አንድ ደንብ ሊወጣ ታስቦ ረቂቁ ለውይይት መቅረቡን ሰማሁ፤ በጎዳና ላይ ማደርንና መለመንን የሚከለክል። ሀሳቡ መልካም ነው፤ ግን ውዶቼ አንድ ነገር አሰብኩና ፈራሁ። ምን ፈራህ ካላችሁኝ ክልከላው ራሱ ክልክል እንዳይሆን፤ ቆዩኝማ ወዳጆቼ፤ ልክ አሁን ሊወጣ እንደታሰበው የልመና ክልከላ ደንብ በአለም አቀፍ ደረጃ ተተግብሮ በየትኛውም ሀገር ልመና አይፈቀድለትም፤ ልመና በአለም አቀፍ ህግ ወንጀል ነው ቢባል ምን ይውጠናል? የእውነት ያስፈራል ለዓመታዊ በጀታችን እንኳን ሳይቀር እቅድ የምንይዘው ገና ለምነን እናገኘዋለን ከምንለው ብድርና ርዳታ እናገኛለን ብለን ያሰበነውን ጨምረን ነው፡፡
አዎ ሀገርን ከልመና ለማውጣት መጣር በራሳችን እንድንቆም መጠንከር ይገባል። ከዚህ አስፈሪ እሳቤ ለመውጣት እንደሀገር ቆራጥ ሆነን መትጋት፤ ለለውጥ መታተር ይጠበቅብናል። እንደ ግለሰብ የከለከልነውን ልመና እንደሀገር ብንከለከል የት ይሆን መድረሻችን ብለን እናስብ! በነገራችን ላይ፤ ሀገር ስትለምን ነው ለግለሰብ የሚያሳፍረው፤ አይደል? አዎን! ሀገር ስትሰጥ እንጂ ስትቀበል ያሳፍራል። መቀበል የምታዘወትር ሀገር ደግሞ ሰጪ ትውልድ ማፍራት ይከብዳታል፡፡
ስለዚህ ጎበዝ ታጥቀን እንነሳ፤ ሀገራችንን ሰጪ ለማድረግ ትውልዱንም ከልመና ለመታደግ። ዛሬ የጎዳና ላይ አዳርና ልመና በህግ ከልክለን ብናስቆም ጎዳና የወጣው ረሀብና እርዛት ወደ ጓዳ እንዲደበቅ ከማድረግ የዘለለ ለውጥ አይኖረውም፡፡መደበቁ ይበልጥ ቢያባብሰው ድህነታችንን ይበልጥ ቢያከፋው እንጂ መፍትሄ አይሆን ነገር። ደግሞስ ከተሸሸገ ችግር ይፋ የወጣ ይሻላል።
ለምን ልመናና የጎዳና ህይወት ሊከለከል ታሰበ አልልም። ምክንያቱም ሀሳቡ በጎነቱ ያመዝናል። ግን ልመናን ባመጣውና ወደ ጎዳና ባስወጣው ችግር ላይ ቀድመን ብንዘምት ውጤቱ ያምራል ባይ ነኝ። ልመና እኮ የሚወድድ አንድም ወገን የለም። ልመናን ሳይወድ እንዲኖርበት የተገደደ እንጂ፤ ተርቦ፣ ታርዞና ተጠምቶ እቤቱ ተቆራምዶ ከመሞት የወገኑን እጅ ለማየት ይገደዳል። የኑሮ ሸክሙ ቢከብደው፤ ጫናው ቢያንገዳግደው አማራጭ አጥቶ ጎዳና ይወጣል ፡፡
ወደጎዳና ያወጣውን ችግር፤ የሰው ፊት የሚያስገርፈውን ማጣት ለማጥፋት መጣሩ ከሁሉ ቀዳሚ ቢሆን ክልከላውም ማረፊያ ይኖረዋል። የሰውን ማህበራዊ ችግር ለመፍታት መጣሩ ቢቀድም መልካም ነበር። ዛሬ ማደሪያ አጥቶ ጎዳና ለመኖሩ፤ ዛሬ የሚቀምሰው አጥቶ ተመፅዋች የመሆኑ ምክንያት ሊከለከል ከታሰበው ቀድሞ ካልተወገደ ክልከላው ውጤቱ አይታየኝም፡፡
በእርግጥ የተቀናጀ ስራ ቀድሞ ቢሆንና እነዚህ ለማህበራዊ ቀውስ የተዳረጉ ወገኖች የሚደገፉበት የተለየ ሁኔታ ቢመቻችና ስራውም ስኬታማ ቢሆን ክልከላው ምንኛ ደስ ባለ ነበር። እዚህ ላይ እየተሰሩ ያሉ ስራዎች ገና ጅምር በሆኑበት ደረጃ የኑሮ ሁኔታ መጨረሻ ባስገኘው ወገን ላይ ኑሮ በከበደውና የመጨረሻ እርከን ላይ ባስገኘው ዜጋ ክልከላን ማሰብ ይከብዳል።
አዲስ አበባ ላይ እኮ የሚከለከሉ መዓት ጉዶች አሉ። ርቦት “ወንድም ዳቦ ግዛልኝ” ከሚለው የኔ ቢጤ ከመከልከል በፊት ሳንፈልግ በየጎዳናና መዝናኛው ሲጋራ አጢሶ እኛን የሚያስጤሰንን መከልከል አይቀልም። ማደሪያ አጥቶ ጎዳና የወጣን መግቢያ ሳይኖረው ግባ ብሎ ከማስገደድ፤ ቤቱ የኔ ነው የፈለኩትን ያህል የቤት ኪራይ እቆልልብሀለሁ የሚል ዘመነኛን ማስቆም አይቀድምም?
ቀድመን ሀገር ከልመና ለማውጣት መስራት ከተረጂነት ለማላቀቅ መጣር ይገባናል። ያኔ ለማኙን ለመፈለግ እንኳን ይከብዳል። ለማኙን አትለምን ከማለት ባለፈ የልመና ትርጓሜ እስከመርሳት የሚያደርስ ገጠመኝ መፍጠርም ይቀላል።
ግን ደግሞ እንደ ሀገር ቆመን በየአደባባዩ እየለምንን እንደ ግለሰብ አትለምንም ማለት አይከብድም። ትልቁ ግለሰብ ነው ሀገር። ገዝፎ ከመለመን አንሶ ከመመፅወት የተሻለ ክብር አለው እንዴ? የሀገር ልምና ፅድቅ ግለሰብ ቸግሮት ሲለምን ኩነኔ ነው። እኔ ምለው የማይለምን ሰው ግን አለ። የአለማምን ስልቱ ይለያይ እንጂ ልመና ሁላችንም ዘንድ አለ እኮ፤
የሚገባንን በትክክል እና በተገቢው መንገድ ከመጠየቅ ልምናን የምናስቀድም፤ ለመገልገል ሄደን አገልጋይ ይመስል ለግልጋሎቱ ልመና የምናስቀድም፤ በስራችና ሳይሆን በልመናችን ትርፍ ማግኘት የምናዘወትር ብዙ ነን። አዎ አለማመናችንና የልመና ስልታችን ይለያያል እንጂ ሁላችንም በተለያየ መልኩ ከልመና አልወጣንም፡፡
አንድ ወቅት ላይ የአሁኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አንድ ጥያቄ አቅራቢ እንዲህ ስትላቸው ትዝ ይለኛል። ለነገሩ የልጅቷ ንግግር አስተያየት አይሉት ጉራ ቢጤ የተቀላቀለበት ውስጥ ያለን ለማውጣት፤ ስሜትን ለመግለፅ የሚያደርጉት አይነት ነበር። እናም እንዲህ አለች። “እኛ አካባቢ አንድም ለማኝ የለም… አሁን እየለመኑ ያሉት ከሌላ አካባቢ የመጡ ለማኞች ናቸው… እኛ ፈፅሞ በልመና ላይ የተሰማራ አባል የለንም…” የልጅቷ ያልተገራ ሀሳብ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ምላሽ ቦታውን አገኘ።
ምሳሌዎች ቀረቡላት፤ ራስዋን ያለቻለች በብዙ ልመና ውስጥ መሆንዋን በማሳያ አሳዩኣት። የእውነት መልስ እንዲህ ጣፍጦ ከጥያቄ በላይ ሲመለስ ደስ ይላል። ለልጅቷ የተሰጣት መልስ ለማኝ አይደለንም ማለት ስለ ነገሩ ያላት እውቀት አነስተኛ መሆንን አመላካች ነበር።
እንደ ሀገር ካልተለወጥን እንደ ህዝብ እራሳችን ካልቻልን በቀር የምንለካው በራሳችን ልክ ነው። አሁን ባለንበት ዓመታዊ በጀቷን ብድርን ታሳቢ አድርጋ ከምትበጅት ሀገር የሚጠበቅ ልኬት ልክ፤ እና ውዶቼ ሁላችንም ራሳችንን የቻልን የበቃን አይደለንም። በቅጡና እጅ ለእጅ ከተያያዝን ለራሳችን መብቃት አይደለም ለሌላም መትረፍ የምንችል መሆናችን አይካድም፡፡
እና የጎዳና ላይ ልመናና አዳር ሊከለከል መታሰቡ ደስ ቢያሰኘኝም ከሱ በፊት መቅደም ያለባቸው ብዙ ጉዳዮች መተዋቸው ግን አተያዬን ለውጦብኛል። እኔ ’ምለው ደንቡ ተግባራዊ ሆኖ ቢተገበርና በልመና ላይ የተሰማራ ሰው ቢያዝ የያዘውን ሰው ልቀቀኝ ብሎ መለመኑ እኮ አይቀርም፤ እናም ልመናው በድጋሚ ወንጀል ያስጠይቀው ይሆን?
ቀድሞ የሚከለከል ስንት ነገር በበዛበት ሀገር ልመናን አስቀድሞ መከልከል ችኮላ አይደል በሞቴ። መከልከልስ የሰውን ሀቅ እየቀሙ የራሳቸውን ኪስ የሚሞሉትን፣ መከልከልስ በህዝብ ሀብት ከብረው የሌላ እድል የዘጉትን፣ መከልከልስ ህግ ጥሰው፤ በህግ አምላክን ደፍጥጠው እንዳሻቸው የሚሆኑትን ነው። አዎን ቀድሞ መከልከል እነርሱን ነው። እነርሱ ስርዓት ሲይዙ፤ ስርዓት አልበኝነት ሲጠፋ ሁሉም ነገር ስርዓቱን ይይዛል፤ ሁሉም ነገር ቦታው ላይ ይደላደላል።
በነገራችን ላይ፤ ህገ ወጥ ተግባር እያደር ይለመድና የተፈቀደ ይመስላል። ለምሳሌ፤ የታክሲ ረዳቶች በብዙ መልክ የሚያስለምዱንን ህገ ወጥ ተግባር የተላመድነው አንድ ገጠመኝ ላንሳ። ታክሲ ላይ ከሚለጣጠፍ ጥቅስ በቀር የሚያስደስት ምን አለ? ብዬ ብጠይቅ ወዳጆቼ የምትማረሩበት ነገር ስለሚበዛ የአብዛኞቻችሁ መልስ “አዎን” የሚል ይመስለኛል።
ስነ ምግባር ፈፅሞ የራቃቸው፤ በአገልግሎት አሰጣጣቸው ህዝብን ያማረሩ፤ የሚሳደቡ፤ ተገቢ ያልሆነ ታሪፍ የሚጠይቁ፤ ብቻ ትንሽ አገልግሎት ሰጥተው ብዙ የሚያበሳጩ ናቸው ታክሲዎች፤ የራሳቸውን ደንብ እያወጡ፤ የራሳቸውን ህግ እየደነገጉ ጠዋት ማታ ወደ ስራ ስንሄድና ከስራ ስንመለስ የምንገለገልባቸው ታክሲዎች በህጋቸው ይገዙናል። ባስለመዱን ስህትት ውስጥ ራሳችንን ተሳታፊ አድርገው፤ አልፈውም ለነሱ ተሟጋች ያደርጉናል፡፡
ለምሳሌ፤ አሁን ላይ እኛን አክብረው ይሆን ንቀውን፤ ሀምሳ ሳንቲምን ደግሞ ንቀዋት ይሆን ወደዋት መመለስ ትተዋል። ጎበዝ የታክሲ ረዳቶች ግን ትልቅ ናችሁ ማለት አላበዙትም። ታላቅነታችን ለመመስከር ቆርጠው መልስ ከመስጠት እየተቆጠቡ ነው። ለትልቅ ሰው መልስ አይሰጥም የሚለውን ፍልስፍና በትክክል ተግብረውታል። የአንድ ብር ከሃምሳውን ታሪፍ በራሳቸው ፍቃድ ሁለት ብር አድርገውታል።
ሁለት ብር የሰጠ ሃምሳ ሳንቲም ሲመለስለት ማየት ይናፍቀዋል። ረዳቶቹ የማይጠየቁበት ህጋዊ ሌብነት ውስጥ እኮ ነው ያሉት፤ ተጠረቃቅሞ ምን ያህል እንደሚደርስ ታውቃላችሁ ውዶቼ? ተዘርፈናል ኡኡኡ እንዳትሉ ደግሞ፤ በትንሽ ትልቁ ኡኡታን የለመደ ህዝብ ምክንያታችሁን ሳጠይቅ አብሯችሁ ጮሆ ደግሞ አታስረብሹን። ለማንኛውም አንድ ታክሲ ከአንድ ሰው ላይ የሚያስቀረው ሀምሳ ሳንቲም ከአንድ ጎዞው ከ12 ሰው 6 ብር፤ ቀኑ ሙሉ ከሚጓጓዘው ደግሞ በግምት ተምኑት ይሄ ሁሉ ተሰልቶ የሚገኘው ገንዘብ የህግ አግባብ ያለው ይመስል ወድደንና ፈቅደን የምናቀርብለት ነው። ፈቅደን ለምደን የምናስረክበው ነው።
ቀን ላይ ሃምሳ… ሳንቲም መመለስ ትተዋል። ትልቅ ናችሁ ብለው እኮ ነው መልስ የሚከለክሉን፤ ስንቱ ነገር የጎደለን መሆኑን ያልተረዱ ግፈኞች ናቸው። ቀን ላይ ሃምሳ፤ ሃምሳ ሳንቲም እየነጠቁን ይውሉና ማታ ላይ ህግ የሌለ በሚመስል መልኩ የ3 ብሩን መንገድ ደረታቸውን ነፍተው አደባባይ ላይ አስር ብር ነው ከከፈልክ ብቻ ግባ ካልቻልክ ውረድ በማለት ያዝዛሉ። አዎን እነዚህን መከልከል ይቀድም ነበር፤ መከልከል ብዙ የተከለከለን ነገር ተዳፍረው የተገባንን ነገር የሚነጥቁንን ነበር።
እናም ጎበዝ ለመከልከል ያሰብናቸው ነገሮች የቅደም ተከተል ችግር አይታያችሁም? የሚከለከለው የተፈቀደ ያህል ተትቶ ለመከልከል ብዙ የሚቀረውን ወይም የማይቻለውን መከልከል አልበዛም? ለኔ በዝቶ ይታየኛል። ሀገርን በትጋት ከልመና ማውጣት ራስዋን እንድትችል ማድረግ የግለሰብን ልመና ያጠፋል። አዎን፤ ይከልከል ግን ከዛኛው ክልከላ ይሄኛው ይቅደም። ወይም ቋሚ መፍትሄ ለሁላችንም መቆም ይበጃል። ቸር እንሰንብት፡፡
አዲስ ዘመን ነሀሴ 10/2011
ተገኝ ብሩ (ሻሚል)