ኀዘን ፣ደስታ፣ ሰርግ ፣ዕርቅ፣ ሽምግልና … የሚገለጽባቸው ቱባ ባህላዊ እሴት ባለቤት ናት – ኢትዮጵያ ። እነዚህ ባህሎች የሚገለጹበት መንገድ ደግሞ እንደ የብሔረሰቡና የአካባቢው ሁኔታ ይለያያል። ኀዘን በብዙዎች ዘንድ በእንባ ታጅቦ መከወኑ ተመሳሳይነት ያለው ቢሆንም መገለጫው ግን ከቦታ ቦታ ይለያያል። በአንድ ስፍራም ቢሆን እንደሟቹ ሰው ደረጃ ክዋኔውም የተለያየ ይሆናል። በዘመድና ዘመድ ባልሆነ መካከል ሰፊ ልዩነት መኖሩን የሚታ ይበት፤ አስለቃሹ ወይም ሙሾ አውራጁ በሚያወጣቸው ግጥሞች የለቅሶ ድምቀትና ግዝፈት ይለያያል።
ዛሬ በጎጃሞች ዘንድ ስላለው ባህላዊ የለቅሶ ስርዓት ልንቃኝ ወደ ጤፉ አገር ጎራ ብለናል ። ባህሉንና የለቅሶ ስርዓቱን ከሚያውቅና ከሚተነትን ባለሙያ ጋር መገናኘት ግድ ነውና በዚህ ጉዳይ ላይ ሰፊ ማብራሪያ እንዲሰጡን በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የባህል ዘርፍ የስነቃል ልማት ጀማሪ ባለሙያ ከሆኑት አቶ ማተቤ ጥላሁን ጋር ቆይታ አደረግን።
መቼም ብዙዎች ጎጃም አዘነ ሲባል በአዕምሯቸው የሚመጣባቸው የጎጃሙ ፎጣ መሆኑ አያጠያይቅም። እኛም ይህንን ፎጣ መነሻ በማድረግ የለቅሶ ጊዜ ምን ይለበሳል ከሚለው ጥያቄ ልንጀምር ወደድን።አቶ ማተቤ እንዲህ አሉ ፤ “ ይህ ፎጣ እንደስሙ በጎጃም አካባቢ ለኀዘን ጊዜ በብዛት የሚለበስ ነው። ምክንያቱ ደግሞ የቀለሙ ሁኔታ ነው። ከዚህም ተነስቶ ስሙን አገኘ“ ሲሉ ይናገራሉ።
ሌላው በኀዘን ጊዜ የሚለበሱ አልባሳት መኖራቸውን ነው አቶ ማተቤ የጠቀሱት። እንስቶቹ የሚያምረውን ነጠላቸውን ከል (ጥቁር ቀለም) በመንከር በአካባቢው ባህል ዘንድ ትክክለኛ የማዘን ምልክታቸውን ያሳያሉ። የአንገትም ሆነ የጆሮ ጌጣጌጦችን ማድረግ አይፈቀድም። በምትኩ ነጭ ክር ወይም ድር በወፍራሙ ይገመድና በአንገ ታቸው ላይ ያስራሉ። ብዙ ጊዜ ከወገባቸው በታች ነጠላ ያሸርጣሉ።ሽርጡን ቢፈቱ እንኳን ነጠላቸውን ማዘቅዘቅ አያቆሙም።
ወንዶቹ ደግሞ ጥቁር ኮፍያ ያደርጋሉ፤ አዛውንቶች ካቦርት ይደርባሉ።በዚያ ላይ ደግሞ የቅርብ ዘመድ የሞተባቸው ከሆነ ወገባቸው ላይ ገመድ ይታጠቃሉ። ገመድ መታጠቁ ለሴቶችም የኀዘናቸው መገለጫ ምልክት ነው።
የለቅሶ ስርዓቱ እንዴት ይከወናል ከተባለ በሁለት ከፍሎ መመልከት ይቻላል። አንዱ አስከሬኑ በቤት ሲኖር ትኩስ ለቅሶ ሲሆን ሁለተኛው ውሎ ብቻ የሚደረግበት ነው። በባህሉ አጠራር መርዶ ይባላል። ይሄ ቀብሩ ሌላ ቦታ ለቅሶው ደግሞ ሌላ ሲሆን ነው።
ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና የቀብር ስርዓት ያለበትን ትኩስ ለቅሶ እንቃኝ። በዚህ የለቅሶ ባህል በርካታ ክዋኔዎች ይተገበራሉ። ከእነዚህም ውስጥ የመጀመሪያው ቤተዘመድ እስኪሰበሰብ ድረስም ወደ ቀብሩ ስፍራ አይኬድም፤ በቤት ውስጥም የተለያዩ ዝግጅቶች የሚደረግ ይሆናል። በዚህ የለቅሶ ስርዓት ቤተሰብ በሙሉ ለቅሶውን የሚያከናውነው የሟችን መገልገያ ቁሳቁሶች እና አልባሳቱን በመያዝ ይሆናል፤ ተቀብሮ ወደ ቤት እስኪመለሱ ድረስ ምግብ መመ ገብ የተከለከለ ነው።
ቤተዘመድ ከተሰበሰበ በኋላ ወደ ቀብር ስፍራ የሚያመራው በፉከራና በሽለላ ታጅቦ ፤ ስለሟች ምንነት እየተነገረ ጭምር ነው። ሰዎችን የሚያበላ የሚያጠጣ ለጋስ ሰው ከሆነ ደግሞ በባህሉ መሰረት የመመገቢያ ቁሶችን ይዘው ይወጣሉ። በትዕይንትነት ከሚቀርበው መካከል ትልቅ መሶብና የመጠጫ የቀንድ ዋንጫዎች ይደረ ደሩለታል። ሴት ከሆነችና ይህንን ተግባር በማድረግ የምትታወቅ ከሆነች ለወንዱ ከሚደረገውም በተጨማሪ ስትዳር ከእናትና ከአባቷ የተሰጣት ሙዳይም ጭምር ይወጣና ለጋስ መሆኗ ይነገርላታል።
ሟች ጀግና እና ባለስልጣን ከሆነ ደግሞ ጠመንጃ፣ ጦር፣ ጋሻ፣ አንካሴ፣ ጎራዴ የመሳሰሉት የጦር መሳሪያዎች ተይዘው ስለማንነቱ ይፎከርለታል፤ ይሸለልለታል። ጥይትም ከቤት አስከሬን ሲወጣና ግብዓተ መሬቱ ሲፈጸም ይተኮስለታል።
በጎጃም የለቅሶ ባህል ሙሾ አውራጅ «ወዬባይ» ተብሎ የሚጠራ ሲሆን፤ በብ ዛት ይህንን ተግባር የሚከውነው ወንድ ነው። በፈረስ ላይ ተቀምጦ ከየአቅጣጫው የሚመጣውን ሰው እየተቀበለ ያስለቅሳል። ስለሰውዬው ወይም ሴትዬዋ ምንነትና ማንነት እየተናገረ ቤተሰቡንም ሆነ አልቃሾች ኀዘናቸውን እንዲወጡ ያደርጋል።
በዚህ ስርዓት ላይ ሴቶች እንደቤተሰብ ከፊት ገብተው ከማልቀስ ውጪ ሙሾ ማው ረድ አይፈቀድላቸውም። ማድረግ ካለባቸው እንኳን ክብ ሰርተው በአስከሬኑ ዙሪያ እየዞሩ ቤተክርስቲያን አስከሬኑ ከመሄዱ በፊት ይህንን ሊያደርጉ ይችላሉ። ቤተክርስቲያን ከሄደ በኋላ ግን እንደቤተዘመድነታቸው የሟችን መገልገያ እቃዎችን ይዘው ማልቀስ ብቻ እንደሚችሉ ባለሙያው ይናገራል።
ከየአካባቢው ባሉ የፈረስ ማህበራት አማ ካኝነት ታጅበው፤ ማህበራቱ ወዬ ባዮችንም በራሳቸው ይዘው ይመጣሉ፤ ለቅሶውም የሚደ ምቀው እንዲህ ሲሆን ነው የሚል አስተሳሰብ አላቸው። ስለዚህ በአንድ ለቅሶ ላይ በርከት ያሉ ወዬ ባዮች ሊገኙ ይችላሉ። ከተቀላቀሉ በኋላ ግን በተራ እየተቀባበሉ ሙሾ ሊያወርዱ እንደሚችሉ ነው አቶ ማተቤ የገለጹልን።
በባህላዊ የለቅሶ ሥርዓቱ እንደ ሟቹ የኑሮና የማንነት ደረጃ ሙሾ የሚደረደር ሲሆን፤ ለአብነት አባወራ፣ እማወራ ወይም የአገር መሪ የሞቱ ከሆነ ለአገር ያለውን ዋጋ ለማስረዳት ሲባል እንዲህ እየተባለ ይለቀሳል።
በሰው ሁላ አገርስ፤ በሰው ሁላ ቤትስ ሻጣ ይመዘዛል
እንደውስ ከእኛ አገር ፤እንደውስ ከእኛ ቤት ምሰሶ ይጓዛል።
ይህ ማለት በሌሎች ቤት ለምሰሶው ደጋፊ የሆኑ“ሻጣ “ ተራ ሰዎች ሲሞቱ በእኛ ቤት ግን ዋናው ምሰሶው ሞተብን እያሉ ኀዘናቸው ከባድ መሆኑን ይገልጻሉ።
በጎጃም ባህል የለቅሶ ስርዓትን ለየት የሚያደርገው ከቀብር በኋላ እሁድን ጠብቆ የሚከወነው የዋይታ ስርዓት ነው፤ይሄ በእለቱ ለቅሶውን ያልደረሰ ሰው ለቅሶ የሚደርስበት ጊዜ ነው። አርባ ወይም መንፈቅ እስኪሆን ድረስ እሁድን ጠብቆ አስከሬኑ በተቀበረበት ቤተክርስቲያን የማልቀሻ ስፍራው ጋር በመሄድ ለቅሶ የሚከናወንበት ስርዓት ነው። በዚህ ጊዜ ቤተሰብ የሆነ ሰው ፎቶ፣ አልባሳቱን በመያዝ ሊያለቅስና እርሱን እያሰቡ ሊያዝኑ ይችላሉ። ለቅሶ ደራሽ እስኪመጣም እስከ አምስት ሰዓት ድረስ በቦታው የሚቆዩበት አጋጣሚ አለ። ይህ ስርዓት መቅረት ያለበት ነው። ምክንያቱም የሟች ቤተሰብ በብዛት የሚጎዱበት ስለሆነ ይላል ማተቤ።
በሁለተኛ ደረጃ የጠቀሰው ደግሞ «መርዶ» የሚባለው የኀዘን መግለጫ ባህላዊ ስርዓት ሲሆን፤ የሚፈጸመው ሌላ ቦታ ሞቶ መርዶው ብቻ ለቤተሰብ ሲደርስ ነው። መርዶ የተባለበት ምክንያት በምንና እንዴት እንደሞተ ስለማይታወቅ ነው። እናም ይህንን ስርዓት ሲያከናውኑ ምስል አስመስለው አልጋ ላይ ይሰሩና ቤተዘመዱ በአጠቃላይ ተሰባስቦ እርሱን እያዩ እንዲያለቅሱ ይደረጋል።
ኀዘን የግለሰብ ስሜት ቀስቃሽ፣ ከዚያም ልቀው ማህበራዊ እውቀትን ልምድን አንሸራሻሪ፣ ግንኙነትን አጠን ካሪ፣ ግንዛቤን በማስፋት ትምህርታዊ መል ዕክቶችን አስተላላፊ ነው። በሰው ልብ ውስጥ ለመግባት እና ለማደርም ቅርብ በመሆኑም ኢትዮጵያውን አዛኝነታቸውን የሚያሳዩበትም ጥበብ ነው። እናም በጎጃ ሞችም ዘንድ በዚህ የኀዘን ቦታ ላይ አለመገኘት፣ አለማስተዛዘንና ከእድሩ አለመ ካፈል ሊያስገልል ይችላል። ጥላቻንም የሚፈ ጥርበት ሁኔታ አለ። ምክንያቱም «ሰርግና ሞት አንድ ነው» አይደል የሚባለው።
ወዬ ባዮች ሁለት ጊዜ ፉከራና ቀረ ርቶ ያደርጋሉ የሚለው ባለሙያው፤ የመጀመሪያው አስከሬኑ በቤተክርስቲያን እያለ ሳይቀበር ዘመድ አዝማዱንና ለቀስ ተኛውን እየተቀበለ የሚያስለቅሰው ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ ግብዓተ መሬት ከተፈጸመ በኋላ ለጀግንነቱ ተብሎ የሚፎከረው ፉከራና ቀረርቶ ነው። በዚህ ጊዜ ግን ለወዬ ባዮች የሚከፈል ገንዘብ የለም። ምክንያቱም ይህ ባህል በመሆኑ ተሰጦዋቸውን እንዲያሳዩ ነው የሚደረገው። ነገር ግን በደንብ አስለቅሶልኛል ብሎ የሚያምን ቤተዘመድ ካለ ብር ሊሸል መው እንደሚችል አጫውቶናል።
ወዬ ባዮች ድንገተኛ አደጋ ደርሶበት ለሞተ ሰው የሚያወርዱትን የሙሾ ግጥም አንድ እንጠቁምና ሀሳባችንን እንቋጭ።
እናዋይ እከሌስ ታስረው ታስረው ሄዱ በጭራ ገመድ፣
ታስረው ታስረው ሄዱ በቱሻ ገመድ፣
ወደውም አይደለም ተይዘው በግድ። ይህ ማለት ሞቱን የሚሟገቱት፤ የሚያስ ቆሙት እንዳልሆነ ለመንገር ነው። በተለይም ላስታመው፤ ላቅናው፣ ላንሳው ሳይባል ድንገትም እንደሚወሰድ ለማሳየት ሲባል ይህ ግጥም በሙሾ መልክ ይደረደራል።
አዲስ ዘመን ሰኔ 23/2011
ጽጌረዳ ጫንያለው