
የሰው ልጆች ሕይወት አንድም በደስታ፣ አልያም በፈተና አጋጣሚዎች መዋዘቱ አይቀሬ ነው:: ብዙ ጊዜ ደስታን እንደራሳቸው ቆጥረው የሚጋሩ፣ በእኩል መንፈስ የሚካፈሉ ወገኖችን ማየት የተለመደ ነው:: እንዲህ መሆኑ ደግሞ ጉዳዩ ላያስገርም፣ በአድናቆት ላያስደምም ይችላል::
የሰው ልጆች የማንነት ልክ የሚመዘነው ችግርና ፈተና ጓዛቸውን ይዘው ወደ ሕይወታችን በደረሱ ጊዜ ነው:: እንዲህ በሆነ አጋጣሚ ታዲያ ደስታን በዋዛ ቀርቦ እንደመካፈል ሆኖ ሁሉም ጉዳይ ቀላል ሆኖ አይገኝም:: ችግርን እንደራስ አድርጎ የመቀበሉ እውነታ ሳስቶ ይታያል:: ፈተናን በእኩል የመጋራቱ አጋጣሚም እየቀነሰ ይገኛል::
በአብዛኛው ይህ እውነታ በበርካቶች የሕይወት መንገድ ላይ የሚከሰት አጋጣሚ ነው:: እንዲህ አይነቱ ሐቅ ሁሌም በሰው ልጆች ማንነት ውስጥ ይኖራል፣ ያጋጥማል ቢባልም ይህን ግድግዳ ጥሰው ታሪክን የሚለውጡ፣ ኅዘንን በደስታ የሚተኩ፣ ትኩስ ዕንባን ከፊት የሚያብሱ በርካታ ልበ መልካሞች አይታጡም::
እንዲህ አይነቶቹ ብዙ ጊዜ በመልካምነት ጎራ ሲገኙ በራሳቸው በጎ ፈቃድ እንጂ በማንም ግፊትና አነሳሺነት አይሆንም:: እነሱ በተገኙበት አጋጣሚ ሁሉ ውስጣቸው ለበጎነት ይፈጥናል:: የየዕለት ድርጊታቸውም በጥሩ ምግባር ተገንብቶ ይገለጣል::
ዓለማችን በጦርነት፣ በበሽታ፣ በድንገተኛ አደጋዎችና መሠል ሁነቶች ስትታመስ መኖሯ አዲስ አይደለም:: አንዳንዴ ይህ አይነቱ ክስተት ኃይል አላቸው ከሚባሉ መንግሥታት አቅም በላይ ሆኖ ችግሩን ለመታደግ ፈታኝ የሚሆንበት አጋጣሚ ይበረክታል:: እንዲህ በሆነ ጊዜ ማንነታቸው በቅንነት የሚገለጽ በጎ ፈቃደኞች መልካምነታቸውን አውጥተው ሲመነዝሩት ይስተዋላል::
ይህ ዓይነቱን ልብ የተቸሩ ወገኖች ታዲያ ሁሌም የሚያስቀድሙት የውስጣቸውን በጎነት ብቻ ነው:: በእነሱ ዘንድ ዘር፣ ሃይማኖት፣ ቀለም ፆታና ዕድሜ ይሏቸው ልዩነቶች ትርጉም የላቸውም:: ሰዎች ናቸውና ቅድሚያውን ለሰው ልጆች ክብር ይሰጣሉ:: በጎነታቸውንም በጉልበት፣ በዕውቀትና በፍቅር ገልፀው ያስመሰክራሉ::
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ማለት ምንም ዓይነት ግዴታ ያልታከለበት፣ ከሰብዓዊ ማንነት የሚመነጭ እውነተኛ ስሜት ነው:: ከበርካቶች መሐል ተለይተው ስለሌሎች እስትንፋስ የሚኖሩ በጎ ፈቃደኞች ዓላማና ትልማቸው ሌሎችን በመርዳት ላይ ይታነጻል:: ይህን በማድረጋቸውም ከማንም የሚጠይቁት የገንዘብ፣ የምስጋናና የአክብሮት ክፍያ የለም:: የእነሱ ዋጋ የሚለካው ያጡትን ሲያገኙ፣ የተቸገሩት ምላሽን ሲቸሩ ብቻ ነው::
በዓለማችን ላይ የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች በበርካታ ተግባራት ይገለጻሉ:: ማኅበራዊ ኢኮኖሚያዊና አካባቢያዊ ችግሮች መላ እንዲበጅላቸው ለማስቻልም የበጎ ፈቃደኞች አስተዋፅዖ የድርሻውን ይወጣል:: በጦርነት፣ በችግር፣ በሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች ሁሉ ለነዚህ ወገኖች ቅስቀሳና ጥሪ አያሻም:: መልካም ልቦናቸው በበጎነት የታነጸ፣ ፈጣን አካላቸው ለሰፊ እገዛ የተዘጋጀ ነውና::
በጎ ፈቃደኝነትን ሁሉም ሰው አይቸረውም:: በጎነትን ለመዋረስ በተፈጥሮ መሰጠትን ይጠይቃል:: የራስን ጥቅም አሳልፎም ስለሌሎች ፍቅር መኖር ግድ ይላል:: በጎ ፈቃደኞች በሚከውኑት መልካም ምግባር በገንዘብ የሚተመን ዋጋ የላቸውም:: የእነሱ የምንግዜም ክፍያ ከድርጊታቸው ጀርባ የሚያገኙት የሕሊና እርካታ ብቻ ይሆናል::
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከማኅበራዊ መስተጋብር ባለፈ ስለ ሰላም የሚኖረው ዋጋ ከፍ ያለ ነው:: ከውስጥ ሰላማዊ ማንነት የሚመነጨው ስሜት አካባቢና ሀገርን ብሎም መላውን ዓለም ለመታደግ ኃይል አለው:: በጎ ፈቃደኞች ስለሌሎች የሚከፍሉት መልካምነት ሕይወትን በብዙ ይለውጣል፣ ዕንባን ያብሳል፣ ታሪክን ቀይሮ የምስጋና በረከት ይሆናል::
በመላው ዓለም የሚገኙ ድንበር ተሻጋሪ በጎ ፈቃደኞች ሁሌም ጊዜና ጉልበታቸውን፣ ገንዘብና ዕውቀታቸውን የሚጠቀሙት በጎ ተግባራትን በመከወን ነው:: አቅም ላጡ ምርኩዝ በመሆን ይደግፋሉ:: ትምህርትን ለሚሹ ዕውቀታቸውን ያጋራሉ:: ከዚህም ባለፈ ረሀብና ጦርነት፣ ስደትና አደጋ በደረሱባቸው ስፍራዎች ተገኝተው ከመልካምነታቸው ያካፍላሉ:: ይህን በጎነት ሲከውኑ ግን ክፍያቸው የተለመደው የሕሊና እርካታ እንጂ በገንዘብ የሚቆጠር ደመወዝ አይደለም::
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የመተባበር፣ የመተጋገዝ መገለጫ ነው:: አንዱ ሲወድቅ ሌላው እያነሳ መተባበሩ አብሮነትን በግልጽ ይተገብራል:: በዚህ ኅብረት መሐል ፍቅርና አንድነት ለሰው ልጆች ማንነት ወሳኝ እውነታዎች መሆናቸውን የሚያመላክት ሐቅ ይገለጣል:: በበጎ ፈቃደኞች መልካምነት በርካቶች ሕይወታቸው ተቀይሯል:: ዕንባቸው ታብሶ ፈገግታቸው ተመልሷል::
በሀገራችን በተለያዩ አጋጣሚዎች በደረሱ ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ አደጋዎች ሞት፣ የአካል ጉዳትና የንብረት ውድመቶች ሲከሰቱ ቆይተዋል:: እንዲህ በሆነ ጊዜ ሰብዓዊ ማንነታቸውን አዳምጠው በስፍራው የተገኙ በርካቶች ችግሮችን ለመታደግ ተረባርበዋል:: በራሳቸው ይሁንታ ተገፍተው ባበረከቱት በጎ አስተዋፅዖም ትርጉም ያለው ተግባራት ከውነው የወገኖቻቸውን ሕይወት ታድገዋል::
እነሆ! ሰኔ ግም ሊል ቀናት ቀርተውታል:: መጪውን የክረምት ወራት ተከትሎ ከበርካቶች የሚጠበቀው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ጥቂት የማይባል ኃላፊነትን የሚጠይቅ ይሆናል:: በዚህ ወቅት ተማሪዎች ከትምህርት ቆይታ የሚያርፉበት፣ አእምሯቸውን ለዕረፍት የሚያዘጋጁበት ነው:: አብዛኞቹ ግን ይህን ጊዜ ለዋዛ ፈዘዛ አይጠቀሙትም:: መልካምነታቸው ከበጎ ተግባር አውሎ ትርጉም ያለው ተግባርን ይከውኑበታል::
የበጎ ፈቃደኞች ልብ ሁሌም ቢሆን ማረፊያው ከመልካምነት ጥግ ነው:: ለእነሱ የክረምቱ ዝናብና ጭቃ የጥንካሬቸው ማሳያ፣ የብርታታቸው ልክ እንደሆነ ይቀጥላል:: በዚህ ወቅት በበጎነት ልቦና የትራፊክ ሂደቱን ያሳልጣሉ:: የአቅመ ደካሞችን ቤት ይሠራሉ:: የተቸገሩ ወገኖቻቸውን ደግፈው ኃይልና ትከሻ ይሆናሉ::
ይህ ጊዜ በጎ ልብ ላላቸው ሁሉ ድርጊታቸው በመልካም እሴት የሚገለጽበት ነው:: በአረንጓዴ ዐሻራ፣ በደም ልገሳ፣ በማጠናከሪያ ትምህርት እገዛና በሌሎችም ተግባራት የሚሰማሩ ወጣቶች የድካማቸውን ፍሬ የሚያዩት ውለው ሳያድሩ ይሆናል:: ለዚህ ሁሉ በጎነታቸው ደግሞ ሽልማታቸው የንዋይ ጥቅም አይደለም:: እርካታቸው የተለመደው የሕሊና ደስታና የአእምሮ ሰላም ብቻ ነው::
በተለያዩ ዩኒቨርስቲ የሚገኙ ተማሪዎች በሚማሩበት አካባቢ ማኅበረሰቡን በማገልገል በርካታ ቁምነገሮችን ይተገብራሉ:: ይህን በማድረጋቸው በብዙ የጎደሉት ተሟልተው ክፍተቶች ይደፈናሉ:: የማኅበረሰቡ አቅም ጎልብቶ የጎበጡት ይቃናሉ:: አብዛኞቹ ይህን በማድረጋቸው የጠቀሙት ራሳቸውን እንደሆነ የሚናገሩት በሙሉ መተማመን ነው:: እርካታው በውስጣቸው ዘልቆ ሲያልፍ ይሰማቸዋል::
በሁሉም ዘንድ ውጤታማ የማኅበረሰብ አገልግሎት ይኖር ዘንድ የእርስ በርስ ግንኙነትን ውጤታማ ማድረግ ያሻል:: በሀገራችን ከጥቂት ዓመታት በፊት በሥልጠና መታገዝ የጀመረው የበጎ ፈቃድ አገልግሎትም ለዚህ መፍትሔ እንደሆነ ዘልቋል:: ወጣቶች ለአገልግሎቱ በየቦታው ሲዘዋወሩ ባህልና አኗኗርን እንዲጋሩ አስችሏቸዋል:: የልምድ ልውውጥን በመቅሰምም በገንዘብ የሚተመነውን ዋጋ በበጎነት መክፈል ችለዋል::
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በማንነት አጥር አይወሰንም:: ማንኛውም ሰው በሚገኝበት ዕድሜና የኑሮ ደረጃ የአቅሙን በማበርከት በጎነቱን ማሳየት ይችላል:: ሰዎች ከሚችሉትና ካላቸው አቅም ጉልበት፣ ዕውቀትና ገንዘብ ቀንሰው ለሌሎች መድረስ ከቻሉ የዜግነት ኃላፊነታቸውን ይወጣሉ::
ችግሮች ባሉበት ሁሉ የመልካሞች በጎነት መገለጽ ባይችል የዓለማችን ሚዛን ወደአንዱ እንዳጋደለ ይቀጥል ነበር:: ክፉ አጋጣሚዎች ለበጎነት ማሳያ የመሆናቸው እውነት ደግሞ ቀይ መስቀልን የመሰሉ የሰብዓዊ ተቋማት እንዲወለዱ ምክንያት ሆኗል::
ዛሬ ለዓለማችን አንገብጋቢ ችግሮች ቀዳሚ የሰብዓዊነት ጋሻ የሆነው ቀይ መስቀል ለመመስረቱ መነሻ የሆነው አስከፊው ጦርነትና የሰብዓዊ ስሜቶች እውነታ ነበር:: የሰው ልጅ በራሱ እጆች የሚፈጥራቸው ችግሮች እንዳሉ ሆኖ ክፉ ታሪኮችን የሚሽርባቸው መፍትሔዎችም ከራሱ አይርቁም:: ይህም መልካም ልቦና ባላቸው ወገኖች ድንበር አልባው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ዕውን እንዲሆን አስችሏል::
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው። በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
በመልካምሥራ አፈወርቅ
አዲስ ዘመን ረቡዕ ግንቦት 27 ቀን 2017 ዓ.ም