ስንት አይነት ዓመል አለ ? እንዲሁ ብድግ ብሎ ነጠላዬን አቀብሉኝ የሚል። ማለቴ ለነገር ማን ነው? ብሎ እንቧ ባይ፤ በፉከራ። ዛቻ። ማስፈራራት እንዳው ደርሶ ሰውን ለማሸማቀቅ መሞከር፤ ኧረ ብዙ አለ። ይሄ ታዲያ ወንዶች ላይ ብቻ እንዳይመስላችሁ ሴቶችም በተመሳሳይ ይታይባቸዋል።
‹‹የቤትሽን አመል እዛው›› የሚል የታክሲ ላይ ጽሁፍ ሳይ ታዲያ ምን ያህል በነገር ተጠብሰው ይሆን ስል አሰብኩ። ይህን ስል ግን እንዲህ አይነት ጽሁፍ የህዝብ አገልጋይ በሆነ መኪና ውስጥ መለጠፉ ተገቢ ነው እያልኩ እንዳልሆነ ይያዝልኝ። ምክንያቱም አገልጋይ ‹‹ተገልጋይ ክቡር ነው›› የሚለውን መቀበል አለበታ፤ እንዳውም ‹‹ደንበኛ ክቡር ነው›› የሚለውን በትልቁ ማስነበብ ይጠበቅበታል።
ደንበኛ ከሌለ ገንዘብ የለም፤ ሥራ የለም። ስለዚህ ሁልጊዜ ደንበኛ መከበር አለበት። አገልጋይስ ካልን ተመሳሳይ ነው። ደንበኛም ካለአገልገይ ምንም መሆን አይችልም። ማን ምን ማድረግ ይችላል? ማለቴ የአንድ ቦታ አገልጋይ የሌላ ቦታ ተገልጋይ መሆኑ አይዘንጋ። ይሄን ወደ ፈላጊና ተፈላጊ እናምጣው።
አርሶ የሚያበላን ገበሬ መቼም የምንሰጠው ትልቅ ቦታ አለ፤ ህይወታችንን የያዘው እሱ በመሆኑ ማለት ነው። ግን እኮ እኛም ለእሱ ስንት እንደምናገለግል በየዘርፉ ሆነን አስሉት። ብዙ ነው እንዳው ዝም ብለን ብቻ እንከባበር፣ እንተጋገዝ … በሚለው እንስማማ። አንዱ ሌላው፤ ሌላውም ለአንዱ አስፈላጊ ነዋ። ከዚህ የተለየ ሀሳብ ያለው ካለ መድረኩ ክፍት ነው ጻፉ፣ ሞግቱን።
ስንት አይነት አመለኛ አለ መሰላችሁ? “አመልሽን እንዳለው ሁሉ አመልክን …” መባል ያለበት። በመንገድም ዘወርወር ሲባል የሚያጋጥም አጀብ የሚያሰኝ ሞልቷል ብቻ እንዲህ አይነቱ አይግጠማችሁ። አንድ ዕቃ ድንገት አይኔ ይገባል። ነገሩ አሁን ለመግዛት ባላስበውም የሚያስፈልገኝ ዕቃ በመሆኑ እገዛዋለሁ ብዬ ዕቅዴ ውስጥ ገብቷል፤ እናም አንድ ቀን መንገድ ዳር ለሽያጭ ቀርቦ አየሁትና ኪሴን የሚመጥን ከሆነ ለመውሰድ ጎንበስ አልኩ። እያገላበጥኩም ደህንነቱን ማረጋገጥ፤ ቀጥሎ የሚመጣው የዋጋ ውጣ ውረድ፣ ክርክር አይደል ወደ ቀጣዩ ምዕራፍ አመራሁ። እናም በዛው መስመር ላይ ነን።
ዋጋውን ደጋግሜ ጠየቅኩ እሱ ግን ምን በወጣው መልስ አይሰጥም፤ ለጠየቀው ሁሉ መመለስ ደክሞት ወይ ሰልችቶት ይሆን እንደእኔው እያገላበጠች የምትመለከተውን እና ከእኔ ቀደም ብላ የነበረችውን ቀስ ብዬ ስንት ይላል? አልኳት። መለሰች ” እሱ አልነገረኝም ሰዎቹ (እንደ እሷ ሊገዙ ዕቃ የሚያገላብጡት) ግን እንዲህ ብለውኛል አለች በሽክሹኩታ ።
ዋጋው ከኪሴም ሆነ ከዕቃው ጋር አልጣጣም ስላለኝ ለምን አትናገርም ዋጋውን አልኩ። ተነፈሰ፤ ሴትየዋ እንዳለችኝ ነው። ስለዚህ ልገዛው አልችልም። በእጄ የያዝኩትን ዕቃ አስቀምጬ መንገድ ስጀምር እሱ ደግሞ ስድቡን ቀጠለ። ካልገዛሽ ምን አስጠየቀሽ በሚመስል መልኩ። ብቻ ያወርደዋል፤ በነፃ ውሰጃ፣ ሌላም ሌላም… ብቻ የማይወረወሩ ቃላቶች የሉም።
ዋጋውን ለመናገር የደከመ የመሰለው ምላስ ለስድቡ ጊዜ ረዘመ “ጉልበተኛ ይዘዝብህ!” ትልቅ ምርቃቱ ነበር ። ኮቴዬ እስኪጠፋ ድረስ የእሱን ድምጽ አዳምጣለሁ የሚለውን በትክክል ባልሰማውም ያው የተለመደው የስድብ ውርጅቢኝ እንደሚሆን መገመት አልቸገረኝም። እኔም እንደ እሱ ወገቤን ብይዝስ ኖሮ ብዬ በገበያው መሀል የሚፈጠረው ሁሉ ተሰማኝ፤ አቤት ስንት አይነት ነገረኛ አለ? ትዝብቴን አጠናከርኩ። ይሄ ነው” አመልክን እዛው” ማለት።
ያለ ዕቃው ዋጋ ሰጥቶ ካልገዛችሁ ማለት አይናችሁን ጨፍኑና ተታለሉ እንደማለት ነው። ግን እኮ የእኛ አገር የገበያ ስርዓት የመንገሪያና የመሸጫ ዋጋው ሀቅና እውነታ ላይ የተመሰረተ ባለመሆኑ ነው እንጂ እንደሌሎች አገሮች የመሸጫ ዋጋው የተወሰነ መሆን ነበረበት። ይሄ ማንም በዋጋም በጥራት ሳይታለል ሳይጭበረበር ግብይት ያካሄድ ነበር። በነገራችን ላይ ከዚህ በመነሳት ነው በመንግሥት እና በንግዱ ማህበረሰብ መካከልም መተማመኑ የማይታየው። የሚነገደውና የሚያቀርበው ፤… አራንባና ቆቦ የሚሆነው።
ይሄንን ስል ምን ትዝ አለኝ? የድሮ ሰፈራችን እማማ ብርቄ ማንም ባይናገራቸው እንኳን ደሞ ይሄ ይቺ ብለው የንግግር መጥፎ ይዘረግፋሉ። ምን አደረጉ? ቢባሉ በእርግጠኝነት መልስ አይኖራቸውም ብቻ አዩኝ። አንጓጠጡኝ። እንዳው ሳስበው ሳስበው የውስጣቸውን ችግር። ድህነቱን የሚገፉበት እየመሰላቸው ይሆናል? ማንም ዞር ብሎ አይዞወት እንኩ ይቺን አይለማ። ያለውም የሌላውም ዝም ጭጭ ከሆነ የተቸገረው ምሬቱን በመጥፎ ንግግር በስድብ ማውጣቱ አይቀርም። እኛም አመለቢስ የሚለውን ስም ሰጥተን ግን ደግሞ የችግሩ መሰረት ምን ይሆን ብለን ብንነሳ መፍትሄው እኮ በእጃቸን መዳፍ ሥር ይሆናል፤ ደግሞም ነው።
ነገርን ቀለል ቀለል የሚያደርጉ ደግሞ አሉ፤ እነሱን ያድርገኝ ማለት ጥሩ ፀሎት ነው። ማን ለነገር ጭንቅላቱን በነፃ ያከራያል? እንዳው ቢሆን ቢሆን ኧረ ደግሞ ይሆናል ክፉ ነገርን ሰምቶ እንዳልሰሙ መሆን፤ ነገርን ቀለል አድርጎ ማየት ለእያንዳንዱ ችግር ምክንያት በመፍጠር ራስን ነፃ ማውጣት ከምንም በላይ ትልቅ ዋጋ አለው። አብሮ ለመኖር ከቤት ውስጥ እስከ ውጭ የሥራ ቦታ በጎረቤት ብቻ ሁሉን ችሎ አቻችሎ መኖር ጥሩ የሚባል ይሆናል። ካልሆነስ ካላችሁ ካልሆነማ ጭንቀት፤ ስኳር፤ ደም ግፊት…መሰል ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን መጥራት ይሆናል። ይሄንን ስል ግን ሁሉም ህመምተኛ በዚህ ምክንያት የታመመ ነው ለማለት እንዳልሆነ ይያዝልኝ።
ዋናው ግን እንዳው የስነልቡና ባለሙያዎች እንደሚሉት ትልቁ ጉዳይ አዕምሮን ሥራ አለማሳጣት ነው። ሰው ቁጭ ሲል የሆነ ያልሆነው ሲያስብ ሌላውም ሌላውም ሲጨማመርበት አዕምሮው ለፈጠራ ለሥራ መሆኑ ይቀርና ለፀብ። ለለከፋ፣ ለተንኮል፣ ሰውን ለማጣላት… ብቻ ለክፋት ይውላል።
እንዲህ አይነት ሰው ከዕለታት አንድ ቀን ቢሆንም ፀባይ ማረሚያ ጎራ ማለቱ አይቀርም። አዎ! ጎራ ማለት አለባቸው። የሕግ የበላይነትን ካለወቁ በሕግ አምላክ ቢባሉም ጆሮ ዳባ ይሆናል። እሱ ብቻ አሸናፊ የሆነ ይመስለዋል፤ መሳደብ፣ መበጥበጥ ትክክለኛ ነገር ሊመስለው ይችላል:: እናም ሁሌም እሱ ልክ መሆኑን ለራሱ ያስረዳል። ለራሱ ትክልል የሆነ ቢመስለውም ትክክል አለመሆን ሕግ እንዲያሳውቀው ቢደረግ እሱ ከጥፋቱ ተምሮ ለሌላውም የሕግን የበላይነት የሚሰብክ አይመስላችሁም?
ይሄንን ስል ምን ትዝ አለኝ። ሁለት ልጆች ኳስ ይጫወታሉ። እኔ ደግሞ በዳኝነት ላገለግል ተመርጫለሁ። እናም ጨዋታው ሕግ ወጣላት ከህጉ አንዱ መበሻሻቅ አለ የሚል ነው። ሁለቱም በዚህ ሀሳብ ተስማሙ፤ መበሻሸቅ የማንንም መብት ሳይነኩ በሚለው መቋጫ ጨዋታው ቀጠለ ። እንደሚያሸንፍ በራሱ የተማመነው እንዳሰበው ሳይሆን ጎል እየገባበት ተቃራኒው ደግሞ ጎሉን እያስቆጠረ ጨዋታው ደራ። አሸናፊና ተሸናፊ ተለይቶ ጨዋታው ይጠናቀቃል። በቤት ውስጥ ሕጉ መሰረት በችሎታው ባልተማመነው ተጫዋች ጨዋታው ተጠናቀቀ። እናም የብሽሽቁ ሰዓት ደረሰና አሸናፊው ብዙ ጊዜ ጎል አግቢዎች የሚደንሱትን ዳንስ በመደነስ እይተገለባበጠም ደስታውን ገለፀ። ይሄን ጊዜ ንዴቱን አልችል ያለው ተቃራኒ ቡድን ዘሎ አናቱ ላይ ጉብ አለ። ይሄ እንግዲህ በንዴት መሆኑ ነው ተገላገሉ ልጁም ተቀጣ፤ ከዛ እንዴት እመታለሁ ብሎ ቡራ ከረዩ አለ፤ ለማስረዳትም ለመረዳትም እልሁ አለና በዕለቱ በቅጣት ታለፈ ።
በተገቢው ቦታ ተገቢው ቅጣት ጥሩ ፍሬ ያፈራል እና ተኝቶ ሲያስበው ጥፋቱ ፀፀተውና በማግስቱ ሁሉንም ሰው ይቅርታ ጠየቀ። ሁሉም ነገር በተገቢው መልኩ ቅጣት ከተሰጠው የጎበጠው ይቃናል። ይሄ ብቻ አይደለም፤ የራስም ችግር ይታያል ወደ መስመር መግባትም ይኖራል። መስመሩን የሚያውቅ ደግሞ የወደፊቱንም ያያል።
አዲስ ዘመን ሐምሌ 28/2011
አልማዝ አያሌው