በዩኒቨርስቲ ትምህርት ቆይታችን ከወሰድናቸው ትምህርቶች ውስጥ አንዱ የተግባቦት ትምህርት/ Communication/ ነው፡፡ በወቅቱ ትምህርቱን የሚሰጡን መምህር አንድ ቀን አንድ የክፍል ስራ አሰሩን፡፡ መረጃዎች ከአንዱ ወደሌላው ሲተላለፉ በመካከል የሚያጋጥማቸውን ፈተናና እንቅፋት ለማሳየት የተጠቀሙበት ተግባራዊ ስራ ነበር፡፡ በዚህ መሰረት በክፍል ውስጥ የምንገኘውን ሃያ የምንሆን ተማሪዎች ደርድረው አንድ ዓረፍተ ነገር ሃሳብ ለመጀመሪያው ተሰላፊ ተማሪ ለብቻው ነገሩት፡፡ ከዚያ በኋላ እሱ ለሚቀጥለው ሰው ሃሳቡን እንዲስተላልፍና እንዲህ እንዲህ እያለ መረጃው የመጨረሻው ሰው ጋ ደርሶ እዲመለስ የክፍል ስራው መሰረታዊ አካሄድ ነበር፡፡
በጣም የሚገርመው በመጀመሪያ ከዋናው ባለቤት የተላለፈው መረጃ በሃያዎቹ ተማሪዎች ውስጥ አልፎ የመጨረሻው ሰው ጋ ሲደርስ ከመነሻው ሃሳብ በተቃራኒ መልዕክት ያዘለ ነበር። ይህም የሚያሳየን መረጃዎች በሚተላለፉበትም ሆነ መረጃውን በሚቀበለው መካከል በርካታ ችግሮች መኖራቸውን በተጨባጭ ያሳዩበት ነበር። ይህንን ሃሳብ ያነሳሁት ስለተግባቦት ለማውራት አይደለም። ይልቁንም ስለማዳመጥና መናገር የታዘብኩት ጥቂት ነገር ለማለት ነው፡፡ እንደው አንዳንድ ጊዜ ሰብሰብ ብላችሁ ስትጫወቱ ወይም በተለያዩ የውይይት መድረኮች ምን ታዝባችሁ ይሆን፡፡
እስኪ በቅድሚያ በስብሰባ ላይ ስለሚታዩ አንዳንድ ድርጊቶች ላንሳ፡፡ መቼም አሁን አሁን ስብሰባ የአገራችን ባህል እስከሚመስል ድረስ ከከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እስከ መንደር፣ ወይም ከዓለም አቀፍ ጉባኤ እስከ እድር ስብሰባ በየቀኑ በርካታ ስብሰባዎች ሲካሄዱ መመልከት አዲስ ነገር አይደለም፡፡ በተለይ አገልግሎት ሰጪ በሆኑ ተቋማት አገልግሎት ፍለጋ ሄደን የምንፈልጋቸው ኃላፊ ወይም ባለሙያ ስብሰባ ላይ ናቸው የሚል መልስ ማግኘትም አዲስ ነገር አይደለም፡፡ ምክንያቱም ስብሰባ የየዕለቱ የስራችን አካል ነውና።
እኔ በበኩሌ ከስብሰባ የሚያላቅቀን ምን ህግ እንደሚመጣ አላውቅም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትራችንም በተደጋጋሚ ስብሰባ ይቀነስ፣ ከሆነም በአጭሩ ይሁን በሚል በተደጋጋሚ ሲናገሩ ቢደመጡም ተግባራዊ ሲሆን አይታይም፡፡
ታዲያ እነዚህ ስብሰባዎች መካሄዳቸው እንደተጠበቀ ሆኖ ምን ያህል ለውጥ የሚያመጡ ናቸው የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡ በስብሰባ ውጤታማነት ላይ ጥናት የሚያደርግ አካል ቢኖር ድምዳሜው “ምንም ፋይዳ የሌለው” የሚል መደምደሚያ ላይ እንደሚደርስ እገምታለሁ፡፡
በሌላ በኩል በስብሰባ ላይ የምንታዘባቸው በርካታ ባሕርያት አሉ፡፡ እኔ ካጋጠሙኝ ውስጥ ጥቂቱን ላንሳ፡፡ አንዳንድ የስብሰባ ተሳታፊዎች ዋነኛ ዓላማቸው በስብሰባው ላይ መሳተፍ ሳይሆን በስብሰባው ላይ መተንፈስ ነው፡፡ በዚህ የተነሳ ስለስብሰባው ዓላማ ጉዳያቸው አይደለም፡፡ በዚህ የተነሳ እነሱ የሚያነሱት ሃሳብና ተሰብሳቢው ሲያነሳ የቆየው ሃሳብ ፈጽሞ አይመሳሰልም፡፡ የሚገርመው ደግሞ አንዳንድ ስብሰባን የመምራት ብስለት ያለው መሪ ካልተገኘ ሁሉም በፈለገው መንገድ የሚጓዝ መሆኑ ነው፡፡
በአንድ ወረዳ ውስጥ ስላለ የፀጥታ ችግር እየተወራ ስለዓለም አቀፍ አሸባሪነት ማብራሪያ የሚሰጥ፣ ስለዋጋ ግሽበት እየተነገረ ስለ ማክሮ ኢኮኖሚ የሚተነትን፣ ወዘተ ብዙ ነው፡፡ በዚህ የተነሳ ከስብሰባው አንድም ፍሬ ነገር ሳይያዝ ስብሰባው የሚጠናቀቅበት አጋጣሚ ይበዛል፡፡
አንዳንዱ ደግሞ ወደ ስብሳባ የሚመጣው ለመናገር ብቻ ነው፡፡ በዚህም መሰረት በመጀመሪያ ስለስብሰባው አጠቃላይ ሁኔታ ምንም ግንዛቤ ወይም ፍላጎት አይኖረውም፡፡ በዚህ የተነሳ ሰብሳቢው እድል ሲሰጡ እጁን ተሸቀዳድሞ በማውጣት የመሰለውን ሃሳብ ይናገራል፡፡ ከዚያ በኋላ ለሚሰጠው ምላሽም ሆነ ለሌሎች ተናጋሪዎች ሀሳብ ደንታ የለውም፡፡
በአንድ ወቅት የሚገርሙኝ ሁለት የስብሰባ ተዋናዮች ነበሩ፡፡ እነዚህ የስብሰባ ተዋናዮች በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች ናቸው። እኔም በተለያዩ አጋጣሚዎች የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች በሚሳተፉባቸው ስብሰባዎች ላይ ለመታደም እድሉን አግኝቼ አውቃለሁ፡፡ በነዚህ አጋጣሚዎች ታዲያ እነዚህ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች አብዛኛውን ጊዜ በስብሰባው የሚገኙት አርፍደው ነው፡፡ ይህ ድርጊታቸው ሁልጊዜ ይገርመኛል፡፡ እውን ስራ እየበዛባቸው ነው? ወይስ ሆን ብለው ነው የሚያረፍዱት? የሚለው የዘወትር ጥያቄዬ ነበር፡፡
አንዳንድ ጊዜ ከመድረክ የሚነገሩ ሃሳቦች ወይም የመወያያ ነጥቦች ከቀረቡ በኋላ በስብሰባው ላይ የሚገኙበት አጋጣሚም ብዙ ነው፡፡ ነገር ግን የመድረኩ ሃሳብ አልቆ ሰብሳቢው ለተሳታፊው ሃሳብ እንዲሰጡ እድል ከሰጡ ከነዚህ አመራሮች የሚቀድም አንድም ተሳታፊ አይኖርም፡፡ ገናሰብሳቢው አሁን ደግሞ ሃሳብ ያላችሁ ሲሉ እጃቸውን ሰቅለው እድሉን ይወስዱና ለረጅም ሰዓት ያወራሉ፡፡
ታዲያ እኔን የሚገርኝ እነሱ የመጡት ዋናው ጉዳይ ከተነገረ በኋላ ነው፤ እንዴት ነው እንዲህ የሚያወሩት የሚለው የዘወትር ጥያቄዬ ነው። ከዚያ በኋላ ደግሞ የሌላውን ሃሳብ የማዳመጥ ምንም ፍላጎት የላቸውም፡፡ የራሳቸውን ሃሳብ ከጨረሱ በኋላ ወዲያው ሞባይላቸውን መነካካት/ በግምት ፌስቡክ መላላክ/ ይጀምራሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜም ስልክ እደተደወለለት ሰው ሞባይላቸውን ጆሮአቸው ላይ ለጥፈው ከአዳራሽ ይወጣሉ፡፡ ታዲያ እነዚህ ሰዎች የመናገር እንጂ የማዳመጥ ፍላጎት እንደሌላቸው አትገነዘቡም?
ሌሎች ደግሞ አሉ፤ ለመናገር ካልሆነ ለማዳመጥ ፈጽሞ ትዕግስት የሌላቸው፡፡ እንዲህ አይነት ሰዎች በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ መናገር የዘወትር ልማዳቸው ነው፡፡ በዚህ የተነሳ የሰውን ሃሳብ የመስማት ፍላጎታቸው የተዘጋ ነው፡፡ ታዲያ ከነዚህ ሰዎች ጋር እንዴት መግባባት ይቻላል የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ ነው፡፡ ምክንያቱም እንዲህ አይነት ሰዎች ለመናገር እንጂ ለመስማት ዝግጁ አይደሉምና፡፡
የሰው ልጅ በሃሳብ ለመግባባትና አብሮ ለመኖር በቅድሚያ በሃሳብ መግባባት አለበት፡፡ የመግባቢያ ዋነኛው መንገድ ደግሞ አንዱ የሌላውን ሃሳብ በማዳመጥ ነው፡፡ አንድ ሰው ከመናገር በስተቀር ለመስማት ዝግጁ ካልሆነ ለመግባባት አዳጋች ይሆናል፡፡ እንዲህ አይነት ባህርያት ትዳርን ሊያፈርሱ፣ ከዚያም አልፎ ሃገር ሊያበጣብጡ ይችላሉ፡፡
ለምሳሌ በአሁኑ ወቅት በአገራችን በተለያዩ አካባቢዎች ለሚከሰቱ አለመግባባቶችና ግጭቶች ዋነኛው መንስኤ ቁጭ ብሎ ያለመነጋገርና በሃሳብ የበላይነት ያለማመን ያመጣው ችግር ነው። ሰዎች በመነጋገርና በመተማመን የሚያምኑ ከሆነ ማንኛውንም ችግሮቻቸውን ለመፍታት አይቸገሩም፡፡ ይህ ሳይሆን ሲቀር እኔ ብቻ ልናገር አንተ አዳምጥ ወይም ያንተን ሃሳብ አልሰማም የሚል አስተሳሰብ ወንዝ አያሻግርም፡፡
ማዳመጥ ማለት የምንሰማውን ሁሉ መውሰድ ማለት እንዳልሆነ ልብ ልንል ይገባል፡፡ ማዳመጥ ሲባል ከግራና ቀኝ የሚነገሩ ማናቸውንም ነገሮች መውሰድና የማይጠቅመንን መጣል ማለት ነው። ከዚያ በዘለለ ግን በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች ሁሉ የምንሰማውን ነገር ወስደን ትክልል ነው ማለት ከስህተት መንገድ የሚወስደን በመሆኑ ልብ ልንል ይገባል፡፡
አዲስ ዘመን ሐምሌ 22/2011
ወርቁ ማሩ