አንድ ህዝብ፤ ሲደሰትም ሆነ ሲያዝን፣ ሲበደልም ሆነ ሲታፈን፣ ሲገፋም ሆነ ሲከፋ፣ ሲደላውም ሆነ ሲመቸው ያንን ክስተት ከነባለቤቱ “ሰንዶ” የሚገልፅበትና ድርጊቱን ለታሪክ የሚያስቀምጥበት የራሱ የሆነ ቋንቋ፤ ዘዴና ብልሀት አለው። “መንጃ” እና “መፍጃ”ም የዚሁ ውጤት ናቸው።
ስነ-ቃል (በተለይም ቃል ግጥም)፣ ልዩ ልዩ ምልክቶች፣ ሙዚቃዎች፤ እንዲሁም የግርግዳ (በየመፀዳጃና መሰል ቦታዎች)፣ ታክሲ … ላይ ፅሁፎች (graffiti) “መንጃ” እና “መፍጃ”ን ከመሳሰሉ ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ሁነቶችን (“Tragedy”ም ማለት እንችላለን) ለመግለፅ ከሚያገለግሉት ሀገር-በቀል መሳሪያዎች ቀዳሚዎቹ ናቸው። ግለሰባዊም ሆነ ማህበራዊ ብሶት፣ የጭቆናና ግፍ መግለጫ እና አንባገነኖችን ማውገዣ ብቻ ሳይሆኑ ፈጣሪ አምላክንም መማፀኛ ረቂቅ ብልሀቶች ናቸው። የ“መንጃ” እና “መፍጃ”ን ጉዳይም ለፈጣሪው የሚያስተላልፍበት ፈጣን መንገድም ይሄው ረቂቅ ብልሀት ነው።
አንድ ህዝብ አንድን ጉዳይ፣ ክስተትና ሁነት አንሻፎ፣ አጣሞ፣ አዙሮና አዟዙሮ ከገለፀው ያለ ምክንያት አለመሆኑን መጠርጠር ተገቢ ነው። ለምን ቢባል ህዝብ ነዋ፤ ህዝብ ደግሞ ከግለሰብም ሆነ ከቡድን በእጅጉ ይለያል። አስቦ፣ መዝኖና አመዛዝኖ ነው ውሳኔ ላይ የሚደርሰው።
ለውሳኔ ደግሞ የጋራ ጉዳይ ይፈልጋል፤ አንድ የሚያደርገው፣ የሚያስተሳስረው፣ አገራዊ የሆነ ነገር ይሻል። ዝም ብሎ እንኳን ስያሜን ቢሰጥ እንኳ የዘላቂነት እድሉ ቀጫጫ ነው። ለዚህም ነው “መንጃ” እና “መፍጃ” እያማረባቸው፤ ታሪካቸው እየተፃፈና እየተፃፃፈ (ልክ እንደዚህ) የሚሄደው።
በአንድ አገር ውስጥ በሚፈጠር ማንኛውም ጉዳይ ተጠቃሚውም ሆነ ተጎጂው፤ ተወቃሹም ሆነ ተወዳሹ ህዝብ ነው። ህዝብ ጠያቂም ተጠያቂም ነው። ያልተመቸውን መንቀል መብቱ እንደሆነ ሁሉ የተመቸውን መትከልም መብቱ ነው። ይህን ካላደረገ ተጠያቂ ነው። በዳይ ሲያጋጥመው፣ ገዥ ሲገዛው፣ አጥንቱ ሲጋጥ ዝም አይልም ይጠይቃል። ለምን? ይላል። የ“መንጃ” እና “መፍጃ” ስያሜና አንድምታውም ይሄው ነው፤ ተጠያቂና ጠያቂን በውስጡ ይዟልና።
ጉዳዩን ወደ ርእሰ-ጉዳያችን እንመልሰው፤ በአገራችን ከትራንስፖርት አገልግሎት፣ ስምሪትና ሥርዓት ጋር በተያያዘ በርካታ አባባሎች በታሪክ ተመዝግበው ይገኛሉ። አሁንም እየተመዘገቡ ያሉት ቀላል ቁጥር ያላቸው አይደሉም። በአስተሳሰብም ሆነ በግብር ቆሞ የቀረን “የተርኪሽ ባቡር”፣ ርህራሄ የለሽ አብዮትንም “ፈጣን ነው ባቡሩ”፣ ከነ“ሚኒ ባስ” በፊት ቀደም ብላ ስምሪት ውስጥ ገብታ የነበረችውን ቶዮታ ታክሲ “ውይይት”፣ አንበሳ የከተማ አውቶቡስን “አንቺ” ብሎ በእናትነት ስሜት መጥራት (ከአገልግሎቷና ዋጋዋ በመነሳት) እና ሌሎችም አሉ። “አባ ዱላ”፣ “ወያኔ” … የመሳሰሉትም የየራሳቸው ታሪክ አይኖራቸውም የሚል የለም።
ይህ አይነቱ አሰያየምም ሆነ አጠራር ብዙውን ጊዜ ከመልካም ነገር በመነሳት ሲሆን በተቃራኒው ሲከሰትም ለተከሰተው ነገር ባህርይና ተግባር የሚመጥን ስያሜም ሆነ መገለጫ ይሰጠዋል። ለምሳሌ የቻይናው “ሲኖ-ትራክ” የሚባለው ከባድ መኪና በየሄደበት ሁሉ ስራው ሰው መግደል ሆኖ ሲያርፈው ከመልኩ፣ ግብሩና በአገራችን ከተከሰተ አንድ ጉልህ አሰቃቂ ታሪክ ጋር በተያያዘ ስያሜ ተሰጥቶት አረፈው፤ “ቀይ ሽብር” ተባለ (በነገራችን ላይ ይህ ትራክ በሰውና ንብረት ላይ እያደረሰ ያለው አደጋ እየከፋ መምጣቱን ተከትሎ ምክንያቱን የሚያጣራ ብሄራዊ ኮሚቴ እስከመቋቋም ተደርሶ እንደ ነበር ይታወሳል)።
እናም ህዝብ ለአንድ ነገር፣ ጉዳይ፣ ክስተትም ሆነ ሁነት ስም ሲያወጣ፣ ስያሜን ሲያፀድቅ እርስ በእርሱ ይነጋገራል እንጂ ዳቦ ሲቆርስ አይገኝም። ይህን ደግሞ የሚያደርገው ያለ ምክንያት አይደለም፤ አገራዊ ችግሮች ሀይ ባይ ሲያጡ፣ ከልካይ ሲጠፋ፣ ተዉ የሚል ሲታጣ፣ ወንጀልና ወንጀለኛ ሲበረታና ሰላም ሲርቅ፤ ህይወት ለአደጋ፣ አገር ለወሮባላ ስትጋለጥ ነው ወደ እዚህ አይነቱ እርምጃ የሚሄደው። “መንጃ” እና “መፍጃ”ም ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚታይ እንጂ ሌላ ሚስጢር የለውም።
ይህን የመሰለውን ወቀሳና ሙገሳ ለዚህ ፅሁፍ ሲባል በአንድ ጉዳይ፣ በ“መንጃ” እና “መፍጃ” ላይ ቀነበብነው እንጂ በየዘርፉ አለ። በተለይ ወደ ቀደመው ታሪካችን ስንሄድ ብዙ ነገሮች ተገልፀው የምናገኛቸው በዚሁ ዘዴና ብልሀት ነው።
አንድ እግር በርበሬ መንቀል አቅቷችሁ፣
አቃጥሎ ለብልቦ አንድዶ ይፍጃችሁ።
የሚለውም ክፉ አገዛዘን መፋለሚያ ቃል ግጥም ነው። እንደ ሲኖ ትራኩ ሁሉ ቀይ ሽብር ልጇን የበላባት እናትም:-
መላኩ ተፈራ የ’ግዜር ታናሽ ወንድም፣
የዛሬን ማርልኝ ሁለተኛ አልወልድም።
የሚሉ ገዳዮች ካቅሟ በላይ የሆኑባት እናት እንጉርጉሩ የዚሁ የህዝብ ታሪክን ሰንዶ የማቆየት ውጤት ሲሆን፤ ጠቃሚነቱም ዛሬ ለበርካታ ተመራማሪዎች የጥናትና ምርምር ርእሰ-ጉዳይ ሆኖ መገኘቱ ነው።
ይህ ነገር በቃል ደረጃም አለ፤ ልክ እንደ “መንጃ” እና “መፍጃ” ማለት ነው። ለዚህም ምሳሌ ይሆን ዘንድ “ባዙቅ” እና “ባሻ ባዙቅ”ን ማንሳት ይቻላል። በወቅቱ የነበረው ህዝብ ይህን ስያሜ የሰጠው “ባንዳ” ለሚለው ቃል በአቻነት ሲሆን የመጀመሪያ ለቱርኮች አድሮ አገሩን ለከዳ ባንዳ የተሰጠ ነው፤ ሁለተኛው ደግሞ አገሩን ክዶ ለጣሊያን ያደረ ኢትዮጵያዊ ባንዳን የሚመለከት ነው።
ይህን መሳይ ህዝባዊ እሮሮ ነው እንግዲህ ህዝብ በተለያዩ ወቅቶችና አጋጣሚዎች የሚከሰቱ ዘግናኝና አስከፊ፤ እንዳይደገሙ የሚፈለጉ ሁነቶችን በቅኔም ይሁን፣ አሽሙር፤ በስላቅም ይሁን በገደምዳሜ እሚለውን ብሎ፣ ለግብራቸው እንዲስማማ አድርጎ ለታሪክ የሚያስቀምጠው። ከዛስ፤ ሁሉንም ታሪክ ይፈርደዋል።
የተነሳንበትን ሳንረሳው እንያዘው። በአሁኑ ሰአት የ“መንጃ” እና “መፍጃ” ጉዳይ ለማንኛችንም ብርቅ አይደለም። እንደወጡ መቅረት የብዙዎች እጣ ፋንታ በሆነበት፤ ከቤት ሳይወጡም ዘሎ በገባ ባለመፍጃ ፈቃድ ሰው ህይወትን ማጣት፣ እየተኙ በሚያሽከረክሩ ባለ“መፍጃ” ፈቃዶች በጠራራ ፀሀይና አውላላ ሜዳ ላይ ህይወትን መቀጠፍ፣ በሚሊዮንና ቢሊዮን ደረጃ ንብረትን ማጣት እንደ ጥሩ ልምድና አዋጪ ቢዝነስ እየተስፋፋ ባለበት በዚህ ክፉ ዘመን ህዝቡ “መንጃ ፈቃድ”ን በ“መፍጃ ፈቃድ” ቢለውጠው፤ በዚህም ቢስማማና ለጋራ መግባቢያነት ቢያውለው ምኑ ሊገርም፤ ማንንስ ሊያበሳጭ ይችላል?
ይህን ፅሁፋችንን፤ ወይም የባለ“መንጃ” እና “መፍጃ” ፍቃድ ባለቤቶችን “ገድል” በተጨባጭ ማስረጃ አስደግፈን እንሰናበተው ዘንድ ወደ ትክክለኛ መረጃዎች እንሸጋገር።
የተለያዩ፣ ግን ደግሞ የተደጋገፉ ተገቢ መረጃዎችን እያጣቀስን ስንመረምር የምናገኘው አስደንጋጭና ሰቅጣጭ ክስተት ቢኖር የትራፊክ አደጋ እያደረሰ ያለው የሰብአዊ ፍጠር ህይወት መቀጠፍና የንብረት መውደም ጉዳይ፤ ይህንንም ተከትሎ የትራፊክ አደጋ ከገዳይ በሽታዎች ሁሉ በላይ የከፋና በደረጃውም ወደ አንደኛ ገዳይነት እየመጣ መሆኑን ነው።
ከትራፊክ ፖሊስ፣ ከመንገድ ደህንነት፣ ከምሁራን የጥናት ወረቀቶችና ሌሎች ሰነዶች ላይ እንደተመለከተው ጉዳዩ ከመስመር እየወጣ፣ የሰው ልጅ ህልውና አደጋ ላይ እየወደቀ መሆኑን ነው። (የተሽከርካሪዎቹ መሪ በባለመንጃ ፈቃዶች ሳይሆን በባለመፍጃ ፈቃዶች እየተዘወረ ነው በሚያስብል ደረጃ።)
ኢትዮጵያ ከዓለም ትንሹ የመኪና ቁጥር እጅግ ከባድና ሰቅጣጭ የመኪና አደጋ ከሚደርስባቸው በጣም ጥቂት አገራት ቀዳሚዋ ነች። ግን 600 ሺህ የማይሞሉ ተሽከርካሪዎችን መምራት ባለመቻሏ ምክንያት በየቀኑ በአማካይ እስከ 41 ሰው ይሞታል፤ 90 በመቶም የትራፊክ አደጋ ይመዘገብባታል።
የቅርብ መረጃዎችን (ለምሳሌ አዲስ ዘመን ሰኔ 29/2011 ዓ.ም) ዋቢ አድርገን እንኳን ብንመለከት በትራፊክ አደጋ ምክንያት ባለፉት አምስት ዓመታት ብቻ የ16 ሺህ ንፁሃን ዜጎች ህይወት የተቀጠፈ፤ ከ50 ሺህ በላይ ከባድና ቀላል የመቁሰል አደጋዎች የደረሱ ሲሆን 85 በመቶ ጥፋቱ የአሽከርካሪዎች ነው። ታዲያ “መንጃ ፍቃድ”ን ወደ “መፍጃ ፍቃድ” የቀየረው ማነው?
በ2009 ዓ.ም ብቻ 4ሺህ 479 ሰዎች ለኑሯቸው ደፋ ቀና ሲሉ ህይወታቸው “መፍጃ ፈቃድ” ባላቸው ሰዎች ተጠልፏል። በ2010 አ.ም 5ሺህ 180 ሰዎች ሲቀጠፉ 3ሺህ 036 ሰዎች ደግሞ ለከፋ አካል ጉዳት ተዳርገዋል። እየተጠናቀቀ ባለው 2011 ደግሞ ደጉን ያሰማን እንጂ ምን እንደተደረገና ምን እየተደረገ እንደሆኑ ገና አልታወቀም። እዚህ ላይ የወደመውን ንብረት ትተነው እንጂ አገር ዜጎቿን (በተለይ ሰራተኛ የሆነውን የሰው ሃይል) ብቻ ሳይሆን ሀብት ንብረቷንም አጥታለች።
የተነሳንበትን ርእሰ-ጉዳይ ተጨባጭ ለማድረግ ያህል ይህንን ካልን ይበቃል። (እዚህ ላይ ግን አንድ ነገር ብሎ ማለፍ ተገቢ ነው። ህዝቡ ምንም እንኳን ችግሩ ካቅሙ በላይ ቢሆንበት “መፍጃ ፍቃድ” ስያሜን ወደ ማንገሱ ሄደ እንጂ ከዛ በፊት “ኧረ የህግ ያለህ፤ ኧረ ይሄ መንጃ ፈቃድን ያህል ነገር በገንዘብ የመለዋወጡ ነገር ይቅር፤ ኧረ ስለነብስ … በማለት ሲጮህ መክረሙን ስለትእግስቱ፣ ትዝብቱና ስያሜ አሰጣጡ ሲባል ማስታወስ ያስፈልጋል።)
“መፍጃ ፍቃድ” ተሽሮ፤ “መንጃ ፍቃድ” ወደ ነበረበት ወርቃማው ዘመን ተመልሶ ለማየትና ለመስማት ያብቃን። አሜን!!!
አዲስ ዘመን ሐምሌ 29/2011
ግርማ መንግሥቴ