የኢራን የኑክሌር ልማት መርሃግብር ለማስቆም፤ እኤአ በ2015 በኢራንና በስድስቱ የዓለማችን ኃያላን አገራት በአሜሪካ፣ ቻይና፣ ሩስያ፣ ጀርመን፣ ብሪታኒያና ፈረንሳይ መካከል ስምምነት ተደርሷል። በስምምነቱ መሰረትም ኢራን የዩራንየም ክምችቷን መቀነስን ጨምሮ የኑክሊዬር መርሃግብሯ ላይ የተለያዩ ማሻሻያዎችን ለማድረግ ወስና ይህንንም በፊርማዋ አረጋግጣለች።
ከሁለት ዓመት በፊት ወደ ነጩ ቤተ መንግሥት የገቡትና በ‹አሜሪካ ትቅደም› መርሃቸው አገራቸው የዓለም መሪና አስተባባሪ እንድትሆን አጥብቀው የሚመኙት ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በአንፃሩ፤ ኢራን የተወሰነውን የስምምነቱን አካል እንዳላከበረችና የኑክሌር መርሀግብሯን ከበጎው ይልቅ ለክፉ አላማ እንደምትቀምረው ያምናሉ።
እናም በምርጫ ቅስቀሳቸው ቃል በገቡት መሰረት ኢራን የተወሰነውን የስምምነቱን አካል እንዳላከበረች በመግለፅ ከዓመት በፊት ፊርማቸውን በይፋ ቀደዋል። በዚህ ብቻ ሳያቆሙም ከአንድ ዓመት ቀድሞ በኢራን ላይ ጠንካራ ማዕቀብን አውጀዋል።
አገራቸው ያለፉትን ዓመታት የስምምነቱን ቃል ጠብቃ ሰለመቆየቷ በተደጋጋሚ ሲወተውቱ የሰነበቱት የኢራኑ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሮሃኒም፣ የዋንሽግተን መንግሥት ከማውገዝ ባለፈ «ውሳኔው ህጋዊነት የሌለውና የዓለም ዓቀፍ ህግን የሚጻረር፤ እንዲሁም ቴሄራን በስምምነቱ የገባችውን ቃል እንድታጥፍ የሚገፋፋ ነው» ሲሉም ተደምጠዋል።
የስምምነቱ ተሳታፊዎች አውሮፓውያኑም ቢሆኑ «ስምምነቱ እጅግ ወሳኝና ጠቃሚ የሆነ ዲፕሎማሲያዊ ድል በመሆኑ የተሻለ አማራጭ ካልተገኘ በስተቀር ሊጣስ አይገባም» በሚል ቴሄራን በቃሏ እንድትፀናና ዋሽንግተንም አቋሟን ዳግም እንድታጤን ሲወተውቱ ቆይተዋል።
አሜሪካ በአንፃሩ፤ የማእቀብ ማሻሻያ ልታደርግ የምትችለውና አዲስ ስምምነትም የሚደረሰው፤ ቴሄራን ለየመን አማፂያን የምታደርገውን ድጋፍ ከማቆም አንስቶ የተለያዩ የአቋምና የፖሊሲ ለውጦችን ስታዳርግ ነው በሚል በተደጋጋሚ ገልፃለች።
ከታወጀ አንድ ዓመት ያስቆጠረውና የኢራንን የኢኮኖሚ አውታሮች ትኩረቱን በማድረግ በተለይ የቴሄራንን የነዳጅ ሀብት ከጨዋታ ማስወጣትን ዋነኛው ትኩረቱ ያደረገው ይህ ማዕቀብም፤ የኢራን ህዝብም ቁጡ ሆኖ መንግሥቱ ላይ እንዲነሳና የፕሬዚዳንት ሃሰን ሮሃኒ መንግሥት ተዳክሞ ወደ ድርድር ጠረጴዛው እንዲጠጋ ማስገደድን ዋነኛ ዓላማው አድርጎም ታይቷል።
በዚህ የልዕለ ሃያሏ አገር ቀመር የተተበተበችው ቴሄራንም፣ ላለፈው አንድ ዓመት የዋሽንግተንን የማዕቀብ ጡንቻ ለመቋቋም ብዙ ደክማለች። ምንም እንኳን እጇን ለመስጠት ባትፈቀድም፤ ማዕቀቡ ኢንቨስተሮቿ ጓዛቸውን ሸክፈው እንዲሸሿትና የፋይናንስ ተቋማቷ ካዝናም እንዲራቆት በማድረግ ህልውናዋን ክፉኛ ፈትኖታል።
ማዕቀቡ ሲበረታባትም አማራጭ የምትላቸውን መፍትሔዎችን በመከተል፤ በተለይ የአሜሪካ ተቀናቃኝ ናቸው ወደሚባሉት ቻይና እና ሩሲያ ተጠግታም ታይታለች። ይህን ያስተዋለችው ዋሽንግተንም፤ ይባስ ብሎ ባሳለፍነው ወር ከኢራን ጋር የንግድ አጋርነታችውን ያላቋረጡ በተለይ ነዳጅ ተገበያይ አምስት አገራትን ይፋ አድርጋለች።
በዚህ ብቻ ሳትወሰንም አገራቱ ግንኙነታቸውን እስካላቋረጡ የኢራንን እጣ እንደሚከተላቸው «እወቁልኝ» ያለች ሲሆን፣ አንዳንድ አገራትም መጪውን በመፍራት ጎመን በጤና ማለትን መርጠው ታይተዋል። ይህ ደግሞ ኢራንን በበለጠ አጣብቂኝ ውስጥ አስግብቷታል። በሀገራቱ መካከል ነግሶ የቆየውን አለመግባባት ይበልጡን አሳድጎታል።
የአገራቱ ጡዘት ከመቀዝቀዝ ይልቅ ይበልጥ በሞቀበት በዚህ ወቅትም፤ ባሳልፈነው ወር አሜሪካ የኢራን አብዮት ዘብ ጠባቂ ወታደሮችን በአሸባሪነት የፈረጀች ሲሆን፣ በተመሳሳይ ኢራንም አሜሪካ በመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ያሰማራቻቸውን የሰላም አስከባሪ ወታደሮች በአሸባሪነት ፈርጃለች።
በእርግጥ ምንም እንኳን የአገራቱ ልዩነት እያደር እየጨመረ ቢመጣም ፍጥጫቸው ግን ቦታ ለይተው ጦር እንዲማዘዙ የማድረግ እቅም ሳያገኝ ቆይቷል። ከቀናት በፊት የተከሰተው ግን ምናልባትም አገራቱ «ጦር የሚማዘዙበት ትክክለኛው ሰዓት ላይ ደርሰዋል» የሚሉ መገናኛ ብዙሃንና የፖለቲካ ተንታኞች እንዲበራከቱ ምክንያት ሆኗል።
ባሳለፍነው ሳምንት ማለትም አሜሪካ ከኑክሌር ስምምነት ከወጣች ልክ አንድ ዓመት ሲቆጠር የኢራኑ ፕሬዚዳንት ሃሰን ሮሃኒ፤ ሀገራቸው ከ2015ቱ የኑክሌር ስምምነት በከፊል ራሷን በማግለል ዩራኒየም ማበልጸጓን ልትቀጥል እንደምትችል አስታውቀዋል። የኢራንን ውሳኔ በርካቶች አስደንጋጩ ያሉት ሲሆን፣ ምክንያታቸውም ደግሞ ቴሄራን በስምምነቱ ካልፀናች መጪው ጊዜ ሊታሰብ ከሚችለው በላይ የጥፋት መሆኑ አይቀርም የሚል ሆኗል።
«እኛ ለ2015ቱ የኑክሌር ስምምነት ተፈፃሚነት ቃላችንን አክብረን ተጉዘናል፤ ይሁንና ቃላችሁን አልጠበቃችሁም ተብሎ ማዕቀብ ተወስኖብናል፡፡ ይህም ቴሄራን በታሪኳ አይታው በማታውቀው ምናልባትም ከ1980ዎቹ የኢራቅ ጦርነት ወቅቶችም በባሰ ኢኮኖሚዋን ክፉኛ ጎድቶታል» ብለዋል። ይህን የፕሬዚዳንቱን ቃል ያደመጡ መገናኛ ብዙሃንም በተለይ እየሩሳሌም ፖስት «የዶናልድ ትራምፕ የኢኮኖሚ ማዕቀብ ውጤታማ መሆን ጀምሯል» ሲሉ አስነብቧል።
የቴሄራን ‹‹ከስምምነቱ እወጣለሁ›› ውሳኔና የፕሬዚዳንቱ አቋም ያላማራቸው አገራትም ውሳኔውን ለመኮነን ብዙ ጊዜያትን አላባከኑም። በተለይ የፈረንሳይ፣ እንግሊዝና ጀርመን፤ ኢራን በስምምነቱ እንድትቆይ በመወተወት ተጠምደዋል። ቻይና እና ሩሲያ በአንፃሩ አሜሪካን ኢራንን ለማንበርከክ የቀመረችው የማዕቀብ ቀመር ቅጥ ያጣና ቴሄራን ህልውና የሚፈትን አቋሟንም የሚያስቀይር ነው ሲሉ ኮንነዋል።
«ቴሄራን ለ2015ቱ የኑክሌር ስምምነት ተፈፃሚነት ቃሏን ጠበቃ ስትጓዝ በአፀፋው ምንም ከለላና ዋስትና አሊያም ጥቅም አላገኘችም» ያሉት ሩሃኒ፣ ይህ እስከሆነም የስምምነቱ አባሪዎች አስፈላጊውን ሁሉ በማድረግ ከዋሽንግተን የማዕቀቡ ጡንቻ ሊታደጓቸው እንደሚገባም ጥያቄ አዘል ትዕዛዝ አስተላልፈዋል።
ቻይና እና ሩሲያን ጨምሮ አውሮፓውያኑ በስልሳ ቀናት ውስጥ የኢራን የነዳጅ አቅርቦትና የፋይናንስ ተቋማትን ለመጠበቅ ቃላቸውን ሊሰጧቸው እንደሚገባም አስታውቀዋል። የዋሽንግተኑ አስተዳደር በሌላ በኩል ለዚህ መልስ በሚመስል መልኩ በኢራን የብረት፣ አሊሙኒየም፣ ኮፐርና ሌሎች ሴክተሮች ላይ አዲስ ማዕቀብን ማሰናዳቱን እውቁልኝ» ብሏል።
የሁለቱ አገራት እስጣ ገባ መጋልም አሜሪካ ከቀናት በፊት ኢራን ለምታደርገው ትንኮሳ አፀፋዊ ምላሽ መስጠት የሚያስችል ነው በሚል B-52 የተባሉ ከባድ ቦንብ ጣይ አውሮፕላኖች የጦር መሳሪያና ወታደሮችን የጫኑ መርከቦች ወደ መካከለኛው ምስራቅ መላኳ ዋነኛው ምክንያት መሆኑም ታውቋል።
ይህን የአሜሪካ እርምጃ ተከትሎ የኢራን ብሔራዊ ደህንነት ቃል አቀባይ ኬይቫን ኮህስራቪ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫም አሜሪካ ኢራንን በስነ ልቦና ጦርነት ለማንበርከክ የምታደርገው እንቅስቃሴ ከንቱ ድካምና ጊዜው ያለፈበ፤ ኢራን የደረሰችበትን ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበና የወቅቱን የስነ ልቦና ጦርነት የማይመጥን ነው» ሲሉ አጣጥለውታል።
በተለይ የዋሽንግተኑ አስተዳደር ወታደሮቹን ወደ መካከለኛው ምስራቅ ማስጠጋት ሁለቱን አገራት እልህ በማጋባት ለጠብ አጫሪነት እጃቸውን እንዲሰበስቡና በመካከለኛው ምስራቅ የወታደራዊ ፍልሚያ ሊያስጀምር እንደሚችልም ተመላክቷል።
ከጦርነቱ ይልቅ ስምምነቱን ለማዳን ስለሚቻልበት መንገድ የሚያትቱ መገናኛ ብዙሃንም በርካቶች ሆነዋል። የፖለቲካ ሳይንቲስት የሆነችው አርያና ታባታቢ ከእነዚህ አንዷ ነች። ፀሐፊዋ ኒውዮርክ ታይምስ ላይ ባሰፈረችው ሀተታም፤ ምናልባት እድለኛ ከሆኑ የአውሮፓ ህብረት ስምምነቱን ማዳን እንደሚቻላቸው አብራርታለች።
«አውሮፓውያኑ ከኢራን ጎን ወግነው ከዓለም የኢኮኖሚ ዘዋሪዋ ጋር መቃቃርን አይሹም፤ ከዚህ የሚያፈነግጡ ከሆነም በግዙፉ የአሜሪካ ገበያ ውስጥ የሚኖራቸው ተሳትፎን ሊከለከሉ እንደሚችሉ ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ በኢራን ላይ ፊታቸውን የሚያጠቁሩ ከሆነ ደግሞ ቴሄራን በስምምነቱ አትቅጥልም፡፡›› የምትለው ፀሐፊዋ፤ አውሮፓውያኑ በዚህ አጣብቂኝ ውስጥ ስምምነቱን የመታደግ ከባድ ኃላፊነት መሸከማቸውን አትታለች።
ይህም ሆኖ አውሮፓውያኑ ጉዳዩን በሰከነና ብልጠት በተሞላበት አኳኋን ማስፈፀም እንደሚችሉ ያመላከተችው ፀሐፊዋ፤ በቴሄራንና በዋሽንግተን መካከል አለመግባባትና አለመረዳዳት ከመከሰቱና አስከፊው ፍልሚያ ከመምጣቱ ቀድሞ በጣልቃ ገብነት አደራዳሪነት ሚናቸውን በማጎልበት ነገሩን ማለዘብ እንደሚችሉ አብራርታለች።
በአጠቃላይ በዋሽንግተንና ቴሄራን መካከል የሚስተዋለው ፍጥጫ እያየለ በመጣባት በዚህ ወቅት በተለይ ኢራን በስምምነቱ እንድትፀና በማሳመን ረገድ አውሮፓውያኑ፣ ቻይና እንዲሁም ሩሲያ የሚጓዙት ርቀትና የሚያሳዩት አቋም ብዙዎችን በጉጉት የሚጠበቁት ሆኗል። አስደንጋጩ የኢራን ውሳኔም ነገ ምን አስክትሎ ይመጣል የሚለው የበርካቶች ጥያቄም ስጋትም ሆኗል።
አዲስ ዘመን ግንቦት 6/2011
በታምራት ተስፋዬ