ሲስተር ይርገዱ ሀብቱ ለቤተሰባቸው ሶስተኛ ልጅ ሲሆኑ፤ ከሆለታ ከተማ በ7 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኝ ገጠር ውስጥ ነው የተወለዱት። ከአርሶ አደር ቤተሰቦቻቸው ጋር በጥሩ ፍቅርና ስነ ምግባር አድገዋልም። ኋላም እድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ አያቶቻቸው ለአካባቢው ነዋሪዎች ባስገነቡት አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸው እንዲጀምሩ ሆነዋል። እስከ ስድስተኛ ክፍል ድረስ ያለውን ትምህርታቸውን በዚሁ ትምህርት ቤት ተከታትለዋል።
“… የድሮ ቤተሰብ እንደ አሁኑ አይደለም፤ አንዳንዶች ጭራሽ ትምህርት ለማስተማርም ላያስቡ ይችላሉ። ግን ደግሞ ትምህርት ማስተማር አለብን ብለው የሚነሱት እንደእኔ አይነት ቤተሰቦችም ቢሆኑ ስለትምህርት ጥቅም ጠለቅ ያለ እውቀት አይኖራቸውም። ይህ ደግሞ የልጃቸውን እጅ ይዘው ትምህርት ቤት አስገብተው ከመመለስ ውጪ የሚያደርጉት ነገር እንዳይኖር ያደርጋቸዋል። እኔም በወቅቱ ወላጆቼ እጄን ይዘው ትምህርት ቤት አስገቡኝ እንጂ ከዚያ ባለፈ ያደረጉልኝ ምንም ነገር አልነበረምና ሙሉ በሙሉ የራሴው ጥረት ነበር የሚንጸባረቀው” በማለት የትምህርት ጅማሯቸውን ያስታውሳሉ።
ሲስተር ይርገዱ በዚህ መልኩ የተቀላቀሉትን የትምህርት ዓለም በጣም የተመቻቸ ባይሆንላቸውም ብዙ አላስከፋቸውም። ትምህርትም ይወዱ ስለነበር ችግሮቹን ሁሉ እየተጋፈጡ ማለፍ ችለው ነበር። ምክንያቱም በአያቶቻቸው ትምህርት ቤት እስከ ስድስተኛ ክፍል ያለውን የትምህርት ሂደታቸውን ከአጠናቀቁ በኋላ ሰባተኛ ክፍል ላይ ሌላ የትምህርት ዓለምን ነው የተቀላቀሉት። ሌላ የሕይወት ገጽታን ያዩበትም ሆኖ ነው ያለፈው። ያንን ሲያስታውሱም እንዲህ ነበር ያሉት ‹‹…ሰባተኛ ክፍል ከገባሁ በኋላ ትምህርት ቤቱ ከመንደራችን የሰባት ኪሎ ሜትር ያህል ርቀት ነበረውና በቀን ውስጥ ስሄድ ስመጣ 14 ኪሎ ሜትር በእግር እጓዝ ነበር። በጉዞው ተሰላችቼ ትምህርቴን አላቋረጥኩም። ይልቁንም ከጓደኞቼ ጋር ቀጠልኩት” ይላሉ።
እሳቸውና መሰሎቻቸው ብዙ ኪሎ ሜትሮችን በእግራቸው አቋርጠው መሄዳቸው ነገን ለማሳመር መሆኑ በእጅጉ ገብቷቸዋል። በዚህም ምንም ዓይነት ቅሬታ አይሰማቸውም። የሚገርመው ነገር ደግሞ ያንን ሁሉ ኪሎ ሜትር አቋርጠው ሄደው ተምረው ሲመለሱ ቤት የሴቶች ሥራ ይጠብቃቸዋል። በዚህም ተቃውሞ የላቸውም። ቤተሰቦቻቸው ስለ ትምህርት እምብዛው ግንዛቤው አልነበራቸውምና ማታ ኩራዝ አብርቶ ጋዝ እየጨረሱ ማጥናት አይፈቀድም። ይህም ቢሆን አንድም ቀን ተስፋ አያስቆርጣቸውም። ይልቁንም ሲስተርና ጓደኞቻቸው ትምህርታቸውን የሚያጠኑበትን፣ የቤት ሥራቸውን የሚሰሩበትን መላ ዘየዱ እንጂ።
“…እንደ ነገርኩሽ የእኔም ሆኑ የሌሎች ጓደኞቼ ወላጆች ስለ ትምህርት የነበራቸው ግንዛቤ ውስን በመሆኑ ልጅን ትምህርት ቤት ከመላክ ባለፈ የሚያግዙት ነገር አልነበረም። እንደውም ጋዝ አትጨርሱ በሚል ማታ ኩራዝ አብርቶ ሁሉ ማጥናት አይፈቀድም። ነገር ግን እኔና ጓደኞቼ ያንን ሁሉ ኪሎ ሜትር በእግራችን አቋርጠን ስንመጣ ምንም ዓይነት ከትምህርት ውጭ የሆነ ወሬ አናወራም፤ የተማርነውን እንጠያየቃለን ቆም እያልን የቤት ሥራችንን እንጨርሳለን፤ እንዲህ እንዲህ እያልን ጊዜያችንን በአግባቡ በመጠቀም ነበር የምንማረው” ይላሉ።
በራሳቸው ጥረት የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተናን የወሰዱት ሲስተር ይርገዱ፤ የትምህርት ውጤታቸው የነርስነት ሙያን ለመማር የሚያበቃ ነበርና በ1972 ዓ.ም በቀጥታ ወደ ነርሲንግ ትምህርት ቤት አመሩ። ምንም እንኳን ነርስ የመሆን ፍላጎት ባይኖራቸውም አንድ የትምህርት መስክን መርጦ ሥራ የመግባት ፍላጎቱ ስለነበራቸው ትምህርቱን መከታተል ጀመሩ።
“…ወደ ነርስነት ሙያ የገባሁት ተምሬ ሥራ ለመያዝ ካለኝ ፍላጎት እንጂ የልጅነት ህልሜ ሆኖ አልነበረም፤ ነገር ግን ከገባሁበት በኋላ በጣም ወደድኩት፤ ትምህርቱም ላይ ሆኜ ታካሚዎች በህመም ሲሰቃዩ ሳይ፤ በምንኖርበት አካባቢም እናት የእንግዴ ልጇ ለይቶ የሚያወጣላት አጥታ ሕይወቷን ስታጣ ያየሁትና የሰማሁት ነገር ሁሉ ፊቴ ይመጣ ጀመር። ከዚያ በኋላ እንደውም ከመውደድም አልፌ ምነው ቀደም ብዬ ነርስ ሆኜ በነበረ እረዳቸው ነበር ሁሉ ብዬ መቆጨት ጀመርኩ። በዚህም ከእለት እለት ፍላጎቴ እየጨመረ ሄደ” በማለት ሁኔታውን ይገልጹታል።
የነርስነት ትምህርታቸውን በወለጋ ነቀምት ነርስ ትምህርት ቤት የተከታተሉት ሲስተር ይርገዱ፤ በተለይም የመጀመሪያዎቹን ስድስት ወራት አካባቢን ለመልመድ ብሎም ከትምህርቱ ጋር እስኪዋሃዱ ድረስ ከፍ ያለ ጊዜን ወስዶባቸው እንደነበር ያስታውሳሉ። እንዲያውም አስጨንቋቸው እንደነበር አይረሱትም። ‹‹…እንግዲህ ትምህርት በገጠር በራስ ጥረት የሚታለፍ ነው ፤ ቤተሰብም ልጆቹን ትምህርት ቤት ላክሁ ከማለት ውጭ የሚወረውረው ጠጠር የለም። እንደውም ልጆች ከትምህርት ሲመለሱ የቤቱን ሥራ እንዲያግዙ ይፈልጋሉና ምንም እንዲያጠኑ አይፈቅዱላቸውም። ስለዚህም በዚህ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሄደን ነው 12ተኛ ክፍልን ማጠናቀቅ የቻልነው። ጠንክረን ያለንን አቅም ሁሉ አሟጠን ብንጠቀም የት እንደርሳለን የሚለውን አላሰብነውም፤ ይህንን እንድናስብ እድል የሚሰጠን የለም። እናም ከፍ ወዳለ የትምህርት ደረጃ ስንገባ ሁሉም ነገር ከባድ አስጨናቂ ይሆናል። እኔም ላይ የደረሰው ይኸው ነው” ይላሉ።
ነርስ ትምህርት ቤት ገብተው መማር እንደገና የሆነባቸው ሲስተር ይጋርዱ፤ የሚችሉትን እየሞከሩ የከበዳቸውን ከመምህራኖቻቸው በተለይም ከጓደኞቻቸው ጋር ሰፊ ጊዜ ሰጥተው እያጠኑ ብዙ ተጉዘዋል። ሆኖም ከቤት ወጥተው አለማወቃቸውና የቤተሰብ ናፍቆት እንዲሁም አንዳንድ ፈታኝ ሁኔታዎች ሲደረስባቸው ግን ‹‹በቃ ይቅርብኝና ትቼ አገሬ ልግባ›› ብለው በተደጋጋሚ ተመኝተዋል። ይህንን ሲያስታውሱም “…በሁለት ልብ ውስጥ ብሆንም ጠንክሮ መስራት ግን የማያሻግረው ዳገት እንደሌለ ተረዳሁ። እንዳልኩሽ ትምህርትን የሙሉ ጊዜ ስራዬ በማድረጌ ከስድስት ወራት በኋላ ሁሉም ነገር ገብቶኝ ጎበዝ ተማሪ የምባል ሆንኩኝ” በማለት የነርስ ትምህርት ቤት ቆይታቸውን እንዲሁም ሰው ለሚማረው አልያም ለሚሰራው ሥራ ጊዜን መስጠት ከቻለ ያሰበበት የማይደርስበት ምክንያት እንደሌለ ማየታቸውን ይናገራሉ።
የነቀምት ነርስ ትምህርት ቤት ቆይታቸውን ሲያጠናቅቁ የተመደቡት በአዲስ አበባ አቃቂ ጤና ጣቢያ ሲሆን፤ ህበረተሰቡን በትጋት እያገለገሉ ሶስት ዓመት ከስድስት ወር አካባቢ የሰሩበት ነው። በወቅቱ በተመደቡበት ጤና ጣቢያ ሀኪም እንደልብ ስለማይገኝ የሀኪሞቹን ቦታ ሸፍነው ይሰሩ ነበርም። ይህ ደግሞ ለሥራው እንዲጨነቁ ሁሌ ሲነጋ አዲስ እውቀት እንዲይዙ አድርጓቸዋል። በሥራ ገበታቸው ላይ ለመገኘት በጣም አንባቢ መሆን እንዳለባቸውም ያስገነዘባቸው ነው።
በሽተኛን ችግሩን ለይቶ ለማወቅ ለዛ ሊሆን የሚችል መድሃኒት ለማዘዝ የግድ ንባብ ያስፈልጋል። ያንን ደግሞ ሁሌም በስኬታማነት ለማጠናቀቅ ይጥሩ ነበር፤ አድርገውታልም። ይህ ደግሞ የነበራቸውን እውቀት ከፍ ከማድረጉ ባሻገር ለሥራው ያላቸውን ፍላጎት በሚገባ እንዲወጡበት አግዟቸዋል። ይህ የሥራ ትጋታቸው እንዲሁም ለሙያው ያላቸው ፍላጎት በአለቆቻቸው ዓይን ጥሩ ግምት አሰጥቷቸውም ወዲያው በ1978 ዓ.ም ወደ ጳውሎስ ሆስፒታል ተዘዋወሩ። ጳውሎስ ሆስፒታልም ለ35 ዓመት ያህል አገለገሉ።
እሳቸው ይሰሩበት ከነበረበት ጤና ጣቢያ ጳውሎስ ሆስፒታል በአሰራሩም ሆነ በስፋቱ የተለየ ነው። ሲስተር ይርገዱ ግን እዛም ቢሆን በትጋት ነበር የሚያገለግሉት። ማንንም ሳይጠብቁ መሥራት ያለባቸውን ነገር ያደርጋሉ። ሆኖም አንዳንድ አስገዳጅ ሁኔታዎች ግን ያጋጥሟቸዋል። ይህም የቀደመውን የአሰራር ባህላቸውን መከተል አይችሉም። ምክያቱም ይህ ብዛት ያለው ሰው የሚስተናገድበትና ሁሉም በተሰጠው ኃላፊነት ልክ የሚጓዝበት ነው። አካሄድና አሰራሩ የተለየ ነው። ስለዚህም አሰራርን ወይንም ደግሞ ተዋረድን ጠብቀው መስራት ግዴታቸው ነው።
‹‹…ጳውሎስ ሆስፒታል ሥራ ሲጀምር የተመደብኩት ሚሊተር ዋርድ የሚባል ክፍል ነበር። እዛ ሆኜ አንድ ሰው መጣና ህክምና ጠየቀኝ። ትኩሳቱን ለካሁ፣ ደም ምርመራ ላኩት የላብራቶሪ ውጤቱ ሲመጣም ሰውዬው የወባ በሽታ ተገኘበት። ይህንን ተመልክቼም ራሴ መድሃኒት አዘዝኩለት። በዚህ ተግባሬ ደግሞ በማግስቱ ተከሰስኩ። ተከስሼ የቀረብኩባት ኃላፊም በትህትና ተቀብላኝ ቀድሞ የነበርኩበትና አሁኑ ያለሁበት ሁኔታ የተለያየ የሥራ ቅደም ተከተል እንዳለው፤ ሀኪሞች በብዛት ስላሉም እነሱም ሥራቸውን እንደሚሰሩ በመናገር እኔም በሀኪሞቹ ስር ሆኜ ሥራዬን ማከናወን እንዳለብኝ ነገረችኝ” በማለት ጳውሎስ ሆስፒታል ሥራ ሲጀምሩ ያጋጠማቸውን ያብራራሉ።
በዚህ ሁኔታ ሥራቸውን እየሰሩ በሆስፒታሉ አሉ የተባሉ ሀኪም ሆነው የቀጠሉት ሲስተር ይርገዱ፤ በተከታታይ ታታሪና ምስጉን ተብለው ተሸልመዋል። ልክ በ50 ዓመት እድሜያቸውም በዲፕሎማ ቀርቶ የነበረውን ትምህርታቸውን እንደገና በመጀመር ወደ ዲግሪ ደረጃ ከፍ አድርገዋል። ይህንን ደረጃ ከያዙ በኋላ ሌላኛውን ኃላፊነት ወደመሸከሙ ገቡ። ይህም የቤተሰብ ኃላፊነት ሲሆን፤ ወደ ትዳር ገብተው የራሳቸውን ቤተሰብ ማቆም ጀመሩ።
የትዳር ምስረታ
ሲስተር ይርገዱ ትምህርታቸውን አጠናቀው ወደ ሥራው ዓለም የተቀላቀሉት በ1975 ዓ.ም ነው። በዚሁ ዓመትም ትዳር መስርተዋል። ዘንድሮም በትዳር 40 ዓመት ሆኗቸዋል። “…ትዳር ከባድ ነው ፤ ባልና ሚስት የሚሆኑት ሰዎች አብረው ከመሆናቸው በፊት ሁሉም በየፊናቸው ያደጉበት አስተሳሰብ፣ ባህል ፣ወግ የቤተሰብ ሁኔታና ሌላም ሌላም ነገር አለ። ትዳር ደግሞ እነዚህን ሁሉ ሁኔታዎች አስማምቶና አስታርቆ መሄድን የሚጠይቅ ተቋም ነው። እኛም እንደማንኛውም ባለትዳሮች እነዚህን ነገሮች አጣጥመን ትዳራችንን በጸና መሰረት ላይ ለማቆም ጊዜ ወስዶብናል።›› ይላሉ።
ይቀጥሉናም ‹‹እኔ ደግሞ እናትና አባቴ 65 ዓመታትን በትዳር ሲቆዩ እነሱ ላይ አይ የነበረው መደማመጥና መከባበርን ነበር። እኔ ጋር ስመጣ ደግሞ እንደው ትንሽ ነገር እንኳን ከተናገረኝ እንዴ አባቴ እናቴን እኮ ተናግሮ አያውቅም እልና እቆጣ ነበር ፤ ዞሮ ዞሮ ትዳር ቀላል አልነበረም ለማለት ነው። በሂደት ግን ይህ ነገር መስመሩን ይዟል። ባለቤቴ የእኔን ባህርይ ተረዳ እኔም የእርሱን አስተሳሰብ አወቅሁት። እናም በስተመጨረሻ ነገሮች እየተስተካከሉ ትዳራችን መስመር ያዘ። በዚህም አራት ወንድ ልጆችን ለመውለድ በቃን” በማለት ስለ 40 ዓመት ትዳራቸው አመሰራረት ይናገራሉ።
” …የሆስፒታል ሥራ አይደለም ልጆች ወልዶ ለማሳደግ የቤተሰብ ኃላፊነት ብቻ ለመወጣት እንኳን በጣም ከባድ ነው። ነገር ግን ወቅቱ ጥሩ ስለነበር እናትን ተክተው የቤት ሥራ እየሰሩ ልጆችን የሚንከባከቡ ልጆች ነበሩበትና ችግሮች በመጠኑም ቢሆን አልፈዋል። እንደ እናት ሳየው ግን ልጆቼን ጥዬ ሆስፒታል ሳድር ጠዋት እኔ ስመጣ እነሱ ትምህርት ቤት ሲሄዱ የማንገናኝባቸው ጊዜያት ነበሩና ቅር እሰኝ ነበር። ሆኖም ሥራ ስለሆነ ምንም ማድረግ አልችልም። በዚያ ላይ ባለቤቴም ልጆቼም ይረዱኝና ያግዙኝ ነበርና ደስተኛ ሆኜ ጊዜውን አሳልፌዋለሁም ” ይላሉ የሆስፒታል ሰራተኛ ሆኖ የቤተሰብ ኃላፊነት ሲደረብ ያለውን ፈተና ሲያስታውሱ።
ሲስተር ይርገዱ በሥራቸውም በቤተሰብ ሕይወታቸውም የተሳካላቸው ቢሆኑም በተለይም የመጨረሻው ልጃቸው ገና የአንደኛ ደረጃ ተማሪ እያለ የገጠመው የሱስ ችግር የሲስተር ይርገዱንና ቤተሰባቸውን የሕይወት ጉዞ ወደሌላ አቅጣጫ የመራው ነበር። ለአስር ዓመታት ያህል ልጃቸው እሳቸው እንዲሁም መላው ቤተሰቡ ሊያልፈው የተገደደው ችግር በቀላሉ የሚገለጽ አልነበረም። ይህም ቢሆን ግን ለሌሎች የተረፈ ሥራን እንዲሰሩ እድሉን ሰጥቷቸዋል። የብዙዎች ተስፋ መሆን የቻለም ነው። ብዙዎችን ከሞት ወደ ሕይወት የቀላቀለም ነበር። የብዙ ቤተሰቦችን እምባ ያበሰ።
“…አንዳንዶች ልጅሽ ችግር ውስጥ ባይገባ ኖሮ ለሌሎች ብርሃን የሆነውን ሥራ አትሰሪም ነበር ይሉኛል ፤ አዎ እኔም ሳስበው ሰው ሰላም ከሆነ ሆነ ነው እንዴትም ብዬ ልገባበት አልችልም ነበር፤ የሌላውንም ችግር አላይም ነበር እላለሁ። ሱስ የብዙ ሰዎች ሕይወት መመሰቃቀል፣ የትዳር መፍረስ፣ ወጣቶች እራሳቸውን የማጥፋት፣ ቤተሰብ የመበተን ምክንያት ነው።›› ያሉን እንግዳችን፤ ጳውሎስ ሆስፒታል የስነ ልቦና አማካሪ ሆነው በሚሰሩበት ጊዜ ያጋጠማቸው ነገር ስለነበር ኋላም የራሳቸው ልጅ በችግሩ ውስጥ ገብቶ ሲመለከቱት ችግር ፈቺ ለመሆን እንዳሳሰባቸው ያስረዳሉ።
አዲስ ሕይወት ለሱሰኞች
‹‹ አዲስ ሕይወት የእጽና አልኮል ሱሰኞች ማገገሚያ ማዕከልን የከፈትኩትና እዚህ ሥራ ውስጥ የገባሁት እንደነገርኩሽ የሱስን አስከፊነት ቤቴ ድረስ ገብቶ በኑሮዬ ላይ ታይቶ ስላስተማረኝ ነው። እኔ ፈጣሪ እንዲሁም ህክምና አግዞኝ ልጄ ከችግሩ ሙሉ በሙሉ ነጻ እንዲሆን አድርጌያለሁ። ያቋረጠውን ትምህርት ቀጥሎ በማዕረግ ተመርቆ ኋላም ትዳር መስርቶ የልጆች አባት ሆኖም አይቼዋለሁ። ሌሎችስ ስል ግን መልስ የለኝም። በተለይ ያልተማሩት ምን እንደሚውጣቸው ሁሌ ያሳስበኛል። ስለዚህም ከእኔ ውጭ ያስተማረው የለምና ለሌላ መትረፍ እንዳለብኝ ወሰንኩኝ። ወደስራው ስገባ ግን ምንም ነገር አልነበረኝም፤ ለራሴ የምኖርበት ቤት የምንቀሳቀስበት መኪና እንኳን የለኝም። ነገር ግን እኔም ሆንኩ ልጄ እንዲሁም መላው ቤተሰቤ ስናስበው በሱስ ምክንያት የብዙ ኢትዮጵያውያን ቤት ታምሷል፤ ብዙ ወጣቶች መስራትና መለወጥ አልቻሉም። ሀገራቸውን ማገዝ ባለባቸው ልክም ማገዝ ተስኗቸዋል። ራሳቸውን ቤተሰባቸውን እንዲሁም ሀገራቸውን መጥቀም በሚችሉበት እድሜ ላይ ቢሆኑም ለከፋ ችግር ተጋልጠው ቁጭ ብለዋል። ስለዚህም በልጄ ሀሳብና ፍላጎት በቤተሰቤ ተሞክሮ መነሻነት ሥራውን አሀዱ አልነው›› ይላሉ ስለ ማዕከሉ አመሰራረት ሲናገሩ።
“…ቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ለሰራኋቸው 35 ዓመታት አርአያ የምትሆን ነርስ በሚል ሆስፒታሉ አምስት ሺህ ብር እንዲሁም የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ስድስት ሺህ ብርና ሜዳሊያ በሽልማት አበርክተውልኝ ነበር። ይህ ለእኔ በተለይም ላሰብኩት ሥራ መነሻ የሚሆነኝ ብዙ ብር ነበር። ከዚያም ደግሞ አንዳንድ ሃሳቡን የወደዱት ቤተሰቦቼ የአቅማቸውን አገዙኝ። በዚህ ሁኔታ ሄድኩና አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታ አጠናቀቅሁ። ትልቅ ገንዘብ የሚፈልገውን የቤት ኪራይ ግን በቀላሉ የምሸፍነው አልሆነልኝም። በዚህም የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ በጣም መልካም ስለነበር ጉዳዩን ሳማክረው ችግሩን ተረድቶ አንቺ ልክ በጎ ሀሳብ ካሰበች እኛም አብረንሽ ልንሰራ ዝግጁ ነን አለኝ። ሌሎች ኃላፊዎችን አስተባብሮም ሆስፒታሉ አጋር ሊሆን ቃል ገባ። በዚህም እነሱ የቤት ኪራዩን እየከፈሉ ባለሙያና ምግብ እያቀረበልኝ እንድሰራው ሆንኩ›› ይላሉ የማዕከሉ ጉዞ በምን መልኩ እንደቀጠለ ሲያስረዱ።
ማዕከሉ ባዘጋጃቸው 12 አልጋዎች ላይ ከሱስ ለማገገም ጥረት የሚያደርጉ ወጣቶች አሉ። እነዚህ ወጣቶች ደግሞ ለሶስት ዓመታት ያህል በነጻ ሲገለገሉ ቢቆዩም ነገር ግን ጳውሎስ ሆስፒታል ይከፍል የነበረውን ቤት ኪራይ ሲያቋርጥ ሁሉም ነገር ተደራረበ። ደመወዝ፣ ውሃና መብራት እንኳን መክፈል ሲያቅት ከተገልጋዮቹ ጋር ወጪ መጋራት ወይንም ደግሞ የአገልግሎት ክፍያ በማለት አንድ ሰው በወር 6ሺህ 219 ብር እንዲከፈል ሆኗል የሚሉት ሲስተር ፤ ይህም ሆኖ ከ12ቱ አልጋ ሁለቱ ምንም ዓይነት ገቢም ሆነ ደጋፊ ለሌላቸው ወገኖች በነጻ አገልግሎት የሚሰጥበት መሆኑን ይናገራሉ። ጳውሎስ ሆስፒታል ግን እስከ አሁን ድረስ በሳምንት ሁለት ቀን ሀኪሞች፣ ሳይኮሎጂስቶች እየላከ የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገላቸው እንደሚገኝ አልሸሸጉም።
ትኩረት ለልጆች አስተዳደግ
ልጆችን ጥሩ ማብላት፣ ማጠጣት፣ ማዝናናት፣ ጥሩ ትምህርት ቤት ማስተማር መልካምና የሚበረታታ ወላጅም ለልጁ ሊያደርግ የሚገባው ነገር ነው። እኔም የሚመስለኝ ይኸው ነበር። ነገር ግን ልጅ ማሳደግ ይህ ብቻ አይደለም። እኔ ድሮ ስማር ትኩረት አለማግኘቴን ለማጥናት እንኳን የተመቻቸ ሁኔታ አለመኖሩን እያስታወስኩ ያንን ለመበቀል ነበር ልጄን ከፍዬ ሳስተምር የነበረው። ግን ያ ብቻ በቂ እንዳልሆነ አውቄያለሁ። ምክንያቱም ልጆች ከዚያም ያለፈ እንክብካቤን ይፈልጋሉ።
በሌላ በኩል ዛሬ ላይ ያሉ ልጆች እንክብካቤው ስለሚበዛባቸው ሁሉም ነገር በእጃቸው ስለሆነ ለአቻ ግፊትም ሆነ በራሳቸው ለሚያደርጉት ነገር ቅርብ ናቸው። ይህ ደግሞ ገና በዘጠኝና አስር ዓመታቸው ሱስ ውስጥ እንዲገቡ ያደርጋቸዋል። በመሆኑም እኛ ፍላጎታቸውን ማሟላት ብቻ ሳይሆን ባህሪያቸው ላይ መስራት አለብን ይላሉ። ለምሳሌ፡- ልጆች የመጀመሪያ ባህሪያቸውን የሚወስዱት ከየትም ሳይሆን ከቤተሰባቸው ነው። የሚቀጥለውን ከአካባቢያቸው ይማራሉ። በመሆኑም በተቻለ መጠን ሰዎች ልጆች ከወለዱ በኋላ ለልጆቻቸው ጊዜ መስጠት፤ ባልና ሚስት ራሳቸው የግላቸው ጊዜ ማዘጋጀት፤ በልጆች ዙሪያ ሁልጊዜ መነጋገር አለባቸው። ስልኩን፣ ኢንተርኔቱን ሰጥቶ ቁጭ ማለት ብቻ ሳይሆን ምን እያየ/ች ነው የሚለውን መከታተል ይኖርባቸዋልም ባይ ናቸው።
‹‹ የሚገርምሽ ነገር ሰሞኑን ወደኛ ተቋም የ15 ዓመት ልጅ መጥቶ ነበር፤ ይህ ልጅ ደግሞ ትምህርት ቤት ሲሄድ አረቄ፣ ጅን ምናምን በትንንሽ ብልቃጦች እያደረገ በቦርሳው ይዞ ነው። ይህንን እናቱ አታውቅም። ግን ደግሞ ከፍ ያለ የባህርይ ለውጥ ያመጣ ጀመር። ነገሩ ሲጣራ ችግሩ ሌላ ሆኖ ተገኘ። እናት ይህንን ስትሰማ ራሷን ልትስት ነበር። በመሆኑም ልጆቻችንን ልንፈትሻቸው፣ ልናዋራቸው ፣ ልንቀርባቸው ይገባል። ስለ ሕይወትም ግንዛቤ እንዲኖራቸው ማድረግ የእኛ ኃላፊነት ነው።›› ሲሉም ከሥራቸው አኳያ ያለውን ሁኔታ በማንሳት ይመክራሉ።
እኛ ሁሉንም ነገር አትንኩ ብቻ ነው የምንላቸው ነገር ግን ሁሉንም በግልጽ መንገር ያስፈልጋል፤ እንዲፈሩን ሳይሆን እንዲያከብሩን ማድረግ ግድ ነው። ሌላው ደግሞ ልጄን ከሁሉም ነገር አርቄ ይዤ ማንንም ሳላገናኝ አሳድጋለሁ ማለቱም ጥሩ አይደለም። አንድ ቀን ሲወጡ የሚያርፉት ያ የተከለከሉት ነገር ላይ ነው። ስለሆነም ልጆቻችንን ጠዋትና ማታ ነው ማግኘትና ነባራዊ ሁኔታዎችን ማስረዳት ያለብን። እኛ ልጆቻችን የምናገኛቸው ብዙ ጊዜያቸውን የሚያሳልፉት ከእድሜ እኩዮቻቸው ጋር ነው። ቤታቸው ውስጥ ያለ ችግርን እንኳን ቢኖር ለጓደኞቻቸው ነው የሚነግሩት ፤ በዚህ ጊዜ ጓደኞቻቸው የሚሏቸው ከጭንቀትሽ ለመውጣት ይህንን ኪኒን ዋጪ፤ ይህንን ጠጪ፤ እዚህ ቦታ ሂጂ ነው። ይህ ደግሞ ለልጆች ችግር ውስጥ መግባት ግንባር ቀደም ምክንያት ይሆናል። ስለዚህም ለልጆቻችን ጊዜና ፍቅርን መስጠት ከእኛ የሚጠበቅ ትንሹ ሀላፊነት ነውና ተጠያቂ እንዳንሆን በተቻለ መጠን ቤታችንን ሰላማዊ ማድረግ ይኖርብናል መልእክታቸው ነው።
መልዕክት
አሁን ላይ በሱስ ዙሪያ ተረዳድተን ሰርተን ለውጥ ካለመጣን በየቤቱ ለቅሶ ይሆናል። ሁሉም ያለቅሳል፤ በመሆኑም በተለይ ቤተሰብ የባህርይ ለውጥ እንዲያመጣ በእድሮች፣ በመስሪያ ቤቶች ላይ ሰፋ ያለ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት ያስፈልጋል። በእኛው ስህተት የተበላሹ ልጆቻችንን ከቤት አስወጥተን የጎዳና ተዳዳሪ የምናደርግ ብዙ ነን።
ሱስ ዛሬ ላይ ከቤተሰብ አልፎ እንደ ሀገር እየፈተነን ነው። ነገር ግን እኔ አንዳንድ መስሪያ ቤቶች እየሄድኩ እስቲ በዚህ ላይ እንስራ ይህንን አግዙን ብዬ በምጠይቅበት ጊዜ ‹‹ሀገራዊ ችግር ላይ ነን›› የሚል መልስ የሚሰጡ አሉ ፤ አዎ ሀገር ችግር ላይ ናት። ነገር ግን ትልቅ የሀገር ችግር የትውልዱ መጥፋት ነው። ይህ ትውልድ በዚህ ሁኔታ እያጣነው ከመጣን ማነው የሚተካው? የሚለውን ማሰብ ከምንም በላይ አስፈላጊ ነው። በመሆኑም እኔ በ60 ዓመቴ ይህችን ጠብታ እሰራለሁ። ሌላውም እንደዚሁ ቢተባበር ብንሰራ በጅምሩ ላይ ደግሞ መንግስት አይዟችሁ በርቱ ብሎ ደጀን ቢሆንልን ዘላቂ መፍትሔ እናመጣ ነበር።
እኛ የፈጀውን ጊዜ ፈጅተን ልጆቹን ከሱስ ካላቀቅን በኋላ የሚቀበላቸው፣ ስራ እንዲሰሩ የሚያግዛቸው ቢኖር ዳግም ወደሱስ ውስጥ እንዳይመለሱ እንደውም እነሱ ራሳቸው ሌሎችን እንዲያስተምሩ ይሆኑ ነበር። በመሆኑም ይህችን ጅማሮ ያየ መንግስት ማዕከሉ ተጠናክሮ የራሱን ስራ ፈጥሮ በራሱ ገቢ ተዳድሮ ለብዙዎች ለውጥ ምክንያት ይሆን ዘንድ ባለድርሻ አካላት ማየት ቢችሉ ሲሉ ሲስተር ጥሪያቸውን ያቀርባሉ።
እፀገነት አክሊሉ
አዲስ ዘመን ጥር 21 ቀን 2015 ዓ.ም