እንደተለመደው ባለፈው ረቡዕ በምሳ ሰዓት ወደ ሰራተኞች ክበብ /መዝናኛ/ ሳመራ ለብዙ ዓመታት ለመዝናኛ ክበቡ ግርማ ሞገስ በመሆን ሰራተኛውን ከፀሐይ ከልለው ኦክስጂን ሲመግቡ የአካባቢውን ተፈጥሮ መልኩን ሳይቀይር እንዲቀጥል ብርቱ ትግል ሲያደርጉ የነበሩ ሁለት የፅድ ዛፎች በጋራ ተቃቅፈው ተገንድሰው አገኘኋቸው። ከዘመኑ ሰው የተሻለ በሚመስል ጥምረት በአንድነት ተያይዘው ወደቁ። እንደው ምን ይሆን እንዲህ ያስተሳሰራቸው በሚያሰኝ አብሮነት ተቃቅፈው በሚያስቀና አብሮነት ተያይዘው ከመሬት ደረሱ።
እዚያ ቦታ የተገኘሁት፤ ምሳ ለመብላት ነው። ብቻዬን ነኝ፤ ዛፎቹን ስመለከት አንዳች ነገር በውስጤ ተፈጠረ። ዛፎቹ በአብሮነት ከኔ ተሽለዋል። አብረው ኖረው አብረው ተከንብለዋል። እኔ ብቻዬን ዛፎች ግን ሁለት ናቸው። እኔ ቆሜ የወደቁት ዛፎች ከኔ የተሻሉ መሰሉኝ። ውዶቼ ይሄ ነገር እንዴት ነው? ግለኝነታችን፣ መነጠላችን የእርስ በእርስ መደጋገፍና አብሮ የመቆም ልምድና ጥሩ እሴታችን የት ሄደ?
ዛፍ ሲወድቅ ብዙው ሰው የየራሱን መላምት ይሰጣል። ትልቅ ዋርካ ሲገነደስ በባህላችን የሚሰጠው ትርጓሜ ይከብዳል። እኔ ግን በመስሪያ ቤቴ የተገነደሱት ትልልቅ የፅድ ዛፎች ከራሴ አስፍቼም ከማህበረሰባችን አሁናዊ ተግባርና ሁነት ጋር አገናኝቼ አየሁት። የኛ መነጣጠል ከነሱ ጥምረት የኛን ግለኛ መሆን ከዛፎቹ በጋራ መውደቅ ጋር አመሳከርኩት። የኛ ሰውነት ከዛፎቹ ዛፍ መሆን ጋር አነካካሁት። የዛፎቹ ዛፍ ሆነው መገኘት አስምሬ፤ የኛ የሰዎቹ ሰው መሆን ላይ ስብዕና መለበስ ላይ ጥያቄ መጠየቅ ፈለኩ።
የዛፎቹ ተያይዞ መውደቅ ከዛሬ ነባራዊ ሁኔታዎች ጋር አዛመድኩ፤ ይህ ንፅፅራዊ ምልከታዬን አሰፋሁት። ከማህበረሰባችን የዛሬ እውናዊ ህይወት ጋር አነፃፀርኩት። ዛሬ ላይ የምናሳየው አብሮ የመቆምና የእርስ በእርስ ትብብር በኖ ታየኝ። የእርስ በእርስ መረዳዳትና አብሮነታችን ተሸርሽሮ ግለኝነት ሰፍኖ ስለራስ እንጂ ስለሌላው ምን አገባኝ ወርሶናል።
ኧረ ጉድ ነው! ከዛፎቹ አንሰን ተገኘን ማለት ነው? ተቃቅፈው ፍቅር እስከ ማገዶነት ካሉት፤ አብረን ኖረናል ነገ አልተፈቀደልንም አብረን እንውደቅ ካሉት ዛፎች የማንሻል ነን ማለት ነው። በነገራችን ላይ ዛፎቹ ሳይቀዳደሙ እንደተቃቀፉ በጥላቸው እንዳይደርቅ ለብዙ ዓመታት ጥላ ከለላ የሆኑለት መሬት በክብር ተቀብሏቸዋል።
አቤት ዛፎቹ እንደው አንደበት ቢኖራቸው ስንቱን በነገሩኝ። የዛሬን አያድርገው ዛፎቹ ከመገንደሳቸው በፊት በሻይና በምሳ ሰዓት እስሩ ቁጭ ብለን ምሳ በልተን ቡና ስንጠጣ የበዛ ያልረባ ወሬና ጥቂት ቁም ነገር ተለዋውጠናል። የመዝናኛችን ግርማ ሞገስ የነበሩት ዛፎች ከተገነደሱ ቀን ጀምሮ ወደ መዝናኛው ሳመራ አንዳች ነገር የጎደለ ያህል ይሰማኝ ጀምሯል። በእርግጥም ለመዝናኛው ባለውለታ ናቸው። ምን ዋጋ አለው? ከቀናት በኋላ አንድ ፈላጭ ለማገዶነት ሲነርታቸው አየሁ። ዛፎቹ አብረው አድገው አብረው ወድቀው በጋራ ሊማገዱ በሂደት ላይ ናቸው።
የክበቡ መዝናኛ ግቢ ውስጥ የጣራን ያህል ተንዠርግገው ዘመናት የቆዩት ዛፎች ስንቱን ሰው ታዝበው ይሆን? ደግነቱ ኢትዮጵያዊ የፅድ ዛፎች ናቸው። ትዝብታቸው አይበዛም፤ እንኳን የፈረንጁ አልሆኑ። የሀበሻ ፅዶች ስለነበሩ ሀሜት የለመዱና ስለሀሜትም ግድ የሌላቸው ሊሆኑ ይችላሉ ብዬ ገመትኩ እንጂ ስንት ነገር ሰምተው ችለው ይሆን?
እድሜ ጠገቦቹ ዛፎች ስንቱን ታዝበው ይሆን! ከስራቸው ተሰይሞ ሰዎችን ያማ፤ ዛፎቹን ተከልሎ የሰው ሀሳብ የቀማ፣ በቡጨቃ ሌላውን ያደማ፤ ጥላቸውን ተጠቅሞ ተገቢ ያልሆነን የሰማና ያሰማ፤ አንዳንዴም ከሰው የተስማማ አይጠፋም። ብቻ ዛፎቹ ቅጠላቸው ረግፎ ከጎረቤት የተዋሱት ሌላ ቅጠል ለብሰው በአብሮነት ዛሬ ድረስ ቆይተው ነበር።
ቆዩኝማ ሰሞኑን 200 ሚሊዮን ችግኞች ይተከላል መባሉን ሰምተው እኛን መች በቅጡ ተንከባከባችሁን ብለው እራሳቸውን ከዛፍነት ወደ ማገዶነት በመቀየር ተቃውሞ ማሰማታቸው ይሆን እንዴ? ጠረጠርኩ እዚህ አገር ላይ የማይቃወም እኮ የለም ተቃዋሚነት የሀበሻ ሱሱ ሆኗል። ለነገሩ ፅዶቹን ሀበሻ ናቸው፤ ይሄ ደግሞ ጥርጣሬዬን ያሰፋዋል።
ዛፎቹ በሕይወት ዘመናቸው የመዝናኛው የአየር ንብረት ክልል የተዛባ እንዳይሆን ብዙ አስተዋፅኦ አበርክተው ነበር። በተለይ እስሩ ቁጭ ብለው ጢስ ለሚያጤሱት በጥላው ከልሎ የምትለቁት ነገር መልካም ባይሆን እኔ ችዬዋለሁ። እያለ ጢሱን ሲምግ በአንፃሩ ደግሞ ተስማሚውን ሲቸሩ ቆይተዋል።
ተያይዘው የወደቁት የፅድ ዛፎቹ ግን የምር አስቀንተውኛል። አብረው የተፈጠረላቸውን እየተቋደሱ ቆይተው አብረው መውደቃቸው የኛ አብሮነት ክፍተት በጉልህ ለማሳየት አያስችልም? ወዳጆቼ።
ውይ ትዝ አለኝ፤ እንዴ ፈዘናል፤ ተነጥቀን ዝም ልንለው የማይገባ ብርቱ ጉዳይ ይሄ ነው። ሀበሻ ሆይ አሁን ዘራፍ በል! ተነጥቀሃል። የእውነት ማንነትህ ማሳያ የሆነው የእርስ በእርስ ፍቅርና ህብረትህ ተሸርሽሮ እኛ ግቢ ካለው ዛፍ አንሷል። እኔ ምለው ማነው ግን የቀማን? ማነው የወሰደብን? ኧረ ጎበዝ እናስመልስ ተነሱ። አገር ስትወረር እናብር የለ? ታዲያ በአገሪቱ ኗሪ የሆነው የሰው ልጅ መለያ ባህል ሲሸረሸር ዝም ይባላል።
የእርስ በእርስ መተሳሰብ ውዱ እሴታችን የተነጠቅን መሆኑን የሚያሳይ አንድ ትልቅ ማሳያ ከገጠመኜ ላመላክታችሁ ውዶቼ። አንድ ጎረቤት አለኝ፤ የከበረ። የከበረ ስል ገባችሁ ፈራንካ የተራረፈው አስመጪና ላኪ በከተማይቱ ከ10 ያነሱ ቦታዎች ላይ ቪላዎችን እየሰራ የሚያከራይ ነው።
እናላችሁ ስግብግብነቱ ደጋግሞ ቢያሳየኝም የሰሞኑ ሁኔታው ግን ለሰውዬው ያለኝን ነገር በሙሉ ወደ ታች ወሰደብኝ። ወደታች ያስኬደኝ ጉዳይማ ወዲህ ነው ውዶቼ። መንግስት ለስራ አጥ ወጣቶች ብሎ የመደበው ስራ አጥ ወገኖቻችን እንዲጠቀሙ የተበጀተ በጀት ሊቀራመት መሞከሩ ነው።
ወዳጆቼ ይሄ ሰው ወረዳ ሄዶ መታወቂያ ቀይሩልኝ አለ። ስም ሳይሆን ስራ ነጋዴ የሚለው ወደ ስራ አጥ እንዲቀየር ጠየቀ። ያወቁት ነበርና እንደማይሆን ነግረው ሸኙት። በድብቅ ያደረገው ነበር እና ያው አምላክ ክፉ ስራ አጋላጩ አይጠፋምና ወረዳ ይዞት የሄደው ህፃን ልጁ ውሎዋቸው የት እንደሆነ ለጠየቀችው እናት ወረዳ ለመታወቂያ ቅየራ መሄዳቸውና እንዳልተሳካ አባቱም እንደተናደደ ተናገረ።
እናት ይሄኔ ጥያቄዋን አከታተለች። ‹‹የምን የመታወቂያ ቅያሪ ነው?” የሚስት ጥያቄ ሆነ። ይሄኔ አባት አፍረጠረጠው። ስራ አጥ ለማስባል ሄዶ እንዳልተሳካለት። ያንን ለማድረግ ያነሳሳው ደግሞ ለስራ አጥ ብር እንደሚሰጥ በብድር መስማቱና ለጀመረው አዲስ ቤት ማሰሪያው ብር ፈልጎ እንደሆነ ተናገረ። እኔ እንደማፈር ቃጠኝ። በኋላ የድርጊቱ ተዋናይ ይፈር ምን አገባኝ ብዬ ተውኩት። ለቡና የተጠራሁት እኔን እያየች እናት ተሸማቀቀች። አባት ባደረገው ስግብግብነት በጣም አዘነች። ቃል ሳታወጣ በብርቱ ፊትዋን በቁጣ አለበሰችው።
እንደው ይሄ አብሮት የነበረው ብላቴና ከሱ ምን ይሆን የሚማረው? ስግብግብነት፤ ገንዘብ አምላኪነት? ሌላ መልካም ነገር ከወላጅ አባቱ ካላየ ከዚህ ልጅ ምን እንጠብቅ? ወገን ይሄ ምን ይሉታል? እንደው ለሰው አለማሰብ ብቻ እኮ አይደለም ከሰው መቀማት ስለሌላው ምን አገባኝ ብሎ እራስን መውደድ ስግብግብነት እንጂ። እኔ ምለው ከዚህ አይነቱ እነዚያ እኛ ግቢ መዝናኛ ውስጥ ወደቁ ያልኳችሁ ዛፎች አይሻሉም? የእውነት በጣም።
ለማንኛውም ውዶቼ ዛፎቹን ተክለን የተሻለ ጠቀሜታ እንዲሰጡን ተንከባክበን የምናሳድገው እኛ፤ ሰብዓዊነት ተላብሰን ስለ ሰው ትልቅ ማሰብ የሚጠበቅብን እኛ፤ ከሰው ጋር ተሰልፈን ከሰው ጋር ተጋርተን ሰውነታችንን ከፍ እናድርገው። በስግብግብነት ስብዕናችንን አናጉድለው። ሰው የመሆንን ልዩ መለያችንን በሰው በመሆን እናፅናው አበቃሁ። ቸር ይግጠመን።
አዲስ ዘመን ሀምሌ 19/2011
ተገኝ ብሩ (ሻሚል)