መሰለፍ በዝቷል፡፡ ለዳቦ፣ ለታክሲ፣ ለዘይትና ስኳር ኧረ ለምግብ ብፌም ጭምር መሰለፍ ግድ ሆኗል፡፡ ጊዜ የተረፈን ይመስል ሰዓታትን በሰልፍ ማሳለፍ ሳንወድ በግድ ለኛ የቀረበልን የየዕለት ገጠመኛችን ብሎም ተግባራችን ሆኗል፡፡ ዛሬ ስለ ዳቦና ዘይት ሸመታ ሰልፍ አይደለም የማውራው ወዳጆቼ፡፡
እሱማ ተብሎ ተሰለቸ ፤ ጭራሽ ተላምደነው ረስተንዋል እኮ፡፡ ይልቅ መንገድ ዘግተው መኪኖችን የሚያሰልፉ ምን አገባኝ ብለው ሰውን ብዙ ጉዳይ ውስጥ የሚያስገቡ መንገድ ዘጊዎች ላወራችሁ ነው፡፡ በእነርሱ ምክንያት መንገድ መድረሻችን ርቆን በእነርሱ ሰበብ ወደምንፈልገው መድረስ ያልቻልንና ስራችን ተበላሽቶብን ውስጣችን የደበነ ስንቶቻችን እንሆን?
ታክሲ ውስጥ ነኝ፡፡ አጠገቤ የተቀመጠው ሰው እጅጉን መቸኮሉ ከሚለዋወጠው የስልክ ምልልስ ተረዳሁ፡፡ “እየደረስኩ ነው 10 ደቂቃ ብቻ፡፡” ይህን አረፍተ ነገር እሱን በመጠበቅ ላይ ላለና ለሚደውልልት ሰው እየደጋገመ ይመል ሳል። የታክሲው ተሳፋሪዎች አብዛኛዎቻችን መነሻችን አራት ኪሎ መዳረሻችን ደግሞ ሜክሲኮ ነው ፡፡
ታክሲው ከአራት ኪሎ ትምህርት ሚኒስቴር ህንፃ አለፍ እንዳለ ከፊት ለፊቱ አላነቃንቅ ያሉት የተሰለፉ መኪኖች ተከትሎ ይንፏቀቃል፡፡ አጠገቤ የተቀመጠው ደዋይ አሁንም ቃሉን ሳይለውጥ “አስር ደቂቃ ብቻ ታገሰኝ መጣሁ ማለቱን አላቋረጠም፡፡
የሰውዬው አስሬ ከኪሱ የሚጣራውን ስልክ እያወጣ በጣም ይቅርታ አሁን እየደረስኩ ነው አስር ደቂቃ ብቻ ማለት ማብዛቱ ካለው ሁኔታ ጋር አነጻጽሬ ግራ ገብቶኝ ይሄ አስር ደቂቃ ለውጥ ተደርጎበት ተሻሽሎ ይሆን እንዴ ብዬ ማሰብ ጀመርኩ፡፡
በነገራችን ላይ ምንም ማደስ መለውጥ እና መቀየር ሲቻል የማይታደስ የማይለወጠው አንዴ ከመረሸ መመለስ የማይቻለው ጊዜ ብቻ መሆኑን ስንቶቻችን አስበነው ይሆን፡፡ ወደ ኋላ የለም በቃ፡፡ ካለው ላይ መቀነስ የነበረውን ትቶ ያልነበረ ላይ ማድረስ የጊዜ ተፈጥሮአዊ ኡደት ነው፡፡
ሰውዬው ቀጥሏል መጣሁ ደረስኩ አስር ደቂቃ…ወይ አስር ደቂቃ! እኮ ሜክሲኮ አይደለም ፍልውሀ ሳንደርስ ብዙ አስር ደቂቃዎች አለፉ፤ ተደምረው ሰዓት የሚሞሉ አስር አስር ብዙ ደቂቃዎች፡፡ ከወዲያኛው የስልክ ደዋይ ወይም ባለ ጉዳይ ደውሎ በማርፈዱ ምክንያት ትቶ በሆዱ ነገረው፡፡ ሰውዬው ተበሳጭቷል ያመለጠው ወሳኝ ጉዳይ መሆኑ ሁኔታው ያሳብቅበታል፡፡
ከታክሲው ወርዶ በእግር አይሮጥ አይደርስ ነገር፤ ታክሲውን አይታገስ ነገር ቆሟል፡፡ ወዳጄ ከወዳጁ ጋር ተቀያይሞ መቅረቱ አልያም ደግሞ ጉዳዩ ሳይሰምር መቅረቱ አናዶታል ። የሚጠብቀው ሰው ቁጣ በተቀላቀለ ግሳፄ ሲናረውና ያሰበው ባለማሳካቱ ቆጨው፡፡ ያለመው ያለመስመሩ አበሳጨው፡፡
እዚያ መድረስ ያልቻለበትን ምክንያት ቢያቀርብ፣ ይቅርታ ቢጠይቅ፣ ቢያስረዳው ወይ ፍንክች፡፡ ከወዲያኛው ስልክ የሚሰማው የቁጣ ድምፅ የሰውዬውን ታጋሽነት እንዳውቀው አደረገኝ፡፡ ሰውዬው በስልክ የሚያወራውን ንግግር ለማስረዳት አልተቸገርኩም፡፡ የደዋዩ ድምፅ አጠገቤ ከተቀመጠው ሰው አልፎ በደንብ ይሰማኛል። ስልኩ የሚልከው ብቻ ሳይሆን የሚቀበለውም እንዳይመጥን የተደረገ ነው፡፡ እና ሰውየው ተሳድቦ ተሳድቦ ዘጋው፡፡ አጠገቤ ያለው ሰው የምር አሳዘነኝ፡፡ እሱም አለመታመኑም ያሰበው አለመሳካቱም አናዶታል፡፡
ወዶጆቼ ስንት ተመሳሳይ ገጠመኝ ገጥሞን በሁኔታውም ተማረን ይሆን፡፡ ከተማዋ ያልዋት መንገዶች በስርዓት መጠቀም አለመቻላችን ለትራፊክ መጨናነቁ አንድ ምክንያት ነው፡፡ አዲስ ያሏት መንገዶች ከሚርመሰመሱባት መኪኖች ጋር አለመግጠሙ ብቻ አይደለም ወዳጆቼ የተሳፈርንባቸው መኪኖች ተሰልፈው እያየን የማሳለፋችን ምስጢሩ፡፡ ይልቁንም መንገዶቹ በአግባቡ መምራት በሥርዓት የትራፊክ ፍሰቱን እንዲያሳልጡ ባለመድረጋቸው ነው፡፡ እርግጥ የመኪናው ቁጥር መጨመር የመንገዱ ውስን መሆን ለዚህ ችግር ማባባሻ ትልቅ ምክንያት መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡
አንዱ ጓደኛዬ ደጋግሞ ሲቀልድ እሰማ ዋለሁ ። እንዲሁ እንቶ ፈንቶ አይደለም ቀልዱ ቁም ነገር የበዛው ለዛን የተላበሰ ቀልድ የሚቀልድ ነው። አንዳንዴ ቢያወሩ የማንሰለቻቸው ጥዑም ንግግሮችን የተካኑ ቢነገሩ የማይጠገቡ ወጎችን አዋዝተው የሚያቀርቡ አንደበተ ርቱዕ የሆኑ ሰዎች ይገጥሙናል፡፡ እንደዚያ ያለ ሰው ነው ወዳጄ፡፡ በሚከብዱ ነገሮች ላይ መቀለድ የሚወድ በዚያም ከባድ ነገሮችን አቅሎ የሚያይ፡፡
ቀላጁ ጓደኛዬ መኪና መግዛት አይደለም በቀን በታክሲ ብዙ ተመላልሶ ኑሮን መግፋት የከበደው ነው፡፡ ኑሮ አንዳይቀልድበት ቀድሞ ኑሮ ላይ ይቀልዳል፡፡ እንዲህ ነው መዳፈር ምን አባቱ የቀለዱበት ጉዳይ መቅለሉ አይቀር፡፡ ሰሞኑ የሆነ ስብሰባ ላይ አርፍዶ ተገኝቶ ለምን እንደዘገየ ተጠየቀ፡፡ “ያው አዲስ አበባ መኪና መንዳት ይከብዳል፤ መኪናዬ መንገድ ዳር ጥዬው አልመጣ ነገር መንገድ ተዘጋግቶብኝ በየት ልንዳ፡፡” የሱ ምላሽ ነበር፡፡
ከኔ በቀር ሁሉም የእሱን ምላሽና አሁን ያለው ሁኔታ አገናዝቦ ያላንዳች ምክንያት ጥርጣሬ ተቀበለው፡፡ አዲስ አበባ መንገዶችዋ ጠበው መሄጃ አጥሮ ብቻ እኮ አይደለም ይሄ ሁሉ የትራፊክ መጨናነቅ ውስጥ የገባችው፡፡ እነዚያን የበዙ ምክንያቶች ደግሞ መኪናው በሚፈለገው መልክ እንዳይጓዝ ሰራተኛውን የፈለገበት በሰዓቱ እንዳይደርስ አድርገውታል፡፡ አስራ አንድ ሰዓት ተኩል ከስራ የወጣን በትራፊክ መጨናነቁ እቤት የምንገባው አምሽተን የናፈቁን ልጆቻችን ጋር ሳንጨወት ደክመው ተኝተው ሆኗል፡፡
ውዶቼ አንዳንዴ መድረስ የፈለጋችሁበት ሳትደርሱ መገኘት ያለባችሁ ቦታ ሳትገኙ ታክሲ ውስጥ ቁጭ ብላችሁ ሰዓታት ያሰለፋችሁበት ጊዜ ትዝ ይላችኋል? ትዝ ይላችኋል ነው ያልኩት የኔ ነገር ያለንበትና የምንኖርበት እኮ ነው ምን ነካህ ካላችሁኝ ልክ ናችሁ፡፡ አንዳንድ ልክ ያልሆኑ ነገሮች ልክ እንዳንሆን ያደርጉናል፡፡ እናም ልክ ባልሆኑ መንገድ ብዙ ልክ የሆኑ ነገሮች ይናዳሉ፡፡
በተለይ የመንገድ መዘጋጋቱን ለማቅለል የሚሰራው የአዲስ አበባ መንገድ ትራፊክ ማኔጅመንት በትራፊክ መጨናነቅ የታወቁና ለጉዞ አስቸጋሪ የተባሉ መንገድና ቦታዎች ለይቶ ማሳለጥ እንዴት ከበደው፡፡ በየመሸታ ቤቱ በራፍ ላይ ተሰልፈው መንገዱ በመዝጋት ሌላን አላሳልፍ ያሉ እነርሱ ደግሞ በአንፃሩ እርፍ ብለው አልኮል በየአይነቱ የሚኮሞክሙ ግድ የለሾች ለምን መግራት አቃተው፡፡
አሁን አሁንማ አንዳንድ ሰፈሮች ላይ ቀን ሲያንቀላፉ ውለው ማታ የሚያብዱ ጉዳኛ የውስኪና መጠጥ ቤቶች ተበራክተዋል ። የመጠጥ ቤቶቹ ደንበኞችም መኪናቸውን አሰልፈው መንገድ ዘግተው በማን አለብኝነት በካካታ ያመሻሉ፡፡ ለመንገድ ስርዓቱ አለመከበር ለትራፊክ ፍሰቱ አለመሳለጥ ትልቅ እንቅፋት የሚሆኑና ያልታወቁ በምክንያት ያልተለዩ ችግሮች እንደነዚህ በርክተዋል፡፡
ይህቺ ከአቅምዋ በላይ ብዙ ነገሮችን የተሸከመችው ከተማ የከተማነት ጥግ ላይ ማድረስ ከብዶን እኛን ጥግ ጥግ ማስያዝ ጀምራለች፡፡ ከፈለግነው ጋር ተገናኝተን በፈለግነው ሰዓት ጉዳያችን ላይ እንዳናወራ ካሻን ቦታ ተገኝተን የሚጠበቅብን እንዳንወጣ ያላትን አቅም ባለመጠቀማችን አቅም አሳጥታናለች፡፡
አዲስ እንደ ባህሪያችን አውላ እንደ አመላችን አሳድራ በሰፊው ሆድዋ ችላን ዛሬ ድረስ ደርሳለች፡ ፡ እኛው በሰራናት ልክ ገጽታዋ የምንመለከት ሰሪዎቿ ነን፡፡ ይህች የብዙኋን መዲና የስምዋን ያህል ባትዋብም የሚበቃንን ባይሆን የአቅምዋን ችራ ታኖረናለች፡፡ እኛ የምንሰጣት ነገር አንሶ ከእርሷ የምንጠብቀው በዝቶ እንጂ ለውጧንማ ማቅረብ እጅጉን በቀለለን ነበር፡፡
ይህቺ የኛ የሆነች ከተማ እንደራሳችን በኃላፊነት የምንይዛት እንደ ግል ጉዳያችን ማደግዋን የምንመኝና ለዚያም የምንታትር ቢሆን ከፍታ ላይ ባስገኘናትና እኛም በዚያ ውስጥ በዋኘን ነበር፡፡ ያላት ውስን ነገር በአግባቡ ባለመጠቀማችን እንቅስቃሴያችን ውስን እንዲሆን አድርጎብናል፡፡ ያሉትን መንገዶች ከኃላፊነት በራቀ ሁኔታ እየዘጋን ለኛ ስራ ስምሪት የሌላውን መዳረሻ ያራቅን ብዙዎች ነን፡፡
ዛሬ ላይ የመንገዱ መጨናነቅ ቀጠሮ እንዳ ናከብር ስራችንን በወጉ እንዳንወጣ አድር ጎናል ። መዳረሻው ርቆን በእግር አንሄደው ነገር ርቀቱ የማይሞከር ሆኖብን የቀጠርነው ሲቀር እየታዘብን ቀጥረውን ስንዘገይ እየታዘቡንም ቅያሜ ውስጥ ገብተናል፡፡ ስለራሳችን ምቾት ስንል የሌላን መንገድ መዝጋቱ ስለራሳችን ስምሪት ስንል ሌላውን መስመር ማሳጠቱ እስከመቼ ይቀጥል ይሆን፡፡
ለእያንዳንዱ ችግር መነሻ ተብሎ የሚጠቀስ ቀጥተኛ የሆነ መነሻ ከማሳየትና ከማየት ባለፈ ትልቁን ችግር የፈጠሩ ትንንሽ ችግሮች ላይ ትኩረት ማድረግ ቢለምድብን የትልልቆቹ ችግሮች መቆሚያ የሆኑ ትንንሽ ችግሮች መቅረፍ የምንችል አይመስላችሁም፡፡ ውዶቼ መንገድ እንሁን ለዚያውም ምቹ መንገድ፤ ሰዎች በተቃና መልኩ ተጉዘው ወዳሰቡበት የሚደርሱበት ቅን መንገድ፡፡ ቸር እንሰንብት፡፡
አዲስ ዘመን ነሃሴ 3/2011
ተገኝ ብሩ (ሻሚል)