ወዳጄ ተነፃፅሮ ይከፋል፤ የተራራቀን ማቀራርብ እጅጉን ከባድ ነው። ሰውን የሚያህል ክቡር ፍጡር ከሌላ እንስሳና ቁስ አካል ጋር በተነፃፅሮ ማስቀመጥ ለአስቀማጩ ችግር ለተቀመማጩ ደግሞ ሸክም ይመስለኛል። በሰሞኑ ገጠመኜ ሰው ከሆንነው ከአንዳንዶቻችን ሰው ያልሆኑ አንዳንዶች የተሻሉ ሆነው አገኘሁና ማነፃፀርን ተዳፈርኩ። በሰሞኑ ችግኝ ተከላ ላይ የተሳተፈችውን “ቡቺ”ን የችግኝ ተከላውን ከተቃወሙት ጋር አወዳድሬ ገዝፋ ታየችኝ። የቡቺ የችግኝ ተከላ ላይ መሳተፍ አለመሳተፍ ሳይሆን የአንዳንዶች የችግኝ ተከላውን በጎ ዘመቻ ማጥላላትና የተዛባ አተያያቸውን ቡቺ ከሰራቸው ተግባር ጋር እንዳወዳድር አደረገኝ።
ሰኞ ዕለት የተካሄደው ሀገር አቀፍ በጎ ዘመቻ የተቃረኑ፤ ህይወት የመዝራቱን ጥረት አይተው የነቀፉ መኖራቸውን ሳይ ማያቸው ላይ ጥርጣሬ አደረብኝ። ተቃውሞን ትጠላለህ ወዳጄ? ውዶቼ የምትታዘቡት ታዛቢ ገጥሟችሁ ያውቃል? ራሱ በብዙ የሚተች ተቺስ? ይሰውረን ነው። ተቺው የሚተቸው ጉዳይ በቅጡ ካልተገነዘበማ ራሱ የትችት ርዕስ ሆኖ ያርፈዋል። ተገቢነት በሌለው መልኩ የሚቀርብ ለመቃወምም የማይመች ጉዳይ ሲቃወሙት ማላከኪያው ይከፋል። ውግዘት ውል የሌለው ሲሆን ትሸሸዋለህ። ትችትን ያለ ቦታው ስታገኘው ከትዝብት ከፍ ይልብሀል።
የእውነት ግን ተቀላቅሎንናል፤ አሊያም ደግሞ ተደናግረናል። ስናሳዝን! ምን ነክቶን ነው? ከኛነታችን ጋር የተሳኩ ውብ እሴቶቻችንን ሽርሽር አድረጎ በጎ ምግባር፣ ልምድና እሳቤያችንን ያከሰመው ምን ይሆን? ይሄኔ ነው መፍራት ወገን፤ እኔ በብዙ መስፈሪያ እውነትና ትክክል ያልኩት ወይም ለብዙዎቻችን መልካም የሆነ ነገር በሌሎች መልካም ባይባል አይገርመኝም። ግን ደግሞ ለሁሉም መልካም የሆነ ነገር እውነታውን ባለመረዳት ጥቂት ሰዎች ያለ መነሻ መልካሙን ሲያጠለሹ እታዘባለሁ።
ከጥልሸት ይልቅ ንጣትን መፈለግ፣ ከፅልመት ይልቅ ብርሀንን ወይም የብርሀን ፍንጣቂ መፈለግ እየተቻለ ለምን መልካምን ማጥላት በጎን ማንኳሰስ አስፈለገ? ውዶቼ ይሄማ በጤና አይደለም። ጤናማነት ጤናማ ሀሳብን እውስጥ ማስረፅ አይደለም እንዴ? ጤናማነት ጤነኛ ነገርን አይቶ ማድነቅ፤ ያልተገባን ማውገዝ፤ ነገሮችን በበጎ መመልከት አይደል? ለዚህ ነው የእነዚህን በጎውን አጥይዎች ጤነኝነት የተጠራጠርኩት፤
የችግኝ መትከሉን ዘመቻ የተቃወሙ፤ አረንጓዴነትን የተጠየፉ ሚስኪኖች፤ ጤና የራቃቸው፤ መልካም ነገር ያለተገለፀላቸው መሆናቸው ሲገባኝ አሳዘኑኝ። ሰው እንዴት የሰው እስትንፋስ ማስቀጠልን፤ ህይወት መዝራትን ይቃወማል? ለበጎ ከመጠቀም ይልቅ ለርዕስ በርዕስ ትችትና ነቀፋ የምንጠቀምበት ማህበራዊ ሚዲያ፤ በተለይ ፌስ ቡክ ብዙ አሳየኝ።
እነ “ቡቺ” እንኳን በተሳተፉበት ዘመቻ፤ ከዛፍ ኦክስጂንን ስቦ የቆመ ሰው ለንግግሩና ለእስትነፋሱ ድጋፍ የሆነውን ዛፍ መትከልን እንዴት ይቃወማል? በዘመቻው የተሳተፈን ሰው በምን መስፈርት ሊኮንን ይችላል? በእውነት! “ቡቺ” ግን ደነቀችኝ። እናስ፤ ከእፅዋት የሚገኘውን ኦክስጂን መጠቀም አለመጠቀሟን እንኳን ሳትለይ ታዛዥ ሆና በችግኝ ተከላው ላይ የተሳተፈችው “ቡቺ” ዘመቻውን ከሚቃወሙት በብዙ አትሻልም? የእውነት ውዶቼ ለኔ ቡችዬ ተሽላ ታየችኝ።
እንዲያው በዚህ የችግኝ ተከላ ላይ የተሳተፈችው ብርቅዬ ውሻ የችግኝ ተከላውን ተቃወሙ የተባሉ ሰዎች መኖራቸውን ብተሰማ ምን ትል ይሆን? በእርግጥ ተቃዋሚዎች አሉ መባሉም ላታምን ትችል ይሆናል። እንጂ! ውዶቼ አንዳች የማናውቀው ክፉ ነገርማ ተጠናውቶናል። በጎነትን ማያ መነፅራችንን አስወልቆ የጎደፈ መነፅር አይናችን ላይ ማን ይሆን ያስቀመጠብን?
በዚህ ተፈጥሮን ጠብቆ የማስቀጠል በጎ ተግባር ጭቃ ላይ ተንበርክኮ ነገን የተሻለ ለማድረግ በብሩህ ምኞት ሳይሰስት ጉድጓድ ቆፍሮ፤ አፈር ዝቆ ችግኝ የተከለ ልበ ቀና እንዴት ይንኳሰሳል ጎበዝ? በምንስ ስሌት ስለዚህ መልካም ተግባርና ሥራ መጥላላት ይነሳል? ይሄ መጠቀሙን መጠቀማችን ቀርቶ አለመጠቀማችንን አጉልቶ ባሳየን ፌስ ቡክ የዘመቻው አጥላዮች በጎን ነገር ሲያጥላሉ የእነሱ እንቶ ፈንቶ ተቃርኗዊ ቃላቸው ከማጥለያው አላልፍ ብሏቸው አይተናል። መልካሙ ባጠለሉት በራሳቸው ማጥለያ አልፎ ከመድረሻው ካሰበበት ሲደርስ የእነርሱ ማጥለያ ግን ራሳቸውን ከከንቱ እሳቤያቸው ጋር አስቀርቷቸዋል።
የቀለለውን፤ ሁሉንም የሚያስፈግገውን፤ በጎውን ነገር አስትቶ ጠል አልባሹን ክፋት በምን ይሆን ያላበሰን ጃል!? ውል ጠፍቶብን የማናውቀውን መነካካት ያልተረዳነውን መተንተን ተክነንበታል። የሁላችን የሥራ ዘርፍ ፖለቲካ መቦትለክ ይመስል የምናነሳ የምንጥልው ጉዳይ ሁሉ ፖለቲካ ሆኗል።
ሁሉም ሥራውን ዘንግቶ ፖለቲካውን አቡኩቶ መጋገር ጀምሯል። አውቆ ለሚተገብረው ፖለቲከኛ እንደመተው ተንታኝነትና ተንባይነት ተላምዷል። ይሄ ልምዳችን ብሶብን ነገሮች የተቀላቀሉብን
ይመስላል። ግን እንዴት ውል እናጣለን? የሐሳብና የፖለቲካዊ አቋም ለውጥን፤ ቋሚ ነገርን በምን መስፈርት ይቃወማል?
እስቲ አንድ እውነት ላይ እናውራ፤ ይሄንን የችግኝ መተከል ዘመቻ የተቃወመና ሌላ ትርጉም የሰጠው ሰው የተተከለው ችግኝ ነገ ዛፍ ሆኖ አድጎ ለራሱ የሚሰጠውን ኦክስጅን ንቆ ነው ወይስ ጥቅሙ አልገባ ብሎት? እረ ወገን ለመቃወምም እኮ የምንቃወመውን ነገር መለየት ተገቢ ነው። አንድ ወዳጄ የአረንጓዴ አሻራ ቀን ዘመቻ ተሳታፊ ነበረና ለማስታወሻ ብሎ የተነሳውን ፎቶ በፌስ ቡክ ገፁ ላይ ያሰፍራል። ትላንት ቁም ነገር ለመቀያየር በማለት ከመረጣቸው ጓደኞቹ መካከል የተወሰኑትና “የተለየን ነን፤ ፎቶህ ላይ ያለው ተግባር ለኛ ምናችን ነው? እንደውም አንተ ማድረግህ ኩነኔ ነው፤” ያሉት አስገረሙኝ።
በፎቶው ስር በአስተያየት መልክ አንዱ ባልተገራ የሹፈት ቃላቱ እንዲህ አለው። “ይሄ ማሸርገድ ምን ይሉታል? ብርቃም ሁላ አረንጓዴ አረንጓዴ እያላችሁ መጮህ…” በማለት፤ ማለት ስለሚችል ብቻ ያላቸው፤ ወይም መጻፍ በመቻሉ ብቻ የጻፋቸው፤ ውስጡ ሚዛናዊነት የጎደላቸው ሀሳብና አስተያየቶች በመስጠት ይቀጥላል። እኔ ’ምለው የትኛው ጩኸት ነው በጎው? የችግኝ መተከል ተቃርኖ? ወይስ “ኑ ሀገርን አረንጓዴ እናድረግ፤ መስኩን እናለምልም” ያለው፤
ይሄን የተንሸዋረረ እይታ ለማረም ይመስላል ወዳጄ ከአስተያየት ሰጪው ወረድ ብሎ በተቀመጠው አስተያየት መመለሻ ሳጥን የአላማውን በጎነት ለማሰረዳት ሲሞክር መልሶ ያገኘው ምላሽ “ከመቼ ጀምሮ ካድሬ ሆንክ ባክህ ሰበካህን እዛ ካድሬው አትስበከኝ እባክህ” የሚል ምላሽ መሰጠቱን ስመለከት የአስተያየት ሰጪው ውስጡ በብዙ የሀሳብ መደበላለቆች መሞላቱን አረጋገጥኩ።
እርግጥ፤ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ እስከዛሬ በዘመቻ መልክ ከተሰሩ ሥራዎች በላቀ ሁኔታ መልካም አስተያየትና ተሳትፎ የነበረበት ይህ ሁነት ከበጎነቱ ግዝፈት አንፃር የተፃራሪዎቹን የሐሳብ መዛነፍና ምክንያት አልባነት በጉልህ የሚያመላክት ሆኖ አልፏል። እውነትም እኚህ የአረንጓዴው አሻራ ቀን ነቃፊዎች በዘመቻው ተሳታፊ በጎ ሰሪዎች ተውጠው በበረከቱት ገፆች ቢጥላሉም የእነሱን መልካም ሥራ የማንኳሰስ ሙከራ ግን የሚያስተዛዝብ ነበር።
በቀዝቃዛቀው አየር በሀገር ፍቅር ስሜት ውስጣቸው በሞቀ በጎ አሳቢ ወገኖች ምክንያትም የታሰበው ተሳካ። ዘመቻው ሀገራዊ ጥሪ ስለሆነ፤ ህይወትን የመዝራት፤ እስትንፋስን የመመለስና የማስቀጠል ጉዳይ ስለነበር፤ በሀገር ወዳድ ዜጎች ልብ
ውስጥ የሞቀ ሀገራዊ ፍቅር ነበረና ቅዝቃዜው በሰናይ ተግባር ሞቀ። በመላው ሀገሪቱ ከሊቅ እስከደቂቅ ሕዝብ ወጥቶ በተሳተፈበት አረንጓዴ አሻራ የማኖር ሀገር አቀፍ የችግኝ መትከል ዘመቻ 353 ሚሊዮን 633 ሺ 660 ችግኞች ተተከሉ።
መልካም ነገር ነውና መተግበር አልከበደም። ሁሉን ባሳተፈ መልኩ የተከናወነውን ዘመቻ እነ “ቡቺ”ን ጨምሮ የነገዋን ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ልማት መሰረት የሚጥል ተግባር ሆኖ አልፋል። ይህ የሆነው በአንድ ቀን ነው። ይህ ሁሉ ህይወት የተዘራው በአንድ ጀምበር ለዚያውም በአንዲት ሀገር። በዚህ ህይወት የመዝራት ሂደት ውስጥ የዘመቻውን ትርጓሜ የለወጡ፤ አላማውን በተሳሳተ መንገድ የተረጎሙ አካላት የተሳሳተ እሳቤያቸው ገሀድ ያወጡበትና የተዋረዱበት ገጠመኝ ሆኗል።
በሰፋ ሀገር የተጣበቡ፤ በለማ መሬት የተራቡ፣ በሰዎች ሀገር ሰው የተራቡ ያረገን የኛ እሳቤ በጎ ያለመሆን ነው። ዝቅ የሚያደርግ ክፉ እሳቤ ከኛ ይርቅ ዘንድ በጎነት ላይ አተኩረን፤ መልካምነትን መፈክር አድርገን ዘመን ተሻጋሪ ሥራ ለመሥራት ዝገጁ ብንሆንስ? ያኔ ሀገሩም የበለጠ ይሰፋል፣ መሬቱም ፍሬ ያፈራል፤ ፍቅራችንም ይደምቃል፤ ጎጆአችንም ይሞቃል። አዎን! ያኔ ሁሉም መልካም ይሆናል። ቸር ይግጠመን!
አዲስ ዘመን ሐምሌ 26/2011
ተገኝ ብሩ