የሩቅ ጊዜ እውነተኛ ታሪክ ነው።ምን ለብሼ ልሳቅ የሰውየው እውነተኛ ስሙ አይደለም።በነገር አገደም አግራሞት የሚያጭርበት ጉዳይ ሲያገኝ ከት ብሎ እየሳቀ ምን ለብሼ ልሳቅ ስለሚል ነበር አካባቢው መንደርተኛው በሩቅ የሚያውቁትም ጭምር በዚህ ስያሜ የሚጠሩት።መለያው መጠሪያ ስም ሆኖ ጸደቀለት።
አዳሩ በዚያን ዘመን ይሰሩ ለነበሩ ቤቶች ከአሰሪዎቹ ከባለቤቶቹ ጋር ተዋውሎ ጭቃውን በጭድ እያቦካ በደንብ በተለያየ ቀናት አገላብጦ ፈርመንትድ ሲሆን (ሲበስል) እንበለው የተማገረውን አዲስ ቤት ደህና አድርጎ በጭቃ ይመርገዋል።በኋላም የልስን ስራ ይሰራል።የእኛ ሀገር የቀደመው ዘመን ሲሚንቶአችን መሆኑ ነው።ዛሬም በስፋት ይሰራበታል፡፡
ብዙዎቹ የሀገራችን ቤቶች የሕዝቡ የመሳፍንቱና መኳንንቱ ሳይቀር ምሰሶው ቆሞ ወጋግራው ከተዋቀረና ከተገደገደ በኋላ የሣር ክዳን ይደረግለታል።ዙሪያውን የሚለሰነው ምርጥ ብቃት በነበራቸው የሀገራችን ጭቃ አቡኪና ለሳኞች ነው።ስንቱን ከተማ መንደር ሰፈር አብረው እንደቆረቆሩ፤ ስንቱን ቤት እንደሰሩ፤ የሚናገርላቸው የሚጽፍላቸው ጠፍቶ እንጂ ሰዎቹስ ምርጥ ባለሙያዎችና ባለታሪክም ነበሩ። እነ ምን ለብሼ ልሳቅን የመሰሉ ብዙ ሺዎች ፡፡
ምን ለብሼ ልሳቅን ለየት የሚያደርገው ለየት ያለ ባህርይና አስገራሚም ስለነበረ ይመስለኛል። ግጥም የለውም። መንደርተኛና ሰፈሩ በአለባበሱ ይደመማል። ትልቁም ትንሹም።ሲመጣ ሕጻናት ይከቡታል። ያውካካሉ።ሱሪ 2 ኮት 3 ሸሚዝ 2 ከረባት 4 ሁልጊዜም መነጽሩ ባዶና መስታወት የሌለው፤ በሸሚዞቹ ኪሶች ላይ የሚሰሩና የማይሰሩ ብዙ እስክሪቢቶዎች የሚደረድር ሰው። ጸጉሩ በዘመኑ ፋሽን ኤልቪስ።ዘመኑም የእነ ኤልቪስ የዝነጣ ዘመን ነበር። በጫማ ላይ ጫማ ስለማይደረግ እንጂ እሱንም ለማድረግ አይመለስም ነበር።
በዚያን ዘመን እንዲያ ለብሶ ከገጠር መንደር ብዙም በማትለየው የአዲስ አበባ ጥርጊያ መንገዶች ላይ ሽር ብትን እያለ በቄንጥ ሲራመድ የሁሉንም ቀልብ ይስባል።‹‹ኧረ ሳቄ መጣ›› ያሠኛል።እሱ ማንንም ከቁብ አይቆጥርም። ይህ ሰው ማነው ለሚለው ማንም መልስ አላገኘለትም።ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ ወይንም ለመጠላት ወይ ለመወደድ እንዲሉ ሆነና።
አዕምሮው ልክ አይደለም ባዮች ብዙ ነበሩ።እነሱ እንጂ እሱማ ልክ ነኝ ብሎ ነው የሚኖረው፤ የሚሰራው።የተዋዋለውን ስራ ጭቃ ማቡካቱንና መለሰኑን አሳምሮ ይሰራል።ስራ ሲሰራ ይዘፍናል።ሰው ሰማ አልሰማ ደንታ የለውም።ዘፈኑ ሁሌም ‹‹አንቺ ልጅ›› ነው። ‹‹አሀሀሀ አንቺ ልጅ፡፡›› ምናልባት ምናልባት ይሄ ስለሚሰራው ስራ እንጂ ስለማንነቱ ብዙ የምይታወቀው ሰው ከጀርባው ምን ታሪክ ተሸክሞ ይሆን የሚለው ጥያቄ የብዙዎች ነበር።
የት ተወለደ፤ አደገ፤ ተማረ፤ ቤተሰቡስ የት ነበር? ምንም ፍንጭ የለም።ብዙ ሰዎች ለማወቅ ጥረዋል።ሲጠይቁት መልሱ አጭር ነው ምን ለብሼ ልሳቅ ይልና ይንከተከታል።ምናልባት በሰዎቹ በመገረም አሊያም ዓለምን በመናቅ ሊሆን ይችላል።እኛ ያላየነው የማናውቀው የለም በሚል ውስጣዊ ምፀት ይሆናል ከት ብሎ የሚስቀው።
አዛውንቶቹ ወጣቱ ሁሉም ሰው ያውቀዋል። አብዝተው ይገረሙበታል። በማይታወቀው ማንነቱ። በዚህ ሰው ማንነት ውስጥ ሌላ የተሰወረ የተደበቀ ማንነት አለ።ግን ለምን እንዲያ ሆነ ቢባል የመልሱ ባለቤት እሱና እሱ ብቻ ነው። ብዙ ሰዎች ደሞ ‹‹ምን ለብሼ ልሳቅ ይላል እንዴ፤ ይሄን ሁሉ የሀገር ልብስ ደራርቦ እየለበሰ›› ይሉና ይሽኮመኮማሉ።
የሚገርመው የስራ ልብስ አለው።ለብሶ የሚመጣው ንጹህ ልብሶች ናቸው። ስራውን ሲጨርስ ተጣጥቦ ሲያበቃ ያንኑ ደራርቦ ይለብስና ሽክ ይላል። ‹‹አሀሀሀሀሀሀ አይ ምን ለብሼ ልሳቅ።›› ዛሬ ከስንትና ስንት ዓመታት በኋላ ታወሰኝ በል፡፡
‹‹በጤናው አይደለም›› ቢሉም ‹‹እኔ እብድ አይደለሁም፤ እናንተ ናችሁ እብድ›› ይላል።‹‹ጤነኛ ነኝ›› የሚል ስንት እብድ እንዳለ መንፈሱ ሹክ የሚለው ይመስላል።ልብሱ፤ ከረባቱ፤ ሸሚዙ ኮቶቹ ይቀያየራሉ።ወይ ሰዎች ይሰጡታል ወይ የራሱ የሆነ የተከማቸ አለው።ለስራ ተዋውሎ ሲመጣ እንጂ መኖሪያው አይታወቅም የምን ለብሼ ልሳቅ።እንደሌሎቹ የእሱን አይነት ስራ እንደሚሰሩት ሰዎች ጠላ፤ ጠጅ፤ አረቄ፤ ቤት አይታይም።ቢሰጡትም አይጠጣም፡፡
አንዳንድ ሰዎች ግን እንደዛው ለብሶ አልፎ አልፎ ግሮሰሪ እንደሚገባ በሥርዓቱ ቁጭ ብሎ አዞ የተወሰነ አልኮል እንደሚጠጣ ይናገራሉ።አንድ ጊዜ ቁምጣ ሱሪውን አድርጎ በባዶ እግሩ ጭቃውን ሲለውስ ከቤታቸው ውሀ ልክ ላይ ቁጭ ብለው ሁለት የተማሩ ወጣቶች ምስጢራቸውን በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያወራሉ።
ማንም ሰው አይሰማንም ነው ነገሩ።መቼም ምንም ቢያስቡ ሊጠረጥሩ አይችሉም። እሱ ስራውን ይሰራል። ሰማ፤ ሰማ ፤ሰማና መጨረሻ ስራውን ከውኖ ተጣጥቦ ሲያበቃ ያንኑ አስገራሚ ልብሱን ከረባቱን ባዶ መነጽሩን አድርጎ ለማረፍ በሚመስል መልኩ ተማሪዎቹ አጠገብ ቁጭ አለ።እየሳቁ ምን ለብሼ ልሳቅ ታዲያስ አሉት።በተለመደው ሳቁ አውካካ።አይ እናንተ አሁን ምስጢራችሁ እንዳይሰማ ነው አይደል በወፍ ቋንቋ የምታወሩት አላቸው።‹‹ልክ ነህ ማንም እንደማይሰማ እርግጠኞች ነን›› አሉት።የተነጋገሩት ስለአብዮትና ለውጥ ስለንጉሱና ሥርዓታቸው የእኛስ በምን መልኩ ነው መሄድ ያለበት የሚል ነበር፡፡
የወጣቶቹን አፍ ያዘጋ ድንጋጤ ውስጥ የከተተ ድንገተኛ ምትሀት የመሰለ ጉዳይ ተከሰተ።በጠራ እንግሊዝኛ የተወያዩበትን ዘርዝሮ ጥያቄአቸውን በመለሰ መልኩ ነገራቸው ጭቃ አቡኪውና ለሳኙ ምን ለብሼ ልሳቅ።ደነገጡ።ማመን ተሳናቸው።እሱ ነው ሌላ ሰው እስኪሉ ድረስ።መጽሐፍቶችን በስም እየጠራ ይሄን ይሄን አንብቡ ሲላቸው ድንጋጤአቸው ሽቅብ ጎነ።ግን አላቸው ለማንም አትናገሩ ቃል ግቡልኝ። እኔ በዚህ መልኩ የምሰራው የምኖረው የእራሴን ኑሮ ነው።ደስተኛ ነኝ።ዓለምን ንቄ ሰውንም እርቄ ነው ብሎ በረዥሙ ተነፈሰ።
እንዴት ብዙ የተማረ ሰው በሌለበት ሀገር የዚህ እውቀት ባለቤት አንዱ ጋ ተቀጥሮ መኖር ሲችል ይሄንን አይነት ኑሮ ለመኖር መረጠ በሚል ወጣቶቹ በእጅጉ አዘኑ።ተደናገጡ።እሱ ግን አላቸው።ለእኔ አታስቡ አትጨነቁም።በጉልበቴ ሰርቼ እኖራለሁ።ስራ አከብራለሁ።የሰው እጅ አላይም።ልመና አልወድም።ዓለምን ስትረሳት ትረሳሀለች። ሁሉን ከረሳህ በትላንት ውስጥ ካልቆዘምክ ትኖራለህ በሉ ቻው አለና ተነስቶ ግቢውን ጥሎ ወጣ።ጉድ ጉድ ሲሉ ውለው አደሩ።ምን ለብሼ ልሳቅ ማነው።ከአሁኑ ትንሽ መገለጥ በቀር ስለዚህ ሰው ማንም ምንም አያውቅም።
ሌላ ሰፈር ሄዶ ያንኑ ጭቃ ማቡካት ሲሰራ እንዲሁ የ11ኛ ክፍል ተማሪዎች በራፋቸው ላይ ቁጭ ብለው በተሰጣቸው የታሪክ ትምህርት የቤት ስራ ላይ በእንግሊዝኛ እያወሩ ይከራከራሉ።የያኔ ተማሪ ብርቱና የቀለም ቀንድ ነበር።ለወረቀት ሳይሆን ለእውቀት የሚተጋ።ለእውቀት የሚታትር ንብ።አንባቢ፤ተከራካሪ፤ሞጋች።ብርቱ የቀለም ደቀመዝሙርና ካህን።መምህሮቹም በእውቀት የላቁ የረበቡ።እሱ ጭቃውን ጭድ እየነሰነሰ ይለውሳል።ተማሪዎቹ በጥያቄው መልስ ላይ አልተስማሙም።ተነታረኩ።አጠገባቸው ወትሮም የሚያውቁት የሚስቁበት ምን ለብሼ ልሳቅ ብቻ ነበር።ሌላ ሰው የለም።
አከራካሪው ጥያቄ በፈረንሳይ አብዮት ላይ ያተኮረ ነው።ምን ለብሼ ልሳቅ አካፋውን ይዞ ጭቃውን እያገላበጠ ይሰማቸዋል። አላስቻለውም። ዝምታውን በድንገት ሰበረና ከት ብሎ ሳቀ።አንዱ ተማሪ ይሄ እብድ ምን ይስቃል ሲል አዎን እብድ ነኝ። ዘመን ያሳበደኝ በራሴ ዓለም የምኖር እብድ አለው። መልሱ ልጁን አስደነገጠው። ምን ለብሼ ልሳቅ ለጠቅ አደረገና በጠራ እንግሊዝኛ ምንድነው የምትጨቃጨቁት ሲላቸው በተቀመጡበት ክው ብለው ቀሩ። እሱ ነው የተናገረው ሌላ ሰው በሚል ጥርጣሬ።ደገመላቸው። የተከራከሩበትን ነጥብ በነጥብ እያነሳ ከመነሻው እስከ መድረሻው አካፋውን ይዞ ቆም እንዳለ አነበነበላቸው።መልሱ ይሄ ነው አለና በረዥሙ ተነፈሰ፡፡
ተማሪዎቹ አብዝተው ተደመሙ።ግን አላቸው ስለእኔ ለማንም አታውሩ ።ስለእኔም አትጨነቁ።አትመራመሩ።እኔ በራሴ የሕይወት መንገድ ደስተኛ ነኝ። ከማንም ምንም እርዳታ አልፈልግም። እስካለሁ በጉልበቴ ሰርቼ እኖራለሁ። ስራዬን አከብራለሁ።እናንተ ግን በርትታችሁ ተማሩ።አንብቡ።
ለወረቀት ሳይሆን ለእውቀት ትጉ አላቸው። በተቀመጡበት በድንጋጤ ተመቱ። ከጭቃው ውስጥ ወጥቶ ተጣጥቦ ልብሱን በተለመደው ሁኔታ ለባብሶ ቻው ብሎአቸው መንገዱን ቀጠለ። ግዜው የ1966 አብዮት ዋዜማ ነበር።ምን ለብሼ ልሳቅ ማነው? እውነተኛ ስሙና ታሪኩስ? ምን ገጥሞት ምንስ ሆኖ ይሄን የሕይወት መንገድ መረጠ?
አዲስ ዘመን ሀምሌ 18/2011
ወንድወሰን መኮንን