የሥራ ባልደረባዬ የነበረ ሰው ስለሆነ ብዙ ጊዜ አስታውሰዋለሁ ። መቼ መቼ ብላችሁ ግን እንዳትጠይቁኝ ፤ ብቻ ብዙ የሚነሳበት አጋጣሚዎች ስላሉት ግን አልረሳውም ። ዛሬ ደግሞ ለጽሁፌ ማድመቂያ አድርጌ አስታውሸዋለሁ ። በተለይም የዛሬ አሥር ዓመት ገዳማ “ኧረ ጎበዝ በሬ ተደግፈን ….” ሲል ባስነበበው ጽሁፉ አማካይነት ። ጸሐፊው ጋዜጠኛና ደራሲ አንተነህ ይግዛው ይባላል። ጋዜጠኛ ጨዋታ አዋቂ ነው። መረጃ ያገኛል አጣፍጦም ለአንባቢው ያቀርባል… ከተባለ እሱን አንድ ብዬ እቆጥራለሁ ።እንዳው ዛሬ ሳስታውሰው ምላሱን እንዳይነክስ አደራውን እንጂ ብዙ ጊዜ በእንዲህ ባለው አጋጣሚ አነሳዋለሁ።
በዛ ፅሁፉ ታዲያ እንዲህ አለ፤ (ከብዙው ጥቂቱን በራሴ የማስታውሰውን ብቻ) አንድ ኪሎ ስጋ 140 ብር ደረሰ ። አባቴ ስድስት ቤተሰቡን ያስተዳደረው በ140 ብር ደመወዝ ነበር ።ዛሬ የአንድ ኪሎ ስጋ ዋጋ እዚህ ደረጃ መድረሱ ያሳዝናል ፤ያስደነግጣል፤ሙክት በግ ፍየል በስድስት ብር ተገዝቶና ታርዶ ጎረቤት ። ዘመድ አዝማድ ተሰባስቦ ማን ጨርሶት፤ የዛሬዋ አንድ ኪሎ መባሏ ቀርቶ አንድ ጉርሻ ልትባል ምን ቀራት … በቀጣይ ስጋ መብላት እንችል ይሆን? እንደእኔ የምን ችል አይመስለኝም! በሬውን ተደግፈነ ፎቶ እንነሳ።
እኛም ካደግን በኋላ በ140 ብር ስንት ደህና ደህና ወይፈን ይገዛ እንደነበር አድምጫለሁ። በዛን ወቅት የነበረውን የዋጋ ሁኔታ ሰምተን ወጣ ብለን ቁርጥ ጥብስ ሌሎች ባልደረቦቻችን አቆላምጠው በሚጠሩበት አባባል “ጥጥ” (ጥብስና ጥሬ) በምንልበት 22 አካባቢ መቆራ ረጣችን መሆኑን አረዳን። ከስጋ ጋር የሚኖረን ዝምድና የመተያየት ፤ የእንቁልጭልጭ ይሆንና ይሄኔ …ነበር ማድረግ ብለን ያው ማለፍ ነው፤ ማለቴ እኛ ደሆቹ ፤ ያለውማ ምን በወጣው ከሽንጡ። ከሻኛ። ከቀዩ… ከፍ ሲልም አውርደው ማለትን ይቀጥላል ።
ይሄንን አባባል ሁላችንም የምንለው መቼ ይሆን? አቤት ይሄንን ቀን ቀርቦ ባየው ብዬ ተመኘሁ ።ኧረ እንዲቀርብ እንጸልይ ።
አይ ዛሬ ! ዛሬማ አይሞከርም፤ አልሰሜን ግቢ በሏት ብሎ የሚሳለቅብኝ እንደሚኖር እገም ታለሁ። አዎ መሳቅ መሳለቅ ይቻላል። ሁሉንም ነገር ኮስተር አድርገን ካየነው አይሆንማ። ሥራ ቦታ ኮስተር ። በቤት ውስጥ ጭፍግግ። መንገድ ላይ ቁዝም። በችግር ። በኑሮ ውድነት። … ሁሉንም ነገ እንደምናሸንፈው አስበን ዛሬ ብንቀላለድበት አይከፋም፤ መራሩን እያዋዙ ማጣፈጥም ሳይሻል አይቀርም። ቅመም ቅቤ ጣል ጣል እናድርግበት። ኮረሪማ አላልኩ እሱም በኪሎ 350 ብር ይላል ገበያው፤ ቅቤውስ ቢሆን እንዳትሉ የጨዋታ ቅመምና ቅቤ ጣለ አድርጉ ነው ያልኩት ። ጨዋታ እናዋጣ!
ዛሬ ስጋ በኪሎ አራት መቶ ብር ሲባል ለአፍ እንኳን አይከብድም ፤እንዳውም ለመድነው መሰለኝ እቁብ ሰብስበን። ጋባዥ አግኝተን (ዲያስፖራ ማለቴ ነው) ጎራ ባልንባቸው ቦታ ዎች ቁርጡ በመጠጥ ሲወራርድ ሳየው ዋጋው ቀንሶ ድንገት የደረስን መስሎኝ ነበር። ከዛ በላይ ዋጋ የሰማ ችሁ። የተጠቀ ማችሁ ካላችሁ ይቅርታ ሰው የሚናገራው ማለቴ የሚጽፈው ባወቀው ልክ ነው። እኔ በማዘወትረው መገናኛ። አራት ኪሎ። ሲኤምሲ አካባቢ ጎራ ባልኩባቸው ዋጋው እንደዛ ነው። እንዳልኳችሁ ባወቅኩት ልክ ጻፍኩ።
በነገራችን ላይ ያን ወዳጄን ርዕሱን ተውሼ ስወስድ ይቅርታ እንኳን ሳልለው። አሁን ትዝ አለኝ ።ለዛሬ መዋሴን ፍቀድልኝና ከአንዳንድ ነገሮች ሳንቆራረጠ አብረን ፎቶ እንነሳ ልበል ።
ያው ሆድ አየሁ አያውቅም፤ የትናንቱንም አያስታውስም፤ ዛሬም አላየሁ የታል ጥያ ቄው ቀጣይ በመሆኑ ማስረጃና መረጃ ማሰ ባሰቡ ይጠቅመን ይሆን ብዬ ነው። ሆድ ከእን ግዲህ አላየሁም፤አልሰማሁም ቢል የፎቶ ማስረጃዎቻችን ደርድረን እንዲህም በልተን ጠጥተናል እያልን እናስጎመጀዋለን። ትልልቅ አድርገን በሳሎናችን ግድግዳ ከፎቶ ግራፉቻችን ተርታ እንስቀለው? ከተስማማችሁበት ብዬ ነው ሃሳቡን ያነ ሳሁት። ብቻ መረጃ ይኑረን ። ይሄ ታዲያ ለስጋ ብቻ አይደለም ። ሌሎችም እንደየአቅማቸው ሽቅብ ሽቅብ የሚላቸው በዝተዋል።
አቤት ሀበሻ! መቼም የስጋ ነገር አይሆንልን ሆኖ እንጂ ሌሎች እኮ ምግቦች ሞልተዋል። ለምን አትክልት አንበላም? ለምን ፍራፍሬ አናዘወትርም? ጥራጥሬ … አልኩና እሱስ መቼ በቀላሉ ተገኘ ብዬ ይቅርታ ልበል ለራሴ ። ማለቴ አንድ ኪሎ ሽንኩርት 27 ብር ፤ አንድ ኪሎ ሙዝ 30 ብር ፤ይባስ ብሎ ደግሞ አንድ ኪሎ ብርቱካን 50 ብር ሲለኝ እንግዲህ ሀኪም ይዘዝልን እንጂ እርም ፍራፍሬ ማለትን መርጫለሁ። ኧረ! እንዳው ያ ወዳጄ እንዳለው ሀኪምም ቢያዝልን ልንገዛው ስለማንችል ብዬ አሰብኩና “ብርቱካን ይዘን ፎቶ እንነሳ!” ልል ወደድኩ። እሱም የቅንጦት ዕቃና ምግብ እንደምንላቸው መሆኑ አይቀርም፤ አሁን በጀመረው ልክ ወደላይ ሽቅብ ሽቅብ ማለቱን ካልተወ። የእናቴን አባባል ስደግመው “አበስኩ ገበርኩ ” ያሰኛል ። እውነትም ያስ ብላል። ድሮ ብርቱካን ማለቴ ከ 20 ዓመት ወዲህ መለስ ብዬ ነው። ኪሎ አንድ ብር ከሃያ አምስት ሳንቲም ነበር። ከኢት ፍሩት ሁለቱን ኪሎ በሁለት ብር ከሃምሳ ሳንቲም ገዝተን ከእነጣዕሙና መዓ ዛው ፊቴ ድቅን አለ። አሁን አሁን አለኝ፤ መከስ ከስ ልበለው መግመጥ እንጃ ብቻ ግን የሆድ እቃችን ቦጭቦጭ እስኪል ድረስ በልተነ ዋል። ሳይንሱ ለጤና በቀን ግማሽ ፍንካች ቡርቱካን በቂ ነው ቢልም ማን ተግብሮት፤ ብቻ ገበታ ላይ የቀረበው እስኪያልቅ የፌስታሉ እስኪጋባ ድረስ መብላት ነው ፤ደግሞ አበላሉ መጀመሪያ ላይ የላይኛውን ቆዳ ብቻ በማንሳት ይሆንና ጥጋብ ሲበዛ ደግሞ ነጩን ሽፋን እስከማንሳት ይደርሳል ።ነጩ የብርቱካን ሽፋን የምግብ መፈጨትን ያፋጥናል፤ ሆድ ያለሰልሳል የሚለውንም ማን ትዝ ብሎት ። አቤት ብርቱካን ከለታት በአንዱ ቀን ልንላት ነው። የዋጋ ግስጋሴው ከዛ ተነስቶ አሁን በስንት እጥፍ አደገ? ይሄን ለሂሳብ አዋቂዎች ልተወውና አትክልት ብሉ ፤ፍራፍሬም አክሉበት ላልኩት አፉ በሉኝ ። ብቻ ግን ብዙ ነገሮች አሉን ፎቶ አንሱን ያሉ። እኛም እየያዝን ፎቶ እንነሳ።
አዲስ ዘመን ነሐሴ 5 /2011
አልማዝ አያሌው