ፍቅር ረቂቅ ነው፤ ከስሜት ይልቃል። ልብን ሰቅዞ የሚይዝ ረቂቅ መንፈስ ነው፡፡ ፍቅር ይሉኝታ አያውቅም፤ ዕ ድ ሜ አ ይ ገ ድ በ ው ም ፡ ፡ ቦ ታ አይመርጥም። ጨለማን እንደብርሃን፣ የጋመ ምጣድን እንደቀዘቀዘ ውሃ አድርጎም ያሳየናል። ዘመናትን አሻግረን እንድንመለከትም ያግዘናል። እናም ይህን ፍቅር ከባህል ጋር ስናስተሳስረው ይበልጥ ኃያልነቱን ያሳየናል። ይህንን ያልኩት ያለ ምክንያት አይደለም። ፍቅርን ከሚያጸናው የባህል ጨዋታ ውስጥ እንድትገቡ በመፈለግ ነው።
በባህላዊ መንገድ ዘመናትን ተሻግሮ የዘመኑ አፍቃሪዎችን የሚያስቀና የፍቅር ጨዋታ በአገራችን ገጠራማ ቦታዎች እንደየባህሉ እናገኘዋለን። ለ አ ብ ነ ት በ ወ ሎ አ ካ ባ ቢ “ ተ በ ቺ ሳ ን “ ስ ና ነ ሳ በትግራይ ደግሞ እነ አሸንዳና አውርስ ተጠቃሾች ናቸው። በሌሎች አካባቢዎችም እንዲሁ በርካታ ያልነካናቸው ባህላዊ የፍቅር ጨዋታዎች አሉን። ለዛሬ ግን የመረጥኩት ትግራይ ውስጥ ተምቤን አካባቢ የሚከወነውን አውርስ የተባለውን ባህላዊ ጨዋታ ነው።
« አውርስ » ባህላዊ ፍቅር እና መተሳሰብ ያሉበት የጨዋታ አይነት ነው። ባህላዊ እና መንፈሳዊ ኩነቶች ይከወኑበታል። ረጅም እድሜን በደስታና በፍቅር መግለጥ የሚቻለው በአውርስ ባህላዊ ጨዋታ ውስጥ ሲታለፍ መሆኑም በባህሉ አልፈው ለወግ ማዕረግ የበቁት ምስክሮች ናቸው። እናም ታሪክን አድራጊው ሲናገር ይበልጥ ያሳምረዋልና ልብን በፍቅር አክንፎ ዓይንን በደስታ የሚገልጠው አውርስ ትርጓሜው ምን ይሆን? ስል የተለያዩ ምሁራንን አነጋግሬያለሁ።
መምህር እንባይ ጆርጆ ይባላሉ። ነዋሪነታቸው ተምቤን ውስጥ ሲሆን፤ በትግራይ አካባቢ የሚከወኑ ባህላዊ ጭፈራዎችንም ሆነ ሌሎች ባህልን የተመለከቱ ጉዳዮችን ለትውልድ በማሸ ጋገር አንቱታን ያተረፉ ናቸው። እናም ስለ አውርስም እንዲህ ነበር ያሉኝ።
አውርስ ማለት ተካኝ፤ ውረስ፤ ደግሞ አንተ ተጨዋት ማለት ነው። ይህ ትርጉም የተሰጠውም ጥንዶች እየተጫወቱ ሲደክማቸው ተተኪ ተጨዋች በማስፈለጉ ደግሞ አንተ ተከተል ለማለት ሲፈልጉ አውርስ ብለውታል። ውርስ እንደሚታወቀው ከትውልድ ወደ ትውልድ መሸጋገር ማለት ነው። ስለዚህም አውርስም ከጥንዶቹ ተጨዋቾች ወደሌላው ተጫዋቾች መዘዋወርን ያመለክታል ይላሉ።
በአውርስ ባህላዊ ጨዋታ ቆነጃጅት ባል የሚያገኙበት ለትዳር የደረሱ ወንዶችም እጮኛ የሚመርጡበት፣ በርካታ ማህበራዊ ትስስሮች የሚፈጠርበት ነው። ለመሆኑ ይህ አጨዋወትስ እንዴት ይተገበራል ከተባለ መልሱ እንደየሰፈሩ ሁኔታ ይለያል ነው። አንዳንድ የጨዋታ ቦታ ክብ ሰርቶ ጨዋታውን በመመልከት የሚደሰት እና ለማድመቅ የሚያጨበጭብ ሰው ይኖራል።
በመካከል ደግሞ አንድ ከበሮ መቺ ይቀመጣል። ከዚያ ጎረምሳው የወደዳትን ኮረዳ ይጎትትና ገብተው ጭፈራውን ያስነካሉ። ሲደክማቸው ሌላ ተተኪ በትግሪኛ «ሆረስ» በማለት ጨዋታውን እንዲወርስ ይደረጋል። እርሱም ሲደክመው እንደቀደመው ተጫዋቾች ሁሉ ከሜዳው ይወጣና ሌሎች ይተካሉ።
በአንዳንድ አካባቢ ደግሞ ክብ መስራት ሳይጠበቅባቸው ሁለት ሁለት እየሆኑ ሊጫወቱ ይችላሉ፤ በአውርስ ጨዋታ መወራረስ ግድ ስለሆነ በብዛት ሆኖ መጫወት አይፈቀድም። የራሱ የአለባበስ ህግም ያለው መሆኑን ይናገራሉ። ሴት ልጅ ወደ ጨዋታው ስትሄድ ከሀበሻ ጨርቅ የተሰራ ልብስ ትለብሳለች። በአንገቷ ላይ ሶስት ነገሮችን ትደረድራለች። እነዚህም እንቆ መስቀል፤ ደብር መስቀል፤ ባቡር መስቀል የሚባሉ ናቸው። ከዚያ እንቁ ፣ ድሪ፣ ጉርር የሚባሉ ጌጦችን ታደርጋለች። በግራ እጇ ላይም የምታደርገው ጌጥ አለ።
ያገባች፣ ያላገባችና የታጨች የሚለውን ለመለየት የሚያስችል የጸጉር አሰራር ከተሰራች በኋላ በግንባሯ ላይ ህምድድ የተባለ ጌጥ ታጠልቃለች። ወደ እግሯ ሲወረድ ብዙ ጊዜ የምታጠልቀውም ቢሆን አልቦ ልታደርግ ትችላለች። ይሁንና ለዚህ ተብሎ እግር ላይ የሚጠለቅ ነገር እንደሌለ መምህር እንባይ ይናገራሉ። ይህ ጌጣጌጥም ሆነ ልብሱ በሌሎች አካባቢዎች ሊደረግ ይችላል። ልክ ከአውርስ ጋር ተመሳሳይነት ያላቸው በትግራይ አካባቢ በሚከበሩ እንደ አሸንዳ አይነት በዓላት ላይ።
“ወንዶች የተለየ አለባበስ አይለብሱም በማንኛውም የትግራይ አካባቢ እንደሚለብሱት አይነት አለባበስ ነው” የሚኖራቸው የሚሉት መምህር እንባይ፤ ለዚህ ቀን ግን በተለይ እጮኛ የሚፈልግ ወንድ ደመቅና ለየት ብሎ መታየት እንዳለበት ይናገራሉ። ይህንን የማያደርግ ከሆነ ግን የጨዋታ አድማቂና የባህሉ አሻጋሪ ሰዎች ይተቹታል። የሚመርጣት ቆንጆም እሺ ብላ ፈቅጃለሁ ልትለው አትችልም። እናም ከመቼውም በበለጠ አምሮ መውጣት እንዳለበት አጫውተውኛል።
ለመሆኑ ምን ምን እያሉ ይጫወታሉ? ስል መምህርቷን ጠይቄያቸው ነበር። የሚያምረው በባህሉ ቋንቋ ሲሆን ነው። በአማርኛው ግን ቤት ላይመታ ይችላል። ይሁንና ሀሳቡ እንዲህ ነው ይላሉ። ግን በትግሪኛ መሆኑን እንዳትዘነጉት። ምክንያቱም የባህሉ ባለቤቶች ተምቤኖች ናቸው።
“ሳብ ረገብ አድርጎ ይሰራል ሸማኔ ፣
የፍቅር ዋስ የለው እንዴት ልሁን እኔ፡፡
ከዚያም ከዚያም ያልኩት ሆዳምነቴ ነው፣
አንጀቴን አስሬ ብጠብቅሽ ምነው፡፡” አፍቃሪው ማለት ነው ይህንን ያለው። (ትንሽ ማስተካከያ ተደርጎበታል) ።
”በአውርስ ጨዋታ ውስጥ እየተጫወቱ ያሉት ጥንዶች ብቻ አይደሉም እንዲተኩዋቸው የሚጠይቁት። ከውጪ ያለውም አካል «ሆረስ» ማለት ይችላል። ቀድሞ የገባው ደከመው፣ አልደከመው በህጉ መሰረት ሆረስ ከተባለበት ማንገራገር አይችልም። ቦታ ይለቃል“ ያሉኝ ደግሞ በአዲግራት ዩኒቨርሲቲ መምህር ዶክተር ገብረመድህን ሮምሃ ናቸው።
እርሳቸውእንደሚሉት፤ «አውርስ» ባህላዊ ጨዋታ እጅግ ረጅም እድሜ ያስቆጠረ ሲሆን፤ የአካባቢውነዋሪዎች እየተቀባበሉ አሁን እስካለንበት ዘመን የደረሰ ነው። እንደውም በአክሱም ዘመነ መንግስት ጣኦታትን ሲያከብሩ የሚከወንም እንደነበር ይነገራል። ሆኖም የአካባቢው ነዋሪ ሀይማኖተኛ በመሆኑ ሳቢያ ዛሬ ከኦርቶዶክስ እምነት ጋር አቆራኝተውት እያከበሩት ይገኛሉ። እንደውም በክረምት ፍልሰታ ማለትም ከነሐሴ 16 እስከ መስከረም 16 እንዲከበርም ሆኗል።
አውርስ ልክ እንደ አሸንዳ፣ ሻደይና ሶለን ወዘተአይነትባህላዊ ትውፊት ያለው ነው፡፡ በዋናነት በተምቤይ ወረዳ የሚከወን ሲሆን፤ ልጃገረድ ሴቶች እና ጎረምሶች በአካባቢው አጠራር‹‹ኮበሌዎች›› የከንፈር ወዳጅ በሚይዙበት ወቅት የሚከወን ስርዓትም እንደሆነ ይነገራል። ይህ ባህላዊ ጨዋታ ከዚያም ያለፈ ተግባር አለው የሚሉት ዶክተር ገብረመድህን፤ ስርዓቱን ብዙ ጊዜ ትልልቆች ተገኝተውበት ባህሉን የሚያስተላልፉበትም እንደሆነ ያስረዳሉ።
የአውርስ ባህላዊ ጨዋታ እንደሌሎቹ ባህላዊ ጨዋታ አይነቶች በቀን የሚከወን አይደለም። ምክንያቱ ደግሞ ቀን ላይ በብዙዎቹ ነዋሪዎች ሥራ ላይ ናቸው። ስለዚህም ምሽት ላይ የተዳከመ ሰውነት በሙዚቃና በባህላዊ ጨዋታ ለማሳረፍ ይጠቀሙበታል። የደከመ አዕምሮም እረፍት እንዲያገኝና ከልብ ሆኖ ጨዋታው እንዲከናወን ለማድረግ ሲባል ይህ ጊዜ ተመርጧል።
በአውርስ ባህላዊ ጨዋታ ትልቅ ሰዎች እየተዝናኑ ባህሉን የሚያሳውቁበት ነው። ማህበራዊ መስተጋብሮችም የሚጠናከርበት ነው። በተለይም በመጨረሻው ቀን ማለትም በደመራ እለት ምግብና መጠጥ በስፋት ስለሚቀርብና ድግስ ስለሚደገስ የተጣላ የሚታረቅበት፤ ማህበራዊ ችግሮች የሚፈቱበትና ለወደፊት የትዳር አጋርን መርጦ የሚመቻችበት ነው። እናም ይህ አስደናቂ ባህላዊ የፍቅር ጨዋታ አሁንም ድረስ እየተከወነ ነውና ተመልካች ያሸዋል። ምክንያቱም ከባህሉ ባለቤቶች ውጪ የሚያውቀው ሰው የለም። ስለዚህ የሚመለከታቸው አካላት ሊያሳውቁት እንደሚገባም ዶክተር ገብረመድህን ይናገራሉ።
ረጅም ዓመት ያስቆጠረውን ይሄን ባህል ከነ ሙሉ ክብሩ ለማቆየት እና ለሌላው ማህበረሰብ ለማስተዋወቅ እርስዎም ቢያዩት፤ ልርሳው ቢሉ የማይረሱትን ትዝታ ያቀዳጅዎታልና መመልከትዎ መልካም ነው እላለሁ። በባህል ፍቅር የተመቱት አያምም፡፡ በባህል ፍቅር የተኮሱት ጥይት አይጮህም፤ ቢጮህም ለጆሮ አይሰቀጥጥም እንዲሉ አበው ሰላም ከፍቅር ጋር፣ ባህልም ከእምነትና ተግባር ጋር ሲዋሃድ በታሪኩ የሚሸማቀቅ ሳይሆን የሚኮራ ህዝብን ይፈጥራልና በዚህ ለመፈጠር እንጣር እያልኩ ለዛሬ የያዝኩትን በዚህ ቋጨሁ። ሰላም!
አዲስ ዘመን ሰኔ 8/2011
ጽጌረዳ ጫንያለው