አንድ በግዜው በጉርምስና ወራቱ የነበረ ወጣት ከገጠር ወላጆቹ ቤት እንደወጣ በዛው ጠፍቶ ይቀራል። በሀገራችን ሰሜን ክፍል የሆነ እውነት ነው። በፍለጋ ሀገር ታመሰ። እናት በነጋ በጠባ አባት ወንድምና እህቶች ዘመድ አዝማዱ ማስኖ ማስኖ ሩቅም እያላላከ ቢያስፈልግ ያንን ልጅ በዚህ ግድም አየሁ የሚል ጠፋ። ብርቱው ገበሬ አባትም አለፉ። ዘመኑ ገሰገሰና ታሪክ መሰለ።
እንደ ዋዛ ሀያ አመታት ነጎዱ። እናት አርጅተው ከዘራ ይዘው እህትም እናቴን ለማን ጥዬ እሄዳለሁ ብላ አብረው በገጠሩ ደሳሳ ጎጇቸው ወንዶቹም አግብተው ወልደው ራቅ ብለው ይኖራሉ። እየመጡ ይጠይቃሉ። አንድ ቀን አሮጊት እናትና ልጅ በራፋቸው ላይ ቁጭ ብለው እያወጉ ጸሀይ ይሞቃሉ። አርጅተውም በጉልምስናው ከቤቱ ወጥቶ በቀረው ልጃቸው እጣ ፈንታ ሁሌም የሚብሰከሰኩት እናት የዚያ የጠፋ ልጃቸውን ጉዳይ አንስተው ከሴቷ ልጃቸው ጋር ያወጋሉ።
መቼም በሕይወት ቢኖር በእናቱ አይጨክንም ነበር እያሉ። ‹‹እማመይ›› አለች ሴት ልጃቸው አቤት አሉ እናት። እስቲ ተይው ዘመኑም ከ20 አመታት በላይ ሄደ። አጠገባችን ቢኖር፤አግብቶ ይወልድ ነበር። አልሆነም። ተይው መንኖ ይሆናል፤ አገልግሎቱ ለሰው ሳይሆን ለፈጣሪ ቢሆንስ አለቻቸው። እናት ሆድ ሆዳቸውን ቢበላቸውም ዝምታን መረጡ።
ከፊት ለፊታቸው ሶስት ቆዳ የለበሱ አግድም ዳዊታቸውን የታጠቁ ፤ጸጉራቸው ተገምዶ ተገምዶ ወደ ኋላ ጀርባቸው ላይ የተኛ፤ጺማቸው የተንዠረገገ፤ በቀኝ እጃቸው ቀጭን አናቱ ላይ የመስቀል ምልክት ያለው የብረት ዘንግ የያዙ፤ በባዶ እግራቸው የሚራመዱ ባሕታውያን ወደቤታቸው ደጃፍ እየቀረቡ መጡ።
እናትና ልጅ ከተቀመጡበት ብድግ ብለው ቆሙ። ‹‹እናታችን፤ ምነው ምነው አይገባም፤ አይገባም በማርያም በማርያም ይቀመጡ›› ቢሏቸውም በጀ አላሉም። ከሩቅ ገዳም ነው አራት ቀን ተጉዘን እዚህ የደረስነው ወደ ሌላ ገዳም ልንሄድ። እዚችው በራፍ ስር አረፍ ብለን ውለን ማልደን እንነሳለን አሉ ባህታውያኑ። ቤት ግቡ ቢባሉ አልገቡም።
ጀንዲ (ቁርበት) ከቤቱ በራፍ ተነጠፈላቸው። ሴቷ ልጅ እግራቸውን ተራ በተራ አጠበች። ተመረቀችም። የሚቀምሱትም ቀረበላቸው። እርጅና የተጫጫናቸው እናት ገና ለጋ ወጣት እያለ ከቤታቸው ወጥቶ ስለቀረውና ከ20 አመታት በላይ ስለጠፋው ልጃቸው በእናታዊ ስስት ናፍቆትና ሰቀቀን ተውጠው ለሶስቱ ባሕታውያውን አጫወቷቸው። በዚያ የገጠር መንገድ ወደዚያችም ጎጆ የገጠር ቤትና መንደር የመጡትን ባሕታውያን እየመራ ያመጣቸው አንደኛው ባሕታዊ ድሮ ድሮ ቤቱንም ሰዎቹንም ያውቃቸዋል።
ዛሬ ማንም ሰው መንደሩም ቢሰበሰብ በፍጹም እሱን ሊያውቀው አይችልም። እናቱንም እህቱንም ለይቷቸዋል። እነሱ ግን አላወቁትም። ሁለቱ ባሕታውያንም ይሄን ምስጢር አያውቁም። አግድም ብቻ ሰረቅ እያደረገ አንዴ እናቱን አንዴ እህቱን ያያል። እንዲህ ነው እንዲያ የሚል ወግ የለም። አለምን ሲክዱ በቃኝ ሲሉ እንዲህ ነዋ። የትላንት ማንነትም አብሮ ይሰረዛል።ይጠፋል።
መሽቶ እናትና ልጅ ጎጇቸው ገብተው ባህታውያኑም በራፉ ላይ ጸሎት እያደረሱ እስኪነጋጋ ቆዩና ማልደው ተነስተው በየት ሳይባል እብስ አሉ። እናት ሌሊት ሕልም አዩ። ከሶስቱ ባሕታውያን አንዱ ዘለግ ያለው ጠፋ የምትይው ልጅሽ እኔ ነኝ። አልሞትኩም። የተመረጥኩት ለእግዚአብሄር አገልጋይነት ስለሆነ የአንቺ አይደለሁም። በጸሎቴ አብሬሽ ነኝ። ልፈልገው ብለሽ አትድከሚ። ቤቱም አንቺ እናቴም እህቴም ተባርካችኋል ሲላቸው ከሕልማቸው በደስታ ሲቃ ነቁና ሴት ልጃቸውን ቀስቅሰው ውጭ የተኙትን ባሕታውያን ለማየት የደጃፉን መሸንጎሪያ ከፍተው ወጡ። ባሕታውያኑ ግን ቀድመው ሄደዋል። ወደ ምናኔቸው።
እንዳሰበው እንዳቀደው እንደተመኘው የኖረ ሰው ብዙ የለም። የሕይወት ፈታኙ ጥያቄ በውጣ ውረድ መሞላቱ ነው። የልጅነት ሕልሙን ከሚያገኘው የማያገኘው ይበልጣል። በምስቅልቅልና ፈታኝ ጎዳና ውስጥ አባጣ ጎርባጣው እንቅፋቱ መውደቅ መነሳቱ ይበዛል። በሕይወት ጉዞ የተለሳለሰ መንገድ የሚባል የለም። መርከቧ በተጠበቀው ሳይሆን ባልተጠበቀው መንገድ ልትተም አውሎ ንፋስ ማዕበል ሊንጣት አደጋው ሊያሰጥማትም ይችላል። የሚጠበቀው ቀርቶ ያልተጠበቀው ሊሆንም ይችላል። ከእልፎች በጣም እፍኞች ብቻ ምኞታቸውን ያሳካሉ።
አባቶች ሰው እህል ውሀው እንደጠራው እንጂ መቼ እንደራሱ ሀሳብ ያድራል ይላሉ። ሰውኛ ተፈጥሮ ፍላጎቱና ምኞቱ ገደብ የለውም። ሁሉም አብዝቶ ከድህነት ማጥ መውጣትን ፤በሀብት የደለበውና የናጠጠው ደግሞ እጥፍ ድርብ ንዋይ ይሻል። እንዲህ ናት አለም። አንዳንዴ ዘመን የሚያቀብጣቸው ሽቅብ በሀብት ማማና በማግኘት ጣሪያ ላይ በድንገት የሚከምራቸው አይነት ሰዎች አሉ። ማግኘትን በቅጡ ሊሸከሙት ካልቻሉ ትከሻን ይሰብራል።
በሕይወት ጠመዝማዛ መንገድ አቀበትና ቁልቁለት፤ ቆላና ደጋ በረሀ ውስጥ አእላፍ አልፈዋል። እልፎች በተመሳሳይ መንገድ ለማለፍ ይሰለፋሉ። የሚደንቀው የሰው ልጅ ተፈጥሮ ግዜና ዘመን ቢፈራረቅ ባሕርይው ጊዜ የማይሽረው ሁኖ መቀጠሉ ነው። ከብዙዎች እፍኝ የሚሆኑት አለም በቃኝ ብለው ሞልቶ ከተረፈው ሕይወታቸው በድንገት ታጥፈው በቃኝ በሚል መንፈስ ምናኔን ይመርጣሉ። ገዳም ገብተው ይኖራሉ። አለም ለምኔ ብለው። አባ አለም ለምኔ። እማሆይ አለም ለምኔ እንደሚባሉት። ለምን እንዲህ ሆኑ ቢባል መልስ መስጠት አይችልም። ካለባለቤቶቹ በቀር ምስጢሩን የሚያውቅ የለም።
ከየትኛውም የሕይወት ዘርፍ ወጥተው አለም በቃኝ ብለው ምናኔን በውሳኔ ያጸኑ አሉ። ከንቱ ከንቱ አለም ከንቱ እንዳለ ጠቢቡ ሰለሞን። የየራሳቸው ግለሕይወት፤ አስተዳደግ፤ ቤተሰብ፤ የልጅነት ታሪክ፤ የስራ ሕይወትና ልምድ የነበራቸው ያላቸውም ናቸው። በአለም ውጣ ውረድ በፍቅር በትዳር በተለየ ሙያ የነበሩ የጣፈጠውን አለማዊ ሕይወት ጠንቅቀው የሚያውቁ ከፊሎቹ አውሮፓና አሜሪካ ሌላም አለም ላይ ረዥም ጊዜ የኖሩ የብርቅዬ ሙያ ባለቤቶች የነበሩ ጭምር አለም በቃኝ ብለው የመነኑ ሞልተዋል። ምናኔን የመረጡ። የጥንቱን ፋይል የዘጉ። አዲስ ፋይል የከፈቱ። ለዚህም የአብነት ትምህርት ቤቶች ተጠቃሽ ናቸው።
ምናኔው መንደር ሁካታ ጫጫታ ሆታ ኮሽታ የለም። ድሎት ምቾት ዘፈን ዳንስ ዝሙት አስረሽ ምቺው አይታወቅም። ወዳጅ ዘመድ ጓደኛ ፤ ሊቅ ድሀ ሀብታም ፈላስፋ ጉልበተኛ ምናምን የለም። ነግቶ እስኪመሽ፤ መሽቶ እስኪነጋ ፍጹም ጸጥታ ነው። የሚታየው ወደላይ ሰማይ ወደታች የቆሙባት ምድር ብቻ። የሚያስፈራ ጥልቅ ጸጥታ። እዚያ መንደር አለቃና ምንዝር የለም።
ለሀብት ለንብረት ለኮተት ለስልጣን ማሰብ መስገብገብ የለም። ቀን የአእዋፋት ዝማሬና የነፋስ ሽውታ፤ የቅጠሎች መንኮሻኮሽ ሌሊት ደግሞ በቅርብም ሆነ በሩቅ የዱር አውሬዎች ድምጽ ሲያስተጋባ ይሰማል። በምናኔ መንደርና ገዳም ሌላ የሚሰማ የሚታይ ነገር የለም። ራሱን የቻለ አሰፈሪ አለም ነው።
መምህራን፤ የጦር መሪዎች፤ ሀኪሞች፤ መሀንዲሶች፤ ደራሲዎች፤ የናጠጡ ሀብታሞች፤ ፓይለቶች ውብና ቆንጆ ወይዛዝርት የነበሩ ሁሉ ይገኙበታል። ግን ደግሞ ማንም አያውቃቸውም። በየራሳቸው ምክንያት የመነኑ። አለም በቃን ያሉ። ሀገራችን በአራቱም ማዕዘናት ለቁጥር የሚያታክቱ ገዳማት አሏት።ጥንትም ነበሩ። ዛሬም አሉ። ወደፊትም ይኖራሉ።
ሰዎች የአለም ሕይወት በቃን ሲሉ የትላንት ማንነታቸውን ረስተው አውልቀው ጥለው ንስሀ ገብተው በየገዳማቱ ሕግ ተገዝተው በጸሎት እየተጉ በአቅማቸውም አገልግሎት እየሠጡ እድሜ ዘመናቸው እስከፈቀደ ይኖራሉ። ሲያልፉም እዛው ይቀበራሉ። የወንዶች ፤የሴቶች ገዳም ተብለው የተከለሉም አሉ። አሰቦት ገዳም፤ጣና ገዳም፤ ዋልድባ ገዳም፤ደብረሊባኖስ ገዳም እያልን ሌሎችንም ገዳማት መጥቀስ ይቻላል።
ገዳማቱ ውስጥ ከሰው የማይገናኙ በሱባኤ ብቻ የተወሰኑ ፤ መንፈሳዊ ስጦታቸው የረቀቀ የበቁ አባቶችም አሉ። ለሁሉም አይከሰቱም። ከተገኙም ሽረትና ፈውስ ነው። በቀን አንድ ጊዜ ዳቤ ወይ የተቀቀለ ጥሬ ብቻ በራፋቸው ላይ ተደርጎላቸው ቆልፈው ከውስጥ ያሉት መናኝ /ባህታዊ /መነኩሴ በፈቀዱበት ሰዓት ያነሱታል። አይታዩም። የሚታዩም አይጠፉም።
በገዳሙ አካባቢ ባለ ዋሻ ውስጥ የሚኖሩ ። አለምን ንቀው ረስተው። ትላንትን ቀዳደው ጥለው። የከተማ አሸሼ ገዳሜ መብራትና ውሀ በቀን ሶስቴና ከዚያም በላይ እየጠቀጠቁ ማግሳት አቀብ አቀብ መተንፈስ ጭርሱን አይታሰብም። ረሀብን መግታት ጨለማን መልመድ ቀንና ሌሊቱን በጸሎት ማሳለፍ ትንሽ ብቻ ለነፍስ ማቆያ መመገብ የየገዳሙ ዕለታዊ ትዕይንት ነው።
አትክልቶችን መትከል መንከባከብ መመገብ ከስጋ ነክ ነገሮች መራቅ የገዳም ስራ መስራት። እነዛ ገዳማት ውስጥ ስንትና ስንት አለምን ጠንቅቀው ያዩ የወጡና የወረዱባት በዘመናቸው ደምቀው የታዩ ሰዎች ይኖራሉ። ስማቸው የኋላ ታሪካቸው ተሰርዟል።ማንነበርክ/ሽ አይጠየቅም። እነሱም ላይመለሱበት ረስተውት በአዲስ ስብዕና ይኖራሉ። ትላንትን አያነሱም።
አዲስ ዘመን ነሀሴ 9/2011
ወንድወሰን መኮንን