እንዴት ያስቀናል! ምኑ? አላችሁኝ፤ የሰማሁት ነገር። ብዙ ሰዎች ስላችሁ የኢኮኖሚ አቅማቸው ደህና የሆኑትን ማለቴ መሆኑ ይያዝልኝ። የእረፍት ጊዜያቸውን ለማሳለፍ ወጣ ማለትን እንደ ባህልም ልበለው ልማድ ተያይዘውታል። የሀገር ውስጥ ቱሪስት በመሆን የተለያዩ ታሪካዊና ሀይማኖታዊ ስፍራዎችን በመጎብኘት ላይ ናቸው። ሀገርን ማወቅ ራስን ማወቅ አይደል? ያወቁትን ደግሞ ለማያውቁት በመንገር ሀገርን ማስተዋወቅ ደስ ይላል። እኔም በስራ አጋጣሚም ቢሆን ብዙዎቹን የቱሪስት መስህብ የሆኑ ስፍራዎች
የመጎብኘት እድሉ አጋጥሞኛል፤ ባየኋዋቸውም ተደስቻለሁ። እነሆ ለንባብ ያልኳቸውም እንዲሁ አሉ እና ስለታሪካዊ ስፍራዎች ማለቴ በሀገር ውስጥ ስላሉት ሲነሳ ለብዙዎቹ አዲስ አልሆንም። እኩል በማውራት፣ያወቅኩትን ለማሳወቅ ያህል እሞክራለሁ።
የክረምቱን የተማሪዎች የእረፍት ጊዜ ምክንያት አድርገው ወዳጆቼ ከነሙሉ ቤተሰባቸው ታላቋን ሀገር፣ ብርቅ እና ድንቅ የሆነችውን፣ለብዙዎች ኢትዮጵያውያን ስደተኞች መኖሪያና የእንጀ ራቸው ማዕድ የሆነችዋን ሀገረ አሜሪካን ለመጎብኘት ወጣ ብለው ነበር። ኧረ እንዳውም
ትንሽ እንጥፍጣፊም እስከ እኛም ዘልቋል። እና እላችኋለሁ ወዳጆቼ ሲመጡ በኢትዮጵያውያን ባህላችን እንኳን ደህና መጣችሁ መባባሉ አለ አይደል? ይሄንኑ ስንባባል ምን አለችኝ መሰላችሁ “ አሜሪካንን እንዴት አድርገው ሰርተዋታል! እንዴት ውብ ናት ! የምታወጪላት ነገር እኮ የለም… መቼም ሁኔታዎች ቢፈቅዱ ሁሉም ሰው ሊያያት የሚገባት ሀገር ናት። “አለች አድናቋቷ ከቃላትም በላይ በ”አክሽን” የተደገፈ ጭምር በመሆኑ ምን ያህል እንደመሰጣት እኔ ከእሷም በላይ ውስጧን እያነበብኩ ቆየሁ ። አድናቆት ብቻም ሳይሆን በአዕምሮዬ የሚቀር ስራም ትታለችና እሱን በማውጣትና በማውረድ በቁጭት ወደ ራሴዋ ኢትዮዽያ መመለስ ስራዬ ሆነ።
እኔም አልኩ እውነት ግን አሜሪካንን ማን ነው የሰራት?። ከራሷ ተርፋ ለዓለም ህዝብ ሁሉ እንድትተርፍ አድርጐ። የኛዋን ሀገርስ እንዲህ ማድረግ ለምን ተሳነን? ብቻ ብዙ ጥያቄ ማንሳት ይቻላል። በእርግጠኝነት ለመናገር አሜሪካንን የሰሯት አሜሪካኖች ናቸው ይሄንን በድፍረት መናገር ይቻላል። ይሁንና ዛሬም አሜሪካኖች ሀገራችንን ሰርተናታል ብለው ና ባለው ነገር ረክተው አልተቀመጡም፤ ሩጫ ላይ ናቸው። ሰዎች ያልደረሱበት ለመድረስ፣ አዳዲስ አስደናቂ ቴክኖሎጂን ለመፈልሰፍ፣ … ብቻ ስራ ላይ ናቸው። ከሀያልነታቸው ከፍ እንጂ ዝቅ ላለማለት ከተፎካካሪዎቻቸው ጋር በስፖርት አባባል ስገልጸው አንገት ላንገት ተናንቀዋል። በማንም በምንም መልኩ ላለመበለጥ ይለፋሉ። ይለፋሉ ስል ከተራው ሰው ጀምሮ ሁሉም በሚያስብል መልኩ በስራ ጊዜያቸውን ያሳልፋሉ፤ ሁሉም የራሱን ሀላፊነት ለመወጣት የራሱን ኑሮ ለማሸነፍ ይታትራል፤ ምን እነሱ ብቻ የእኛም ሀገር ስደተኞች በዚሁ መስመር ገብተዋል። የስራ ምርጫ የሚባል ነገር አይታሰብም፤ አንድ ስራ ብሎ ራስን መወሰን የለም። ገቢ መደበቅ፣ ግብር ማጭበርበር አይታለምም። በዚሁ የእነሱ ስርዓት ውስጥ ገብተው ነው ኑሮን ለማሸነፍ የሚሮጡት። ለእኛም ቢሆን የሚደጉሙን የማይገለጹ ስራዎችን ሁሉ ሰርተው ፤ እንቅልፍ አጥተው ከለፉበት ቆንጥረው ነው። እነሱ በለፉበት ተደጓሚ ፈታ ብሎ እየኖረ ነው ብል መሳሳት አይሆንብኝም። ይህን የምለው ከማየው ተነስቼ በመሆኑ በክፉ አትቁጠሩት።
እኛስ ብዬ አንጠልጥዬ የተውኩትን ሀሳብ ዳግም አነሳሁና በሁሉም ውስጥ ሆኜ ራሴን ታዘብኩት። ለስራ ሳይሆን ለወሬ የምንሰጠው ጊዜ ታየኝ፣ የምንሰራበትን ሳይሆን በማህበራዊ ሚዲያ ላይ ተጥደን የምንቆይበትን ሰዓት አስታወስኩ፤ ሰርተን ሳይሆን የሌሎችን ስራ የምናጎድፍበትን አጀንዳ ሁሉ አሰብኩት፤ ስራ መረጣ፣ አቃቂር ማውጣት… ብቻ የምታዘበውን ሁሉ ብታዘብ ቦታም አይበቃምና የእኛ ነገር! የእኛ ነገር ነው አልኩ። ስንፍና፣ ምቀኝነት፣ ሸፍጥ…ሁሉ በፊቴ ተደቀኑ።
በሀሳብ ዋና ተጠምጄ፤ ጠመድኳችሁ አይደል። ልመለስ ወደ ወዳጄ ወግ” እዛኮ የበላሽውን፣ የለበስሽውን፣ የምትሰሪውን፣ የምትነጂውን መኪና፣ የምትኖሪበትን ቤት… ማን አይቶት ማን ስለማን ትዝ ብሎት ብቻ ሩጫ ነው፤ ማን ትሆን ወይም ምን ትሆኚ ምናልባት የደህንነት ባለሙያና ጉዳዩ የሚመለከተው የስራ ክፍል ይከታተል ይሆናል እንጂ በግለሰብ ደረጃ ማንም ማንንም አያውቅም። ለማወቅም አይፈልግም፤ እንግዳ መጣብኝ ዘመድ ሞተብኝ የሚል ጣጣ ፈንጣጣ ሰበባ አስባብ የሚያደምጥም ስራ የሚፈታም የለም። ምክንያቱም ለዚህ የሚሆን ሰዓት የለማ። ሁሌ ስራ ነው፤ ስራን ማሸነፍ ለመኖር መስራት ካልሆነ ኢንሹራንስ፣ ታክስ፣ የቤት ኪራይ፣ ትምህርት ቤት ክፍያ … ከየት መጥቶ፤ ሁሉም በሩን ከፍቶ በሰዓቱ ይጠብቃልና ይሄንኑ በሰዓቱ መዝጋት የግድ ይሆናል። ይህንን ማሸነፍ ያልቻለ የሚሸከመው የለምና ዕጣው ጎዳና ነው። በቃ ይሄው ነው ኑሮ።” ሁሉንም አደመጥኩ።
አሁንም ጥያቄ አነሳሁ “የኛን ሀገር ማን ይስራት?” ስል። አንዷ ጓደኛዬ ይሄንን ሀሳብ በኮምፒውተሬ ሳፈስ ድንገት ከች ብላ ርዕሱን አየች። “ ኢትዮጵያን ማን ይስራት!” ስትል ከእኔ መልስ የምትሻ ይመስል መልሳ ጠየቀች አዎ ማን ይስራት ደገምኩ በቃላት ጥያቄዬን እሷም መለሰች “ሀገር ወዳድ፣ ልባምና አርቆ አስተዋይ ሰው” ስትል። እውነት ነው። እንዲህ ያሉ ሰዎች ያስፈልጉናል ፤ እንዲህ አይነት መሪዎች ያስፈልጉናል። እንደነዚህ ያሉት ይበዙልን ብለን እንጸልያለን ።
እኔ ግን ከዚህ ትንሽ ልለይ ፍቀዱልኝ። ኢትዮጵያን መስራት ያለብን ሁላችንም ነን። እኔ፣ አንተ፣ አንቺ፣ እናንተ እነሱ ሁላችንም ነን ሀገራችንን ልንሰራት የሚገባው። መቼም በዚህ ሀሳብ የሚስማሙ እንዳሉት ሁሉ አንስማማም ብለው እጃቸውን የሚያወጡ አይጠፉም። ይሄንን ለሚሉም መድረኩ ክፍት ነው። ዲሞክራሲን የምንለማመመደው ከዚህ ጀምሮ አይደል? የሌላውንም ሀሳብ መስማትና ማክበር ስንችል፤ በግድ ግን ሀሳቡን መቀበል ወይም መተግበር አይጠበቅብንም ፤ የምንተገብረው አብዛኛው የተስማማንበትን ለህዝባችንም ለሀገራችንም ጠቃሚ የሚሆነውን ነው። ሀገራችንን አሜሪካ የደረሰችበት ሊያደርስ በሚችለው ሀሳብ። አቤት የእኔ ነገር ከርዕሰ ጉዳዬ ወጣሁ አይደል፤ ልመለስ ወደ ጉዳዬ ።
እናም ኢትዮጵያን የምንሰራት ሁላችንም በያለንበት ደረጃና ሙያ ያለብንን ሀላፊነትና ግዴታ በተገቢው መንገድ፣ በቅንነትና በታማኝነት መወጣት ስንችል ነው። ማለቴ ተማሪው በትምህርት ቤት ማድረግ የሚገባውን መማር፣ የትምህርትና የትምህርት ቤቱን ስርዓት ማክበር ሲችል የሚጠበቅበትን ትምህርት ካለኩረጃ፣ ከመምህራኑ ጋር ሳይሞዳሞድ በራሱ ጥረት ማለፍ ሲችል ነው።
ነጋዴው ስል ሀቀኛውን፣ ግብር የማይሰውረውን፣ ደረሰኝ የማይደብቀውን፣ ገቢውን የማይሸሽገውን፣ በወቅቱ ግብሩን የሚከፍለውን ለማለት አይደለም። ከዛ ወዲህ ያለውን ማለቴ መሆኑ ይያዝልኝ። በኮንትሮባንድ፣ ሰነድ በመደበቅ፣ በማጭበርበር… የሚጠረጠረውን የሚያዘውን ማለቴ ነው። ይሄ ሀገሩን እየሰራት ሳይሆን እያፈረሳት ነው።
የመንግስት ሰራተኛው ሀገሩን የሚሰራት መንግስት የጣለበትን ሀላፊነት ሳይሸራርፍ ሲሰራ ነው። ዘመድ አዝማዴ ጎሳዬ ሳይል ሁሉንም እኩል ሲያገለግልና መታወቂያ ካለሙስና መስጠት ሲችል ነው። የስራ ሰዓቱን ሲያከበር እና ለስራው ብቻ ሲያውል የተገልጋይ ክብር የሚሰማው በማገልገሉም ደስተኛ የሆነ እሱ ሀገሩ ስትሰራ ማገርና ሚስማር አቀብሏል። ሌላውስ ካላችሁ ሁሉ አይዘረዘር ሆኖብኝ እንጂ ተልኮውን በሚገባ የፈጸመ ሁሉ ሀገሩን ሰርቷታል። ሀገርን መስራት ማለት እንዲህ ነው። የአሜሪካኖችን አገር አሜሪካን እያልን ብናቆለጳጵሰውና ብንመኘው የሚሆን ነገር የለም። እንዳልነው ሰርተው ጥረው ግረው ነው ሀገራቸውን ሀገር ያደረጓት።
እኛም እስኪ ወደ ልቦናችን እንመለስና ማንም ተነስቶ አፈርሳታለሁ የሚላትን ኢትዮጵያ ሀገራችንን ከሸክላ የተሰራች እንስራ እንዳይደለች እናሳይ። እናፍርሳትና እንበታትናት የሚለውን መጥፎ እሳቤ ትተን ኢትዮጵያን እንዴት እንስራት ብለን እንነጋገር! ከእኛ ተርፋ ለሌሎች የምትበቃ አድርገን መስራቱ ለምን ተሳነን ? ራሳችንን እንመርምር! አበቃሁ!
አዲስ ዘመን ሐምሌ 21/2011
አልማዝ አያሌው