ውዶቼ እዚህች ሀገር ላይ ሁሉን አውቃለሁ ባይና ጉዳዮችን በልበ ሙሉነት ኧረ እንደውም በድፍረት የሚተነትን በዝቷል። መፍትሄን አመላካች ከመሆን ይልቅ ጠያቂና ፈላጊ በርክቷል። ለኔ ያለ ስራና ያለ ሙያው ብዙ የሚናገር በዝቶ ታየኝ፤ያለ ሚዛን የሚፈርድ ያለ መረጃና እውቀት የሚናገር ድምፅ ጎልቶም ተሰማኝ። በአንድ አገራዊ ጉዳይ ላይ ወይም ፖለቲካዊ ሁነት ላይ ጥልቅ እውቀት ያለው ይመስል ሁሉም ትንታኔ ግራ አጋብቶኛል።
እንደው ማን ይሙት የአንድ አገር ዜጋ በሙሉ ፖለቲከኛ መሆን በአንድነት እንዴት ይቻለዋል? በየ ታክሲና መጓጓዣው በየስራና መዝናኛው ብቻ በብዙ መዳረሻዎች የሁላችን ሥራ ተመሳሳይ የሆነ ያህል ተመሳሳይ ጉዳይ ላይ ጥልቅ ትንታኔ መስጠት የተላመድነው ጉዳይ ሆኗል። ሁሉም ጋዜጠኛ ከሆነ ከየትኛው ትክክለኛ መረጃ እንቀበል? ሁሉም ተቺ ከሆነ የሚተቸውን በምን እንወቅ? ሁሉም ተቆጪ ከሆነ የሚቆጡትን በምን እንለይ? ሁሉም ተጎዳሁ ባይ ከሆነ ጎጂውን ከየት እናግኘው? ሁሉም ጠያቂ ከሆነ የሚጠየቀው ማን ይሆን?
በተለይ አሁን አሁን ሁላችንም የፖለቲካ ሳይንስ ሙህር አልያም ፖለቲካን አብጠርጥረን የተረዳን ያህል ፖለቲከኞች የሆንን ያህል ፖለቲካን መተርተር እና መስፋት ቀሎናል። ኧረ ከፍ ብለን መፃዩን የፖለቲካ ሁኔታም የምንተነብይ ነብይ ሆነናል። እኔ የምለው ሁሉም ፖለቲከኛና ተንታኝ ከሆነ ማነው ሲቪሉን የሚመራው? ማነው የበዛውን የሲቪሉን ሥራ የመተገብረው? ኧረ ወደ ሥራ። ያለ ተግባርና ሚናችን እየገባን ትነታኔና ብያኔ መስጠታችን ምን ይሉታል?
አገራዊ የሆኑና የራሳችን ጉዳዮች ላይ አያገባንም የሚል አቋም የለኝም። ነገር ግን ሁሉን ልናውቅ ሁሉም በልኩ መተንተን ስለማንችል ሙያን ለሞያተኛ ትትን እኛ የምንችለውና የምናውቅ ላይ ትኩረት አድርገን ሀሳብና አስተያየት ብንሰጥ የሚል ነው መነሻዬ። እሰቲ እውነት አሁን ላይ ያለንን ልመድና አሁናዊ ሁኔታዎች እናስተውል። የምናነሳና የምንጥለው፤ የምንሰቅልና የምናወርደው ፖለቲካ በፖለቲከኞቹ ልክ ገብቶን የፖለቲካን ስሌት በትክክል አውቀን ነው? እንደልባችን የምንተነትነው እንዴት ነው? ድፍረቱ አልበዛም?
ጉዳዩን ለጉዳዩ አዋቂ ትተን እኛ በሚመለከተን በምናውቀው ላይ ብቻ ትኩረት አድርገን አገራዊ በጎ ተፅዕኖ መፍጠር ላይ ብንረባረብስ። ሁሉን አዋቂና ስለሁሉም ብያኔ ሰጪ መሆን እንዴት ይቻለናል? አሁንማ የማናውቀውን እየሰነጠቅን የምናውቀውን በማናውቀው እንዳናጠፋው ሰጋሁ።
ሙያ አለን እኛ በዚያ ሙያችን ላይ ብቁ ከሆንን ተፅዕኖ መፍጠር ከቻልን ለአገር በቂ ነው።
ያለ ሥራችን ገብተን መወናበድ ያለ ሙያችን መተንተንና ምላሽ የሌለው ጥያቄ ማቅረብ እየተላመድን ነው። አንድ ለምላሽ የሚሆን ጥያቄ ሳናቀርብ መቶ መልሶች መናፈቅ ጀምረናል። የምንጠይቀው ጥያቄ እና የምንፈልገው መልስ የሚሰጠን መልስና የሚመለስበት መንገድ አልተገናኝቶም ሆኗል። ውል የሌለው ጥያቄ የተቃና መልስ እንዴት ሊያገኝ ይችላል?
አንድ ወቅት ላይ አንድ እንቁራሪትና መቶ እግር መንገድ ላይ ተገናኙ። መገናኘታቸው አጋጣሚና ለመጀመሪያ ጊዜ ነበረና እንቁራሪት በመቶ እግር ተደመመች። ባየችው ነገር ተደንቃ፤ “አቤት ይሄ ሁሉ እግር ይዞ እንዴት አቀናጅቶ ሳይወላዳ በትክክል ሊራመድ ቻለ?” የሚል የመደመም ምርምር ውስጥዋ ተፈጠረ። መልሱን በራስዋ መግኘት ተሳናትና ጥያቄውን ለመቶ እግር አቀረበች።
“ውድ መቶ እግር እንደው የእግሮችሽ መብዛት ቢያስደንቀኝ በስርዓት መምራትና በተቃና መንገድ መጓዝሽ ቢያስገርመኝ ጥያቄ ላቀርብልሽ ወሰንኩ።” ቅልስልስ እያለች ምላሽ እንዲሰጣት በመጓጓት ቀጠለች። “እግሮችሽ እንዴት እንደሚራመዱና እንዲህ በዝተው ሳይወላገዱ ተራቸውን ጠብቀው እንዴት ሊንቀሳቀሱ ቻሉ? ውዴ! የኔ እኮ አራት ሆነው እኳን በስርዓት መራመድ አቅቶኝ የምሄደው እየዘለልኩ ነው።” በማለት በትህትና ከስዋ እውቀት የራቀውን ለመረዳት የምትፈልገውን ጥያቄ በትህትና ለመቶ እግር አቀረበች። የስዋ አለመቻል እየቆጫትና ከስዋ በተሻለ ትችላለች ብላ ያሰበቻትን የመቶ እግር እግርን እያየች።
መቶ እግርም ኮራ ብላ ስለ እግሮችዋ የተጠየቀችወን ጥያቄ በመመፃደቅ ስሜት በመኮፈስ ምላሽ መስጠት ጀመረች። “ይሄውልሽ እንቁራሪት እኔ የታደልኩ ነኝ መቶ እግሮች አሉኝ። መቶ እግሮቼን ያላንዳች ማወላዳት ተራ በተራ መንቀሳቀስና በኩራት ወደፈለኩት መሄድ ያስችለኛል።” ለተጠየቀችው ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ተፈጥሮ ያደላትን ሰርታ ወይም ለፍታ ያገኘችው ይመስል ስለራስዋ ችሎታ ትዘረዝር ጀመር። እንቁራሪት አልተበሳጨችም ይልቁንም የፈለገችው ምላሽ ለመስማት መታገስ ነበረባት ታገሰች።
በመጨረሻም መቶ እግር ማብራሪያዋን ከመጨረስዋ በፊት እንዲህ አለች “ ይሄውልሽ እንቁራሪት ውዴ ይሄ ምርጥ ችሎታዬ ላንቺ ለማሳየት እወዳለሁ እግሮቼን እንዴት እደማንቀሳቅሳቸው በተግባር ላሳይሽ ነው። አንቺም በአንክሮት ተከታተይኝ።” ብላ በተግባር እርምጃዋን ለማሳየት ተዘጋጀች። እንቁራሪትም በጉጉት መከታተል ጀመረች።
መቶ እግር ማብራሪያዋን ቀጠለች “ስራመድ እኔ የማደርገው ምን መሰለሽ መጀመሪያ የፊት እግሬን አስቀድማለሁ ከዚያ ሁለተኛው እግሬን እንደዚህ በማንሳት አስከትለዋለሁ….” በማለት በተግባራዊ እንቅስቃሴ ማሳየትዋን ቀጠለች መሀል ላይ ግን በማሳየት ሂደት ውስጥ ሳለች ተፈጥሯዊ ቅንጅትዋ ይዛባና መሄድ ይሳናታል። ለእንቁራሪት አረማመድዋን ማስተማር፤ቄንጥዋን ማሳየት አይደለም እግሮችዋ ተወለጋግደው በስርዓት መቆም አቃታት ። በግራ መጋባት ስሜት የምትመለከታት እንቁራሪት በሁኔታው ግራ ተጋባች። መቶ እግር ጭራሽ በፊት ትሄድ የነበረው እርምጃ ጠፍቶባት ኩርት ብላ ቆማ እንቁራሪት ላይ ማፍጠጥ ያዘች፤ጭራሹንም ትቆጣ ጀመር።
በመጨረሻም መቶ እግር ለዚህ ሁሉ ያበቃቻት እንቁራሪት አረማመድሽን አሳይኝ ስላለቻት መሆኑ በፅኑ አምና በንዴት እንዲህ አለች። “አንቺን ከማግኘቴ በፊት እንደ አፈጣጠሬ በሰላም እኖር ነበር። ምን አንቀለቀለሽ አንቺ አጓጉል ጥያቄ እየጠየቅሽ የምችለውንም አጠፋሽብኝ። ሂጅልኝ በቃ ጉዞዬን በተቃና መንገድ ልቀጥልበት።” ብላ ክፉኛ ተጣላቻት።
ውዶቼ ከላይ የቀረበው የመቶ እግርና እንቁራሪት ታሪክ ትርጓሜው ጥልቅ ነው። ምን አልባት እያነበባችሁ ታሪኩን ብዙ መስጥራችሁ ይሆናል። አዎን የዚህ ታሪክ መልዕክትና የያዘው ቁም ነገር በብዙ ይሰፈር ይሆናል። ማያ ላለው ማስተዋልን ለተላበሰው። እኔ ግን ከዚህ ታሪክ አንድ ነገር ብቻ መዝዤ ያየሁትን ላመላክታችሁ። በእርግጥ በዚህ መንገድ ያየሁበት ትርጓሜዬ ላይ ላዩን እንጂ ታሪኩን በጥልቀት መርምረን እንዘርዝረው ብንባል ጊዜም አይበቃንም። እንዲሁ በገደምዳሜ የተነሳሁበትን ሀሳብ ለማጠንከር የሚረዳኝ የታሪኩ ትርጓሜን ተከትዬ በዚህ መልክ ተረጎምኩት።
ወዳጆቼ አያችሁ የእንቁራሪት ፍላጎት ያላትን መሰረት ያደረገ የራስዋን አቅም በራስ ያተቃኘ ነበርና ጥያቄዋ ትክክል አልነበረም። የእንቁራሪትዋ ስህተት የስዋን አፈጣጠርና ቁመና አለመቀበልዋ፤ የተፈጠረችበት ሁናቴ መኮነንዋ ሲሆን የመቶ እግር ደግሞ ባልፈጠረችው መመፃደቋ ባለፋችው መፎከርዋ በመጨረሻም ተፈጥሮ የቸራትን የግሌ ነው አዛዡም እኔ ማለትዋ የተሰጣትን አለመውደድና መቀበል አለመፈለግዋ ይሄም ስታገኘው የነበረን ይብስ ማጣትዋ ያሳያል።
የኛ ነገር በአብዛኛው የእንቁራሪትዋና የመቶ እግርን ጥያቄና መልስ በመጨረሻም ውጤቱን እየመሰለ ነው። ዛሬ ላይ የምንጠይቃቸው ጥያቄዎች ምላሽ የሚፈልግ አልያ ደግሞ እውቀትን የሚፈልግ ሳይሆን ስህተትን የሚፈለቅቅ፤የምንጠይቀውን ሰው ወይም አካል ምላሽ የሚያሳጣ አድርገንዋል። የሚመለሰውም መፍትሄን የሚሰጥ ሳይሆን በጥያቄው ጭራሽ ግራ የሚጋባ አልያ ደግሞ አመላለሱን የሳተ ሆኗል።
የአብዛኞቻችን ጥያቄዎች የሚያደናግሩና መልስ ከማግኘት ይልቅ የነበሩንን የሚያሳጡን ሆነዋል። ለዚህ ምክንያት ደግሞ የምንጠይቀው ጥያቄ በትክክል እኛን ያገናዘበ አለመሆኑና ከመልሱ ይልቅ የምንጠብቀው ቀድሞ ያሰብነው መሆኑ፤ ሲሆን የጥያቄያችን ምላሽ ሰጪ ብለን የተቀበልነው አካል (በእርግጥ ያልተቀበልነውን ነው መጠየቅ የምንወደው) ምላሹ ተገቢ ይሁን አልያም አይሁን እንዲመልስን ያሰብነው ነገር ካልሆነ አንቀበለውም። መላሹ ጋር ያለው እይታና እውነት ደግሞ ብዙ ጊዜ ስለሚለያይ ከጠያቂው የራቀ መልስ ይሆናል።
ሥራ ለሠሪው እሾህ ላጣሪው ሲባል እዳልነበር። ዛሬ በየ ጉዳዩ አውቃለሁ ስለጉዳዩ እተነትናለሁ የሚል በዝቷል። አዎ በምናውቀው ጉዳይ ከምንሰጠው አስተያየትና ጥያቄ ይበልጥ ስለማናውቀው እኛን በማይመስል ጉዳይ ላይ አስተያየትና ጥያቄ መሰንዘር ቀሎናል። ከቤት እስከ አደባባይ የምንወያይባቸውና የምንነጋገርባቸው ጉዳዮች ሁላችንም ስለምናወራበት ጉዳይ የበቃን ተንታኝ አስመስሎናል። በጉዳዩ ላይ ያለን እውቀት ጥግ ላይ የደረሰ ያህል ወገባችን ይዘን እንሞግታለን። ይሄኔ ትክክል የሆነ ሀሳብ ከሌላ ወገን ቢቀርብልን እንኳን የኛ ሀሳብ ካልተስተካከለ ትክክሉ ሃሳብ ትክክል አይደለም።
ከሙያችን ውጪ በሆነና በቂ ግንዛቤ ባልጨበጥንበት ጉዳይ እየገባን የራሳችንን አተያይ እና መሰለኝን “ነው።” እያልን ከምንደመድም መመርመርን ብናዘወትር በስሌት ብንራመድ መልካም ልምድ ይመስለኛል። ሁሌም ስለ አንድ ጉዳይ ያለን ልኬትና አተያይ ይለያያል። ያ ደግሞ በተቀረፅንበት ማህበረሰብና አካባቢ ይወስነዋል። በእርግጥ እንደ ልማድ ያለ ስሌት በጀማ መበየንና መፍረድ በአጀብ መወሰን ተላምዶብን ሊሆን ይችላል። ግን ይህ ልማድ ልንላቀቀው የማንችለውና ከኛ ጋር አብሮ የተሰራ አይደለም። ወደ በጎ ልምድና ተግባር መለወጥ እንችላለን። ወግን ወደ ሥራ ሙያን ለሙያው ባለቤት ትተን ባለንበት መስክ አገር ለማቅናት እንጣር። ያኔ ሁሉም መልካም ሁሉም በጎ ይሆናል። ሰላም ያብዛልን፤ አበቃሁ!
አዲስ ዘመን ሐምሌ 5/2011
ተገኝ ብሩ