እውነተኛ ስሙና ታሪኩ ሳይታወቅ ብዙ ኖረ። ግለ ሕይወቱ እንቆቅልሽ። አይሞቀው አይበርደው። አዛውንቶቹ ‹‹ኬረዳሽ›› ይሉታል። ግድየለሽ ነው ለማለት። የከፋ የሕይወት ውጣ ውረድ ፈተና ችግር ምስቅልቅል ሰዎች እራሳቸውን እንዲጥሉ ትላንትን እንዲረሱ ዓለምን እንዲንቁ ያደርጋቸዋል። ምን ለብሼ ልሳቅ ትላንቱን ለመርሳት በሳቁ ውስጥ የሚሸሸግ ዓይነት ሰው ነው።
ሕይወት በብዙ መድበሎች የተሞላች ተነባ የማታልቅ መጽሐፍት ናት፤ ትጉህ አንባቢ ከተገኘ። እያንዳንዱ ሰው ራሱ መጽሐፍ ነው። የሚነበቡና የማይነበቡ ምልአት ገጾች ያሉት። ምን ለብሼ ልሳቅ በሚገጥመው ነገር ተንከትክቶ ከመሳቅ ውጪ ስለራሱ አያወራም። የተወሰኑ የመንደሩ ተማሪዎች መጠነኛ ፍንጭ ከማግኘታቸው ውጪ ማንነቱ እንቆቅልሽ እንደሆነ ዘልቋል።
‹‹ይሄ እብድ፤ አውቆ አበድ›› የሚሉት ብዙዎቹ በአለባበሱና በአነጋገሩ ነው። እብድ ውስጥ ስንት ቁም ነገር አለ፤ ‹‹አዎን እኔማ እብድ ነኝ፤ ከእናንተ የተሻልኩ እብድ›› ይላቸዋል። እንዲያ ሲል ሰው ሁሉ በሳቅ ያውካካል። ‹‹እብድና ዘበናይ ያሻውን ነው የሚናገረው›› ይሉ የለ የድሮ ሰዎች። ስለምን ለብሼ ልሳቅ ማንነት ሰዎች እርግጠኛ ባይሆኑም የየራሳቸውን ግምት ይሰጣሉ። ከፊሉ ጭቃ እየለወሰ ከሚዘፍነው ‹‹አንቺ ልጅ›› ከሚለው እንጉርጉሮው ተነስተው ‹‹አይ በሆነች ልጅ ፍቅር ተለክፎና አብዶ ነው›› ይላል።
‹‹አይ ፍቅር እንዲህ ራስ አስጥሎ ወፈፌ እብድ ያስመስላል እንዴ፤ አይሆንም አይሆንም፤ ሌላ ነገር ገጥሞት ይሆናል›› ሲሉ ሌሎች ደግሞ አይ ወይ ‹‹ጎበዝ ተማሪ ሁኖ ሳለ በምቀኝነት በመተት አሳብደውት ይሆናል›› የሚሉም አሉ። ሁሉም የሚደመመው ሳይዛነፍ ሥራውን በመሥራቱ ነው። ምርጥ ጭቃ አቡኪና ለሳኝ።
እሱ ብቅ ባለ ቁጥር ‹‹መጣ መጣ›› በሚል ሁሉም ለመሳቅ በመዘጋጀት በነገር ይነካካዋል። ወጋ ወጋ ያደርጉታል። እሱ ምንተዳው ፈጣን ምላሽ ይሰጣል። ወጣት ሴቶች በመካከለኛ ዕድሜ ያሉ እናቶች አዛውንቶች ጭምር ቀልድ አዋቂነቱን ይወዱለታል። ሴቶቹ መልሱን በመናፈቅ ‹‹እናግባህ›› ይሉታል። የዚህ ጊዜ ከት ብሎ ይስቅና ጉልበቴ ጭቃ በማቡካትና በመለሰን አልቋል ‹‹ከእናንተ ጋር ማን ይታገላል›› ይላቸዋል። ቤት ሙሉ ሳቅ ይሳቃል። ግን ‹‹ቆንጆ መሆኔን አውቃለሁ፤ ያውም ባለከረባት ዘናጭ›› ሲላቸው ሁሉም በሳቅ ይዝረከረካሉ። ለመቀለድ ጎተት ሲያደርጉት አንዷን በድንገት አቅፎ ልሳም ይላል። ያኔ የሀገር ሳቅ ይባርቃል። ‹‹ስንታችሁን ላግባ ኸረ ጉድ ነው፤ ምን ለብሼ ልሳቅ›› ይላል።
‹‹እኔ እኔ›› በማለት ልብሱን ሲጎትቱት ይጮሀል። ‹‹ኡኡኡ ኸረ ሊገሉኝ ነው ድረሱልኝ›› እንደማለት። ጨዋታ አዋቂ ሥራውን አክባሪ ነው። ሥራውን ሠርቶ ሲጨርስ ብዙ አይቀመጥም። ቶሎ ለባብሶ በዚያው በተለመደ ሁኔታ ፈጥኖ አካባቢውን ይለቃል። ጠርጣራ ነው። የሚከተሉት ሰዎች እንደሚኖሩ ይገምታል። በአንድ መንገድ አይሄድም። በመጣበት አይመለስም። ያሳብራል። ይቀያይራል። እየሳቀ ይገላመጣል። ምን እንደሚያወራ ባይታወቅም ብቻውን እጆቹን እያወናጨፈ ያወራል። ብቻውን ይስቃል። ኸረ ይቆጣልም። ከራሱ ጋር ግብግብ የያዘ ይመስላል።
ብቻ አልፎ አልፎ ቀረብ ያለ ድምፁን የሰሙ ሰዎች ‹‹በለው፤ በለው፤ እንግዲህ›› ይላል ይላሉ። ወደኋላው ያያል። ደግሞ በራሱ ዓለም እያወራ ፈጠን ብሎ በመዝለል እንደ ሚዳቋ ይስፈነጠራል። እንጣጥ እንጣጥ እያለ ይሄዳል። ይሄ ሰው እራሱም እኮ ትያትር ነው። ምንድ ነው ግለ ምስጢሩ? አጥብቆ የሚሸሸው የሚፈራው እራሱን የጠላበት ወይ የለወጠበት ምክንያት ይኖረዋል። ከእሱ በቀር የሚያውቀው የለም። ማን እንደሚከተለው ይለያል ይላሉ ተከታትለው የሞከሩት ሰዎች።
ከመነን ተነስቶ ሽሮ ሜዳ፤ እዛ አየነው ሲሉ ስድስት ኪሎ ወይንም አፍንጮ በር ሲያሻውም አራዳ ጊዮርጊስ ይከሰታል። አንድ ጊዜ የሚሠራበት ሰፈር አካባቢ የሚያውቁት ጎረምሶች ‹‹ምን ለብሼ ልሳቅ›› ፒያሳ ይሄዳል ይታያል ብለው በፍጹም አልገመቱም ነበርና፤ መሀል ፒያሳ በዛው አለባበሱ ካፌ በረንዳ ላይ ቁጭ ብሎ ሲያዩት ይገረማሉ። እሱ ነው ሌላ በሚል ተደናግጠው ቀረብ ብለው ‹‹ምንለብሼ ልሳቅ ምን ታደርጋለህ›› ፒያሳ ሲሉት ረዥም ሳቅ ሳቀ። ስቆም አልበቃው።
ከጎኑ ካፌው በረንዳ ላይ ዘመናዊና የዘናነጡ ሰዎች ተቀምጠዋል። ወደሰዎቹ ዘወር አለና ‹‹ሉክ ሁዋት ዚስ ቦይስ አር ሰይንግ›› (እነዚህ ልጆች ያሉትን ተመልከቱ) ሲል ሰዎቹ በሳቅ ፈነዱ። አይ የልጅ ነገር ለማለት። አንደኛው በድንገት ‹‹አይ አለማወቅ እናንተ እኮ አታውቁትም፤ እኛም ከስንት ዘመን በኋላ ነው ያገኘነው፤ አረግ አጅሬ›› አለ በድንገት። ‹‹አሳድጋ የምትበላ ድመት የሆነች ሀገር አለ›› ለጠቀና።
‹‹ድንቅ ብለሀል›› አለው ሌለኛው። ስንት ታሪክ ያለው ሰው ነበር እኮ አለና ዝም አለ። ይሄኔ እኔ ታሪክ የለኝም። ታሪክ አታውሩ። ‹‹ዛሬ ሌላ ሰው ነኝ›› አለ ምን ለብሼ ልሳቅ። ከተለያዩ በርካታ ዓመታት የሆናቸውን ሰዎች የለያቸው ካፌው በረንዳ ላይ ከተቀመጡ በኋላ ሲሆን ተነስቶ ለመሄድ ከጅሎትም ነበር። በግድ ይዘው ያቆዩት። በዚሁ መሀል ነው ወጣቶቹ ሲያልፉ ፒያሳ ካፌ በረንዳ ላይ ተቀምጦ ሲያዩት ተገርመው አጠገቡ በመሄድ ያናገሩት።
‹‹ለካስ መንደር መንደሩን እየዞረ የሚሠራው የሚያውቁትን ብቻ ሳይሆን ትላንትን ለመሸሽና ለመርሳትም ነበር። ተው እንጂ ክብረት፤ ተው ተው›› አለው አንደኛው ኮስተር ብሎ። ‹‹የቱን ክብረት የሞተውንና የተቀበረውን ክብረት ነው የምትለው?›› አሀሀሀሀሀሀ አለና አውካካ። ‹‹ክብረት ከሞተ 15 ዓመታት አልፈዋል›› አላቸው። ‹‹እኔ ክብረት አይደለሁም›› ሲል ምን ለብሼ ልሳቅ በጎምዛዛ መልኩ መለሰ። አጠገቡ የተቀመጡት የያኔው ዘመነኞች ሁሉም ያውቁት ነበርና አቀረቀሩ።
ምን ለብሼ ልሳቅ ወደ ወጣቶቹ ዞር ብሎ ‹‹ሰማችሁ›› አላቸው። ‹‹አራዳም ሆነች ፒያሳ እናንተ ሳትፈጠሩ ያቀናናት፤ የዘነጥንባት፤ የደነስንባት፤ የታየንባት፤ መቼ በመጡ የተባልንባት ነበረች። ውቲ ማቲው ሳይፈላ፤ ኩታራው ሳያፍጫጫ፤ ከእኔ በላይ ሰው የለም ሳይል። በነበርትናን፣ ካስተርና በነጀምስ ቦንድ ፊልሞች ነበር የምንዝናናው። አምፒር፤ ኢትዮጵያና ሲኒማ አድዋ። አይ ዘመን አይ ጊዜ አለና ተንገፈገፈ። እንደገና ተንፈቅፍቆ ሳቀና ዝም አለ። ‹‹ፒያሳ መታየት ብርቅ ነው እንዴ!›› ሲል ወጣቶቹን ጠየቀ።
እብድ ፒያሳ ምን ያደርጋል ነው የወጣቶቹ አግድም ጥያቄ። ገብቶታል። ‹‹ግን እኮ ለእብዱም ሀገሩ ነች›› አላቸው። ‹‹ይሄ ሰው ብዙ ታሪክ ያለው ሰው ነው እንደዚህ የሆነው ከባድ ፈተና ገጥሞት መሆን አለበት›› አለ አንዱ ወጣት። አንዳንዱ ሰው ብዙ ያየ፤ ብዙ ያሳለፈ፤ በሆነ አጋጣሚ የሕይወት ዕጣ ፈንታው የተቀየረ፤ አግኝቶ ያጣ፤ ወይ በክፉ ኀዘን የተመታ፤ በክፉ ፈታኝ ችግር ውስጥ በማለፉ ውስጡ የተጎዳ የሕይወቱ መስመር የተቀየረ ይሆናል። እንዲህ ዓይነት እልፍ ሰዎች አሉ። በየመንደሩ። በየሰፈሩ።
‹‹ሰው ራሱ ብዙ ያልተነበበ መጽሐፍ ነው›› ያለው ማን ነበር። ነውኮ ሰው ራሱ ከአንድ ትልቅ ቤተ መጽሐፍት በላይ ነው። የድሮው አራዳ፤ ፒያሳ እነ እሪ በከንቱ፤ ባሻወልዴ ችሎትና ሌሎችም የያኔው ዘመን ስልጡንና አራዳዎች መገናኛና መዝናኛ ነበሩ። እነ ሙሉቀን መለሰ ዘፈን የጀመሩበት የእነ አሰገደች አላምረው መጠጥ ቤት፤ እነ ገዳም ሰፈር ፤ ውቤ በረሀ በዛን ዘመን ብዙ ታሪክ የተሠራባቸው ብዙ የተዘፈነላቸው የተዘመረላቸው እነ ቡጊ ቡጊና ማሪንጌ ቻቻ የተደነሰባቸው። ደናሾቹ ደግሞ የያኔው ዘመን ጌቶች እነ ምን ለብሼ ልሳቅ ነበሩ። ‹‹የፊተኞች ኋላ፤ የኋለኞች ፊት›› ቆመው የሚታዩባት ድንቅ ሀገር ኢትዮጵያ።›› አለ ከተቀመጡት ሰዎች አንደኛው።
ጉድ እኮ ነው ሰውና ዘመን፤ ዘመንና ሰው ሲፈራረቁ። ‹‹ክብረት ጫኔ›› ብሎ ጠራው ምን ለብሼ ልሳቅን። በድንገት አቤት አለና ክብረትነቱን አረጋገጠ። ልጆቹ የምን ለብሼ ልሳቅ እውነተኛ ስም ታወቀ አሉና ተደመሙ። ‹‹እኔ ክብረት አይደለሁም ማለት አይደለሁም ነው›› አለና ዳግም ለማስተባበል ሞከረ።፡ ‹‹እኔ ጭቃ ረጋጭና ለሳኝ ነኝ። ስሜም ምን ለብሼ ልሳቅ ነው›› አላቸው። ክብረታችሁን ፈልጉት።
‹‹የዛሬው ጭቃ ለሳኝ የትላንቱ ዘናጭ፤ የመሀል ከተማው አራዳ፤ ዘልቆ የተማረው፤ ፍቅርና ጨዋታ ወዳዱ፤ የለውጥ መሪና ዘማሪ፤ በመንግሥት ላይ ያሳምጻል ተብሎ በጸጥታ ሚኒስቴር የትም ቦታ ሥራ እንዳይቀጠር በንጉሠ መንግሥት የታገደው ክብረት ጫኔ›› ሲል ጠራው ካፌው በረንዳ ከተቀመጡት አንዱ ደገመና።
ቆመው የነበሩት ወጣቶች ማመን አቅቷቸው ደነገጡ። ‹‹እጅግ ብዙ ፈልገንህ ቦታህ አልታወቀም። በስምህ ድሮ የሚያውቅህ ሰው ብንጠይቅ አልተገኘህም›› አሉት ባልንጀሮቹ። ‹‹እኔ እኮ ክብረት ጫኔ አይደለሁም። ተሳስታችኋል። ሞቶ ስለተቀበረ ሰው አታውሩ። እኔ ምን ለብሼ ልሳቅ ነው ስሜ። ሥራዬም ጭቃ አቡኪና ለሳኝ ነው›› ሲል ደገመላቸው። ‹‹የምትሉትን ሰው አላውቀውም። ካለ ፈልጉት›› ደገመው። ‹‹ዓለም እንዲህ ናት ወሽካታ፤ ዘብራቃ፤ ቀጣፊ፤ አታላይ ፤አማላይ፤ ዝሙተኛ፤ ስቃ ገዳይ፤ ሰው በላ፤›› ሲል ተናገረና ለመሄድ ከተቀመጠበት ተነሳ። እባክህ ቢሉትም በጄ አላለም። ትቷቸው ሄደ።
አዲስ ዘመን ሐምሌ 25/2011
ወንድወሰን መኮንን