጋል፤ይኖራል፤ ይሞታል::በደስታም ኖሮ ይሁን በሀዘን ያልፋል:: ዘመን ያደመቃቸው ዘመን ያከሰማቸው:: በእጅጉ ውስጥን ይመስጣሉ:: ብዙ ቦታዎች ተዘዋውሮ የሰራ የብዙ ሙያዎች ባለቤት የነበረ ጎልማሳ የሕይወቱ መስመር እንደተዛባ ይረዳና በስፋት የሚታወቅበትን ቦታ ለቆ ይጠፋል::
በእጁ ላይ ለነገ ብሎ ያስቀመጣት ምንም አልነበረውም:: የስራው ባህርይ ሀገር አቋራጭና ተንከራታች ቆላና ደጋ ሰሜንና ደቡብ ምስራቅና ምዕራብ የሚያዞር እንዲያም ሲል ከሞት ጋር ተጋፍጦ ከቀናው ተርፎ የሚመለስበት ስለነበር ለእሱ ስለነገ ማሰብ ብሎ ነገር አልነበረም:: ነገ ሌላ ቀን ነው:: መሽቶ ሲነጋ ጨለማው ገፎ ወለል ሲል ይታሰብበታል ባይ ነበር::
ዘርፈ ብዙ ሙያው የትም ቢሄድ ጾም እንደማያሳድረው ጠንቅቆ ያውቃል:: በእድሜ ዘመኑ ያካበተው እውቀት ትምህርትና ልምድ የትም ሆነ የት የሚመነዘር ጥሬ ገንዘብ ነበር:: በባሕርይው ተወዳጅ ሰው አክባሪ አብሮነትን የሚወድ ጨዋታ አዋቂ:: ሀረር ሸንኮር የሚባል አካባቢ ተወልዶ አድጎ በንጉሱ ዘመን መጨረሻ ሠራዊቱ ቤት በልጅነቱ ገብቶ ልዩ ሙያዎችን ቀስሟል:: ድፍን ኢትዮጵያን አካሏል:: በሙያው አንድ ሰው ሊያገኘው ወይንም ሊሆነው የማይችለውን መሆን የቻለም ነበር:: የተማራቸው ሰፊ ሙያዎች ድንቅ ድንቅ የሚሰኙ::
ፈሪሀ እግዚአብሄር ሲበዛ የነገሰበት በሰራው ብቻ መኖር የሚፈልግ ያለውን በትኖና አካፍሎ መኖር የሚወድ ሰው ታውቅ እንደሁ ጎልማሳው እንደሱ ነበር:: በእጁ ትንሽም ሳንቲም ብትሆን ያለው ‹‹ራበን ታረዝን›› ለሚሉ ሁሉ በትኖ ወደደሳሳው ጎጆው የሚመለስ ብቻውን የሚኖር ሰው:: ድሮ ድሮ ጎረምሳ እያለ አንድ ወንድና ሴት ልጅ ሀረር ላይ እንደነበሩት የሚናገሩ አሉ:: በሶማሌ ጦርነት ተለያይተው ልጆቹን ሳይገናኝ ሳያውቃቸው እስከመጨረሻው ኖረ:: ይሄኔ እኮ መንገድም ተላልፈው ይሆናል:: ወይ በጉርብትና ኖረው አሊያም አብረው ሰርተው ሊሆን ይችላል:: ካልተዋወቁ አልተዋወቁም ::
ጎልማሳው በአንድ አጋጣሚ የትላንቱን ሕይወቱን እርግፍ አድርጎ ጥሎ የከተማ ልጅነቱን በልቡ ሸሽጎ መዲናዋን አዲስ አበባን ዳግም አልመለስብሽም ብሎ በመኪና ሳይሆን በእግሩ እየተጓዘ ለቋት ወጣ:: በእግር መጓዙን የኖረበት ነው:: ሱሉልታን ጫንጮን አልፎ ገሰገሰ:: እግሩ በመራው ሄደ እንጂ ወደዚያ ስፍራ ጓደኛ ዘመድ የሚያውቀው ሰው አልነበረውም:: እንዲያ እያለ ደብረ ጽጌ ደረሰ:: የጽጌዎች ደብር::
እሱም ሀገሩን ሀገሩም እሱን አያውቀውም:: ትንሽ ደካማ ቤት ፈልጎ ተከራይቶ አነስተኛ ምግብ ቤቶችን ፈልጎ እየተመገበ ያገኘውን እየሰራ ዳግም እንደገና መኖር ጀመረ:: ባህሪው በውስጡ የተካነው ሙያና እውቀት በአጭር ጊዜ ብዙ ወዳጅ ጓደኛ ተከታይ አፈራለት:: እውቀት ለዘለአለም ይኑር::
ጎልማሳው እኔ ነኝ ያለ መካኒክ ሾፌር፤ የቅርጻ ቅርስ ባለሙያ፤ የንድፍ ሰራተኛ፤ ቤት ቀያሽ መሀንዲስ፤ መሆኑን በአጭር ጊዜ የከተማው ነዋሪ ተረዳ:: አከበረው:: ወደደውም:: ይህም ሁኖ ሌሎች ድንቅ ሙያዎች ነበሩት:: በፍጹም አይናገርም:: ያገኘውን ስራ ሰራ:: ያገኘውን ገንዘብ እዛው ከወጣቶች ጋር ይካፈላል:: ቤት ኪራዩን ይከፍላል:: ማታ ሲሆን የከተማው ወጣት ያጅበዋል:: አብሮት ያመሻል:: መጨረሻ ወደተከራያት ጎጆ አድርሰውት ይመለሳሉ:: እንዲህ ነበር የሚኖረው::
ጠዋት ማልደው ይቀሰቅሱትና ወደቀጣይ ስራቸው ይሄዳሉ:: ስለትላንት ህይወቱ እንዲህ ነበርኩ እንዲያ ነኝ የሚል ወሬ ከአፉ አይወጣም:: ስንትና ስንቱን ሕይወት አሳልፎታል መሰለህ:: በል ሲለው ደብረሊባኖስ ገዳም ሄዶ ይከርማል:: ደብረ ጽጌን እትብቱ የተቀበረባት ያህል ወደዳት:: ከልቡም አፈቀራት:: የሕዝቡ አብሮነት ፍቅር መተሳሰብ መከባባር አብሮ እንብላ እንጠጣ ባይነት በደስታና በሀዘን አለመለያየት ባሕሉን ወዳድነት ምርኮኛ አደረገው::
ሁሉን እርግፍ አድርጎ ጥሎ ከአዲስ አበባ የተሰደደበት ዋነኛ ምክንያት ውስጡ በሀዘን በመሰበሩ ምክንያት መሆኑን አንዳንዴ ብቻ ይናገራል:: እንዴትና ለምን የሚለውን አያነሳም:: በቀድሞው የስራ ሕይወቱ በሙያው በችሎታው በድንቅ ክህሎቱ በጥቂቶች ሳይሆን በብዙ ሺሕ ሰዎች ይታወቅ ይከበርም የነበረ ነው:: በድንገት የመሰወሩና የት እንደገባ ያለመታወቁ ጉዳይ ብዙዎችን ሲያስጨንቅ ኖሯል:: ድፍን አዲስ አበባ፤ ሀረር፤ ደብረዘይት፤ ሻሸመኔ፤ ሀዋሳ፤ ወሎ፤ ጅጅጋ አፋር ድረስ ሌሎችም ቦታዎች ያዩት የት እንደሆነ የሰሙ ካሉ በሚል ሲታሰስ የነበረ ቢሆንም ምንም ፍንጭ ሳይገኝ ኖሯል::
አንድ ቀን ደብረጽጌ ከተማዋ ውስጥ በምትገኝ ትንሽ ጎሚስታና ጋራዥ ሶስት ከአባይ ማዶ አቅጣጫ እየተምዘገዘጉ የሚበሩ ላንድክሩዘሮች የተለያዩ ሰዎችን እንደጫኑ መጥተው ጎማ ለማስሞላት ይቆማሉ:: ጎልማሳው በዙሪያው አምስት የሚሆኑ የከተማዋ ወጣቶች ከበውት የተበላሸች መኪና ፈታቶ ለመግጠም እየሰራ ነው:: ከላንድክሩዘሮቹ የወረዱት ሰዎች በዝግታ እየተሰራች ወዳለችው መኪና ተጠጉና ጎማ ለመቀየርና የመንተፋተፍ ችግር ያለበትን መኪና ባለሙያ ካለ እንዲያይልን ነው ሲሉ ጉዳዩ ቀልቡን የሳበው ጎልማሳ በድንገት ቀና ብሎ ‹‹አቤት ምን ነበር›› ሲል ከሶስቱም ሰዎች ጋር አይን ለአይን ተገጣጠሙ::
ጠንቅቀው ያውቁታል:: ውድ ሙያ አሰልጥኗቸዋል:: አስተምሯቸዋል:: ኩሩ ቆፍጣና ስነስርአት አክባሪና አስከባሪ የብዙ እውቀት ጌታ የሆነ አለቃቸው ነበር:: ጊዜ ገፍቶትና ከፍቶት ከመሰወሩ በፊት:: ረዥም አመታት እንደጠፋ ተፈልጎ ተፈልጎ ፍንጭ አለመገኘቱን ጭምር ያውቃሉ:: እናም ሰዎቹ እራሳቸውን ይዘው ጮሁ:: አምስቱ ወጣቶች ደንግጠው ምን ተፈጠረ በሚል መንፈስ ባሉበት ቆመው ቀጣዩን ክስተት መከታተል መረጡ::
ሻምበል፤ ሻምበል፤ ሻምበል ብለው ተጠመ ጠሙበት:: አቅፈው እየሳሙትም አልበቃቸው አለ:: መልሶ መላልሶ እያቀፈ ሳማቸው:: አይኖቹ በማያቋርጥ እምባ ታጠቡ:: ብዙ ፈተናና ውጣ ውረዶችን አብረው አሳልፈዋል:: እዛው እንደቆሙ መኪናዎቻቸውን ሰራርቶ ጨረሰ:: ጎማዎቹን አስሞላ:: ገንዘብ አውጥተው ቢሰጡትም እምቢኝ አለ:: ባዶ ኪሱን ለይሉኝታ ብሎ የሚግደረደር ሰው ታውቃለህ አይደል? ይሄ ድርጅት የአንተ ነው ሲሉ ጠየቁት:: አይደለም ሰውየው አያውቀኝም:: ለሙከራ ብሎ ነው የገባሁት ሁለት ቀኔ ነው አላቸው::
ወጣቶቹ አሁንም ይሰማሉ አጠገቡ አሉ:: አይ ግዜ አይ አለመተዋወቅ እስቲ ጥሩት ባለቤቱን አሉ:: ተጠርቶ መጣ:: እሞክራለሁ ስላለ እንጂ ሰውየውን አላውቀውም አላቸው:: ከት ብለው ሳቁ:: አንተ ልክ ነህ:: አታውቃቸውም:: እኛ ደግሞ በሚገባ እናውቃቸዋለን:: ለዛሬ ደረጃ አስተምረው አሰልጥነው ያበቁን ሰው ናቸው አሉ:: ጎልማሳው ትንፍሽ አላለም:: በግድ በግድ የተጠቀለሉ መቶዎች በኪሱ ሸጉጠው ነገ እንመጣለን የትም እንዳትሄድ ብለው መኪናቸውን አስነስተው ተፈተለኩ::
ሶስቱም ከፍተኛ ሹማምንት ነበሩ:: የዛኑ እለት ወጣቶቹ የሰሙትንና ያዩትን ሁሉ ለትንሽዋ ከተማ ነዋሪ የጥሩምባ ያህል አዳረሱ:: ሰውየው ለሀገር ብዙ ያገለገሉ የተከበሩ ሻምበል ናቸው:: ከእንግዲህ እያንዳንድሽ በማዕረጋቸው ነው መጥራት ያለባችሁ ተብሎ አዋጅ ተነገረ:: ባለላንድ ክሩዘሮቹ አዲስ አበባ እንደገቡ አስራ ስድስት አመት ጠፍቶ ተሰውሮ የኖረው ተወዳጁ ሰው ደብረጽጌ ላይ መገኘቱን ለብዙዎች አበሰሩ::
በራሪ ነብሮቹ ከያሉበት እየሄዱ አገኙት:: እንውሰድህ ቢሉትም ከእንግዲህ የእኔ ወገን የክፉና የችግሬ ቀን ደራሽ የሀዘኔ ማስረሻ ሰው አክባሪውና ወዳጁ የደብረጽጌ ሕዝብ ስለሆነ ብሞትም የሚቀብሩኝ እነሱ ናቸው የትም አልሄድም አለ:: አንድ ቀን የተከራያት ትንሽ ቤት ውስጥ ሊያዩት ሄዱ:: የሬሳ ሳጥን ገዝቶ ሸፍኖ አስቀምጦታል:: ይሄ እንጨት ምንድነው ብሎ አንዱ ጣል ያረገበትን ጨርቅ አወረደው:: ምነው አሉት:: ምንድነው ምነው ማለት ሕዝብ ማስቸገር የለብኝም:: ብሞት በዚሁ እንዲቀብሩኝ ነው የሚል መልስ ሰጠ:: አንደኛው ጓደኛው ተሸክሞ አውጥቶ ሰባበረው:: የሚገርመው ብዙም ሳይቆይ አለፈ:: በስልክ ሁሉም ከያለበት ተጠራርቶ መኪናውን እየስጓራ ወደ ደብረጽጌ ተፈተለከ:: ድንኳን ጥሎ የተቀመጠው ጎረቤቱና ሕዝቡ ነው:: ሚስት ድስት አልነበረውም::
ቀብሩ ካበቃ በኋላ ራሱን ዝቅ አድርጎና ደብቆ 16 አመታት በኖረበት ብዙም የኋላ ታሪኩንና ማንነቱን በቅጡ ለማያውቁት የአካባቢው ነዋሪዎች የጎልማሳው የሕይወት ታሪክ ተነበበ:: በንጉሱ ዘመን የነበረው ስፔሻል ፎርስ አባልና ልዩ ኮማንዶ፤ መኮንን ከሆነ በኋላ የኢትዮጵያ አየር ወለድ አባልና የኮማንዶ አሰልጣኝ፤ የዘመቻ መኮንን፤ የንድፍና የቅርጻ ቅርጽ ባለሙያ፤ ሾፌር መካኒክ፤ ከሶማሊያ ጦርነት እስከ ኤርትራ ብዙ በረሀዎች ያሳለፈ ብቸኝነትን መርጦ ኖሮ ያለፈ ሰው መሆኑ ተነገረ:: ዳግም እሪታ ጩሀት አንጀት የሚያላውስ ለቅሶ በቀብሩ ዙሪያ ባለው ጫካ ደጋግሞ አስተጋባ:: ሞልቶት ዘለቀ:: ሞልቶም ፈሰሰ::
አዲስ ዘመን ነሀሴ 16/2011
ወንድወሰን መኮንን