ስራ ያስከብራል ! ይህ የማይታበይ ሀቅ ነው፡፡ ሰዎች ደግሞ በተለይም ነገያቸውን ለማሳመር ዛሬ ላይ ተግተው መስራት አለባቸው፡፡ ብዙ ሰዎችም በዚህ መንገድ አልፈው ያሰቡበት ደርሰዋል፡፡ ከእነዚህ ሰዎች መካከል ደግሞ የዛሬው የህይወት ገጽታ አምዳችን እንግዳ አቶ በዳዳ ገመቹ አንዱ ናቸው፡፡
አቶ በዳዳ ወደዚህች ምድር ሲመጡ ጀምሮ ያን ያህል ኑሮ የተሳካላቸው በተመቻቸ ሁኔታ ተወልደው ያደጉ አይደሉም፡፡ ይልቁንም ብዙ ፈተና (አሜኬላ) ከበዛበት ህይወት ውስጥ ተፈጥረው ከእህት ከወንድሞቻቻው ጋር ገና በልጅነታቸው ነው የህይወትን አቀበት ይገፉት ዘንድ የተጋፈጡት፡፡
ይህንን ለመሰለው ተስፋ አስቆራጭ ችግር ግን እጅ ያልሰጡት አቶ በዳዳ ዝቅ ካለ ስራ ጀምረው ዛሬ ላይ ከአገር አልፈው በዓለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ የሆኑበትን ስራ በመስራት ላይ ይገኛሉ፡፡
አቶ በዳዳ ገመቹ ተወልደው ያደጉት አገራችንን በዓለም አደባባይ ከፍ አድርገው በሚያስጠሩልን አትሌቶቻችን የትውልድ ቀዬ አርሲ ክፍለ አገር በቆጂ ነው፡፡ እሳቸውን ጨምሮ ዘጠኝ ልጅ ባለበት ቤት ውስጥ የተወለዱት አቶ በዳዳ የመጀመሪያ ልጅ እንደመሆናቸው በትምህርትም በሌላውም በኩል ተሽሎ የመገኘት ትልቅ ሀላፊነት የተሸከሙም ነበሩ። የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን የጀመሩት እዛው በቆጂ ኮጂ ቁብሳ በሚባለው ትምህርት ቤት ነበር፡፡ ነገር ግን አቶ በዳዳ እንደሌሎቹ እኩዮቻቸው በተመቻቸ ሁኔታ የሚማሩበትን እድል ባለማግኘታቸው እስከ ስደስተኛ ክፍል ተምረው ማቋረጥ ግድ ሆነባቸው፡፡
“……..እንደነገርኩሽ እኔ የመጀመሪያ ልጅ ነኝ፤ ከኔ በታች ስምንት ልጆች አሉ ፤ ቤተሰቦቻችን ደግሞ ምንም ነገር የሌላቸው ድሆች ነበሩ ፤ በንጉሱ ጊዜ ጭሰኞች ስለነበሩም የሚታረስ መሬትም ሆነ የማረሻ በሬ አልነበረንም፤ ኑሯችንም አስከፊ ነበር፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ ደግሞ እናታቸን ይህንን ሁሉ ልጅ ያለአባት ነበር የምታሳድገው፡፡በጠቅላላው ኑሮ ለእኛ በጣም ከባድ ነበር” ይላሉ፡፡
ይህንን አስከፊ ችግር እያዩ ትምህርታቸውን መማር ያልሆነላቸው አቶ በዳዳ ለእናታቸው አጋዝ ለመሆን ለእህት ለወንድሞቻቸውም የታላቅነታቸውን ሚና ለመወጣት በማሰብ ትምህርታቸውን ከስድስተኛ ክፍል አቋርጠው ውትድርና መግባትን መረጡ፡፡ በወቅቱ ውትድርና መግባት ግዴታ ባይሆንም እሳቸው ግን ኑሮን ለማሸነፍ እናታቸውና ወንድሞቻቸው በችግር ከሚያጡ በማለት የመረጡት የስራ መስክ ነበር።
” …………በወቅቱ የእኔ አላማ የነበረው ወትድርና ገብቼ በማገኘው ደመወዝ እናቴና እህት ወንድሞቼን ማገዝ ነበር። የኑሮ አማራጬ ብዬም በፍቃደኝነት የገባሁት ለዚሁ ነው ” በማለት ውትድርና የገቡበትን ምክንያት ይናገራሉ።
አቶ በዳዳ ውትድርና ገብተው ምንም እንኳን ስልጠናው ከእሳቸው የልጅነት ጉልበት በላይ ቢሆንም አላማ አላቸውና ተቋቁመው በማለፍ ኋላም በተመደቡባቸው ቦታዎች ሁሉ ግዴታቸውን በሚገባ በመወጣት ለ16 ዓመት ያህል ማገልገላቸውን ይናገራሉ፡፡
አቶ በዳዳ ከባዱን የኑሮ ውጣውረድ በውትድርና ለማለፍ ትምህርታቸውን ቢያቋርጡም የመማር ፍላጎታቸው ግን ከውስጣቸው ተሟጦ የወጣ አልነበረም ፡፡ ከውትድርናው ጎን ለጎን ነገሌ ቦረና ሆነው የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን አጠናቀቁ ፡፡ ኋላም ወደ አዲስ አበባ የመምጣት እድልንም ሲያገኙ ደጃዝማች ገነሜ ትምህርት ቤት ገብተው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርትቸውን መከታተላቸውን ይናገራሉ፡፡
” …..ውትድርና ላይ ይከፈለኝ የነበረው ደመወዝ 60 ብር ነበር፤ ከዚህ ብር ላይ ደግሞ 20ዋን ለራሴ አስቀርና 40ውን ብር ለእናቴ እልክላታለሁ ፤ በዚህ ደግሞ እህት ወንድሞቼ ሳይራቡ ትምህርታቸውንም እንደእኔ ሳያቋርጡ ተምረው ዛሬ ላሉበት ደረጃ በቅተዋል፡፡በዚህም ትልቅ እርካታ ይሰማኛል” ብለዋል፡፡
በወቅቱ ምናልባት እኔ ወታደር ባልሆን ኖሮ እናቴንም በአጭሩ አጣት ነበር፤ እህት ወንድሞቼም አሁን ያሉበት ደረጃ ለመድረስ በጣም ይቸገሩ ነበር፤ የሚሉት አቶ በዳዳ ነገር ግን እሳቸው መስዋዕት ሆነው ለቤተሰባቸው እንደ ሻማ መቅለጣቸው ውጤቱን ሲያዩት በጣም እንደሚደሰቱበትም ያብራራሉ፡፡
አቶ በዳዳ የቤተሰባቸውን ጉሮሮ ለመድፈን ለእናታቸው ብሎም ለወንድም እህቶቻቸው ጋሻ ለመሆን በገቡበት ውትድርና ላይ ብዙ ዓመት አገልግለዋል፤ በዚህ የአገልግሎት ዘመናቸው ደግሞ በእግራቸው ላይ የመቁሰል አደጋ ደረሶባቸው ከውትድርናው አለም ተገለሉ፡፡
ከውትድርና ከወጡ በኋላ ለራሳቸውም ሆነ ለቤተሰቦቻቸው ሲሉ ሌሎች ስራዎች ላይ መሰማራት ነበረባቸው ፤ ከውትድርና ለወጣ ሰው ደግሞ ሊሆን አልያኝም ሊገኝ የሚችለው ስራ ጥበቃ ነበርና አቶ በዳዳ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የጥበቃ ስራ የሚሰሩበትን ቦታ ማፈላለግ ጀመሩ። ስራውን ማግኘታቸው አልቀረም አገኙ፡፡ ሀላፊነታቸውን በአግባቡ ሲወጡ የቆዩት አቶ በዳዳ በስራው ላይ ልምድ እያገኙ ሲሄዱ በዚሁ ሌላ መስሪያ ቤት መቀየርን ፈለጉ፡፡
አሁን ሁለተኛው መስሪያ ቤታቸው ላይ ደርሰዋል። መስሪያ ቤቱ ደግሞ የመኪና መለዋወጫ ስሙም ችርቻሮ ንግድ ኮርፖሬሽን ይባል ነበር፤ በእዛም ስራቸውን በታማኝነት ከመወጣታቸውም ባሻገር ተጨማሪ ገቢ ሊያስገኝላቸው የሚችል ስራን በግቢው ውስጥ መስራት ጀመሩ፡፡
“…….የሚገርምሽ በመንግስት ችርቻሮ ንግድ ኮርፖሬሽን ውስጥ ስሰራ ሁለት ሁለት መኪና የነበራቸው አለቆች ነበሩኝ፤ እኔ ደግሞ ከጥበቃ ስራዬ ጎን ለጎን የእነሱን መኪና ማጠብ ጀመርኩ ፤ አንዳንድ የሚፈልጉትንም ስራ ሲያዙኝ እሰራለሁ፤ ይህ አካሄዴ ደግሞ በቅጥር ከሚከፈለኝ 70 ብር ደመወዝ ሌላ በወር እስከ 450 ብር ድረስ እንደአገኝ እረዳኝ፤ ” በማለት ሁኔታውን ያስታውሳሉ፡፡
አቶ በዳዳ ህልማቸው ሰፊ ግባቸውም ሩቅ ነበርና የጥበቃ ስራውን እየሰሩ ብሎም የአለቆቻቸውን መኪኖች እያጠቡ ከሚያገኙት ገንዝብ ላይ ቤተሰባቸውን ማገዙ እንዳለ ሆኖ ተቀማጭም ያደርጉ ነበር፡፡ይህ ተቀማጭ ገንዘባቸው ደግሞ በተለይም ዛሬ ላይ ለስኬት ላበቃቸው የድለላ ስራ መነሻ ሆናቸው፡፡
“…….የመጣሁበት ቤተሰብ የእኔን እጅ የሚጠብቅ ነበር፤ እናም እኔ ገንዘብ አገኘሁ ልብላ ልጠጣ ልዝናና የሚል አምሮቱ እንኳን ቢኖረኝም እነሱን የመርዳት ሃሳቡ ግን ከልጅነቴ ጀምሮ አብሮኝ የኖረ በመሆኑ ገንዘብን ማጥፋት አልችልም ነበር፡፡ 450 ብር እንኳን ከደመወዝ ውጪ ሳገኝ ግማሹን ለእናቴ እልክ ነበርⵆ በነገራችን ላይ እኔ ከልጅነቴ ጀምሮ ህይወቴን ሙሉ በስራ ስላሳለፍኩ አሁንም ድረስ መዝናናት የሚመስለኝ ስራ መስራት ነው፡፡ በመሆኑም መዝናናትን የምገልጸው በመጠጣት አልያም ሆቴል በመሄድ ሳይሆን በስራ እርካታን በማግኘት ሰዎችን በማስደሰት የእጅን የድካምን ዋጋ በማግኘት ነው ” ይላሉ፡፡
“…….ስራ ለእኔ ትልቁ እርካታዬ ነው የሚሉት አቶ በዳዳ ድሮም ሆነ አሁን መሸታ ቤት ሄዶ መጨፈር አልያም ከጓደኛ ጋር ተሰብስቦ በመንጫጫት ሌላም ሌላም እያደረጉ ደስታን ማግኘት ይቻላል ብዬ አላስብም፡፡ ዛሬም ለእኔ ከቀኑ 11 ሰዓት ሰዓት እላፊዬ ነው፡፡ 11 ከ 30 ሲሆን ቤቴ ነኝ። መዝናኛዬ ልጆቼ ቤተሰቦቼ ናቸው፡፡ ይህ ባህሪዬ ደግሞ ከእኔ ጋር አድጓል፡፡መዝናናት ለእኔ በስራዬ እርካታን ማግኘት ነው”፡፡
አቶ በዳዳ ጥበቃ ሰርተው መኪና አጥበው ገንዘብ ቢያጠራቅሙም ነገ ላይ የተሻለ ነገርን ለማግኘት ለራሳቸውም ሆነ ለቤተሰባቸው የተሻለ ኑሮን ለመስጠት ምን ብሰራ ያዋጣኛል የሚለውን ሳያስቡት ውለው አድረው አያቅውቁም፡፡ይህንን ሀሳባቸውንም ለተለያዩ ሰዎች ያማክሩ ነበር፤ ሁሉም የየራሳቸውን ይሻላል የሚሉትን ቢነግሯቸውም ደላልነት ግን ገንዘብ የሚያስገኝ ስራ መሆኑን የነገራቸውን ተቀበሉ። ግን ደግሞ እንዴት ብዬ ነው ደላላ የምሆነው ሲሉ ማሰባቸው አልቀረም ፡፡ ወደ ስራው ከመግባታቸው በፊትም ያጠራቀሟትን ሶስት ሺ ብር በማውጣት አንድ ዶክተር በሙያው ላይ የሚሰጠውን ስልጠና ወሰዱ፡፡ ስልጠና ዛሬ ላይ ለደረሱበት ውጤት እንዳበቃቸውም ይናገራሉ፡፡
“…….ከስልጠናው ሶስት ነገሮችን ተምሬያለሁ፤ አንደኛው ለራስህ ታማኝ ሁን የሚባል ሲሆን ምናልበት እንዴት ሰው ለራሱ ታማኝ አይሆንም ሊባል ይችላል ፤ ነገር ግን ለራስህ ታማኝ ሁን ማለት እሰራዋለሁ ብሎ ለታቀደው እቅድ እና ለተገባው ቃል ታማኝ መሆን ማለት ነው። ይህንን ማድረግ ካልተቻለ እንግዲህ ለራስ ታማኝ አልሆንም ይመጣል ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ለስራ ታማኝ መሆን ነው፤ ይህም ማለት ስራን እውነት የሆነውን ነገር ብቻ በመናገርና በማድረግ መግለጽ ማለት ነው፡፡ በነገራችን ላይ ዛሬ ላይ የምናየው የድለላ ስራ ውሸትና ማጭበርበር የበዛበት ነው፡፡ ነገር ግን ድለላ እውነትን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ ሶስተኛው ለደንበኞች ታማኝ መሆን ነው፤ ለደንበኛ ታማኝ መሆን ሲባል ደግሞ አንዱና ዋናው ሚስጥራቸውን መጠበቅ፣ የሚፈልጉትን ነገር እንጂ እኛ የፈለግነውን ነገር አለማቅረብ ፣የሚሉት በስልጠናው ያገኘሁት ስንቅ ነው ” ይላሉ።
አቶ በዳዳ ስራቸውን “ሀ ” ብለው የጀመሩት አራት ኪሎ ቱሪስት ሆቴል አካባቢ ነበር፤ በቦታው ላይ በርካታ መሰል የድለላ ስራዎችን የሚሰሩ ሰዎች የነበሩ ሲሆን እሳቸውም እነሱ የሚሰሩትን እያዩ እዛው እየዋሉ ግን ደግሞ የወሰዱትን ስልጠና በማያፋልስ መልኩ ስራቸውን ሲያከናውኑ ቆዩ፡፡
“……ቱሪስት ሆቴል አካባቢ ስራዬን ጀመርኩ ፤አንድ ቀን በአጋጣሚ አንድ ሰው ቤት መሸጥ እንደሚፈልግን ገዢ እንዳገናኘው ነገረኝ፡፡ በነገረኝም እለት ቤት የሚገዛ ሰው መጣ፤ የሁለቱንም ሀሳብ ስሰማው የሚስማማ ነው ፤ቤቱ ለፈላጊው ትክክልኛ ሆነ፡፡ ይህ አጋጣሚ ብዙ ጊዜ የሚገኝ ባይሆንም እኔ ቀናኝና ቤቱን በ5 መቶ ሺ ብር አገበያየሁ። እኔም ከሁለቱም ሰዎች ሁለት በመቶ ታስቦልኝ 60 ሺ ብር ክፍያን አገኘሁ፡፡ ቀን ይህንን አገኝቼ ማታ ወደጥበቃ ስራዬ ነበር የሄድኩት ፤ ከዛ በኋላ በሀቅኝነት ከተሰራ ድለላ ጥሩ ስራ መሆኑ ገባኝ ” በማለት ስለመጀመሪያ የድለላ ስራ አጋጣሚያቸው ይናገራሉ፡፡
በዛች እለት ብቻ እንኳን ይህንን ገንዝብ ካገኘህማ የጥበቃ ስራህን ተው ያለኝ ብዙ ነበር ፤ነገር ግን እኔ ስራዬን ሳልተውም ሁለቱንም ጎን ለጎን እየሰራሁ አምስት አመት ቆየሁ በማለት ይናገራሉ፡፡
“…….በ27 ዓመት የድለላ ስራ ቆይታዬ አንድም ቀን ፍርድ ቤት ቀርቤ በፍትሃብሔርም ሆነ በወንጀል ተከስሼ አላውቅም ፡፡ ይህ የሆነው ደግሞ ጥፋት ሊያሰሩ የሚችሉ ነገሮችን ስለምሸሽና ህግና ደንብን ጠብቄ ስለምሰራ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ እንደውም አሰርቶ ገንዘብ ለመክፈል በጣም የሚሳሳ ሰው ሲገጥመኝ ገንዘቡን እተውለታለሁ፡፡ ምክንያቱም ስራ እንጂ ነገር ስለማልፈልግ ” ይላሉ፡፡
በአንድ ወቅት ግን ለአውቶቡስ የሚሆን አምስት ሳንቲም ጎድሏቸው በእግራቸው የሄዱትን ኋላም የገጠማቸውን መቼም እንደማይረሱት ይናገራሉ”……የጥበቃ ስራውን ከድለላ ስራዬ ጋር አጣጥሜ በምሰራበት ወቅት አንድ ቤት ለማየት ኮተቤ አካባቢ ሄድኩኝ ፡፡ ይዘውኝ የሄዱት ሰዎች ደግሞ ጉዳያቸውን ከጨረሱ በኋላ ሰንዳፋ አካባቢ ደርሰን እንምጣ ብለው ትተውኝ ሄዱ፡፡ እኔ ደግሞ ማታ የጥበቃ ስራዬ ላይ መገኘት አለብኝ ፡፡ በወቅቱ 33 ቁጥር አንበሳ የከተማ አውቶቡስ ከኮተቤ ተነስታ አራት ኪሎ በ15 ሳንቲም ታመጣ ነበር፤ እኔ ግን
ኪሴ የነበረኝ አስር ሳንቲም ብቻ ነው፡፡ በህይወቴ ደግሞ ሌብነትና ልመናን በጣም እፈራለሁ፤ ስለዚህ አምስት ሳንቲም ሙሉልኝ ማለት አልቻልኩም። በመሆኑም በጦር ሜዳ በደረሰብኝ ጉዳት አንድ እግሬ ያነክሳል፤ ከዘራም እይዛለሁ፤ ግን ምንም አማራጭ ስላልነበረኝ ጉዞዬን በእግሬ እያነከስኩ ጀመርኩ፡፡ መካከል ላይ እግሬም በጣም ስላመመኝ ቁጭ አልኩ፤ እዛው ቁጭ ብዬ ሳላስበው አለቀስኩ ፤ ሰዎች በሁኔታዬ ተደናግጠው እናግዝህ ቢሉኝም አይ ብዬ ከተቀመጥኩበት ተነስቼ መንገዴን ጀመርኩ፤ አራት ኪሎ መስሪያ ቤቴ በር ላይ ስደርስ ወደቅኩ፡፡ ››ዛሬ ይህ ሁሉ አልፎ ሳየው ከታገሱ የማያልፍ ነገር እንደሌለ እንድረዳ አድርጎኛል፡፡
ደላላ ለመሆን ጥሩ ተናጋሪ መሆን ያስፈልጋል የሚባለው ውሸት ነው። በነገራችን ላይ በእኛ አገር ደላሎች ካላቸው የስነ ምግባር ደረጃ አንጻር በጣም ተናጋሪና ውሸታም መሆን የግድ እንደሆነ የሚያስቡ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡ ይህ ፍጹም ሀሰት ነው፡፡ ድለላ ለእኔ ግን እውነት መናገር ነው፡፡ ምክንያቱም አንድ ሰው ሁለት ክፍል ቤት ሊከራይ መጥቶ ደላላው 12 ክፍል ያለውን ቤት ቢያሳይ በራሱ እየቀለደ ነው፡፡ በመሆኑም ለድለላ ስራ ቁልፍ መንገዱ የሚሰራውን ስራ ማወቅና ማክበር ብቻ ነው፡፡ በሌላ በኩል ሰዎች ወደ ደላሎች ሲመጡ ፍላጎታቸውን በውል መረዳት በፍላጎታቸው መሰረት ለማስተናገድ እኔ ጋር ምን አለ ምን ልሰጠው ነው የምችለው የሚለውን ማጤን ይገባል ይላሉ፡፡
ጎዞ አሜሪካን አገር
አቶ በዳዳ ባለፉት 27 ዓመት በላይ የሰሩት የድለላ ስራ ገንዘብና እውቅና ብቻ ሳይሆን ያስገኘላቸው በርከታ እንደቤተሰብ የሚተያዩቸው ደንበኞችም እንዲያፈሩ አድርግቸዋል፡፡ በታማኝነታቸው በስራ ወዳድነታቸው ቃላቸውን የሚያከብሩ የሚችሉትን ብቻ የሚሰሩ የሰው ሃቅ የማይፈልጉ መሆናቸው ወዳጆቻቸው ምን እናድርግላቸው ብለው እንዲጨነቁም አድጓቸዋል፡፡
እነዚህ ወዳጆቻቸው ደግሞ ምን እናድርግላቸው ብለው አልቆሙም ይልቁንም ወደ አሜሪካን አገር ጠርተዋቸው ከ 38 ዓመት በላይ ሲያስነክሳቸው የነበረውን የጦር ጉዳተኛ እግራቸውን በማሳከም አቶ በዳዳ ከከዘራ ውጪ እንዲንቀሳቀሱ አስቻሏቸው፡፡ ይህንን ላደረጉላቸው ወዳጆቻቸውና ደንበኞቻቸውም ላቅ ያለ ምስጋናን ያቀርባሉ፡፡
አቶ በዳዳ አሜሪካን አገር ለህክምና ይሄዱ እንጂ ወደ አገራቸው ይዘውት የሚመጡት ነገር አላጡም። አቶ በዳዳ ከአሜሪካን አገር የሚሸጥ የሚለወጥ አልያም የሚበላ የሚጠጣ የሚለበስ ነገርን ይዘው አይደለም ወደ አገራቸው የተመለሱት ይልቁንም ለአገራችን የድለላ ስራ ፈር ቀዳጅ የሆነና ሙያውንም ከፍ ወዳለ መንገድ የሚያደርስ ቴክኖሎጂ ወይም እውቀትን እንጂ፡፡
“……..አሜሪካን አገር ሁሉም ነገር በህግና በደንብ የሚመራ ነው፤ ሰዎች መኪና ሲያቆሙ በስርዓት ነው ፤ጎዳናዎችን ንጹህ አድርገው ነው የሚጠቀሙት ፤የባንክ ስራቸው የተቀናጀና በተቻለ መጠን ከወንጀል ተግባር የተጠበቀ ነው፤ በሌላ በኩል ደግሞ አሰራሩ ግልጽ በመሆኑ ሁሉም ሰው መመልከት ይችላል፤ ተደብቆ የሚሰራ ስራ የለም፤ ይህን ወደ አገሬ ማምጣት ብመኝም እንዲህ በቀላሉ የሚሆን ግን አይደለም። ነገር ግን ከዛ ወዲህ በተለይም አገራቸው ላይ ንብረትን ማፍራት የሚፈልጉ ኢትዮጵያውያንን ማገዝ የሚያስችል ስራ ግን መስራት እንዳለብኝ አመንኩ “ይላሉ፡፡
አሜሪካን ያሉ ብዙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን አገራቸው ገብተው ንብረት ሲያፈሩ በቤተሰቦቻቸው ጭምር ይዘረፋሉ ፤ እህቴ እናቴ አባቴ ቤት ይኑረኝ ግዙልኝ ሲሉ ገንዘባቸው ይዘረፋል፤ ተገዝቷል ብለው ሲመጡም ሌላ ነገር ነው የሚጠብቃቸው፡፡
አቶ በዳዳ የእኔ ህልም ይላሉ ” ከኢትዮጵያ ውጪ ሆነው ኢትዮጵያ ውስጥ ቤት ለመግዛት የሚፈልጉ ደንበኞች ስለቤቶቹ ሙሉ መረጃ ማለትም የቤቶቹን ስፋትና የተሰሩበትን ማቴሪያል፤ አድራሻቸውንም ጭምር በኢንተርኔት በማየትና በኢንተርኔት የክፍያ ስርዓት በመፈጸም ቤት ገዝተው፣ የቤት ባለቤት የሚሆኑበትን አመቺ አሰራር ይዞ መምጣት ነው፤ “ኢትዮ ሌግዠሪ ሆምስ” በአሜሪካ አሌክሳንድሪያ ከተማ ሥራ የጀመረ ሲሆን በዚህ አገልግሎቱ ኑሯቸውን ባህርማዶ ያደረጉ ወገኖች በሀገራቸው የመኖሪያ ቤት እንዲኖራቸው እድልና አጋጣሚ ፈጥሮላቸዋል፡፡ድርጅቱ ከቤት ግብይቱ በተጨማሪ ዳያስፖራው ማህበረሰብ ከአገር ውስጥ ባንኮች ጋር መስራት የሚችልባቸውን ሁኔታዎች ያመቻቻል፡፡ ገዢዎች ከባንኮች ጋር መስራት ስለሚችሉባቸው ሁኔታዎችም ያማክራል። ከዚህ በተጨማሪም ቤቶች ግንባታቸው ሳይጠናቀቅ የግብይት ስርዓት እንዲኖራቸው ማድረግ፤ የቤት ዋጋዎችን ግልጽ የሚያደርግ ቴክኖሎጂ ማዋቀር፤ ድርጅቱ ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል ይጠቀሳሉ” በማለት ህልማቸውን ይናገራሉ።
በተቃራኒው ደግሞ አገራችን ላይ ብዙ የቤት አልሚ ባለሃብቶች አሉ፤ እነዚህ በተለይም በጥሩ ስነ ምግባር የሚሰሩትን በሰው አገር የሚለፉ ወገኖቻችን አገራቸው ውስጥ ያለምንም ውጣ ውረድ ራሳቸው እየተቆጣጠሩ አሰርተው የቤት ባለቤት የሚያደርግ መላ ማዘጋጀት አለብኝ ብዬ ነው የመጣሁት ይላሉ፡፡
“………ወገኖቼን በምችለው አቅም ለማገዝ ከልቤ ተነሳሳሁ ፤ ይህንን ሁኔታ የሰሙ ዳያስፖራ ወገኖቻችን በስራው ተደስተው ወዲያውኑ ነው መመዝገብ የጀመሩት ፤ ከዚህ በኋላ በዘመድ አዝማድ የሚበዘበዝ ለችግር የሚጋለጥ ኢትዮጵያዊ አይኖርም፡፡ ” በማለት ሁኔታውን ይናገራሉ፡፡
ይህ ስራ ኢትዮጵያውያኑን ከስጋት ነጻ ከማድረግ ልፋታቸው ሜዳ እንዳይወድቅ ከማስቻል ባሻገር ሁሉም ስራና ግንኙነት በባንክ በኩል ስለሚሆን ለመንግስትም የሚያስገኘው የውጭ ምንዛሪ በረከት ቀላል የሚባል አይደለም በማለት ጥቅሙ ዘርፈ ብዙ መሆኑን ይናገራሉ፡፡
የድለላ ስር ድሮና ዘንድሮ
እኔ ደላልነትን ስጀምርበት ከነበረው ጊዜ ዛሬን ለማነጻጸር በጣም ከባድ ነው ፤ዛሬ ላይ የሰዎች ስነ ምግብር እጅግ ተበላሽቷል፡፡ሰዎች አምላክንም ህግንም አይፈሩም ፡፡ በአንድ ጀምበር በብዙ ቢሊየን የሚቆጠር ገንዘብን አግኝተው ማደር ይፈልጋሉ፤ አሁን አሁን የምሰማቸው ነገሮች በራሱ ይቀፉኛል፡፡
ሰው ህግን የማይጥሰው መታሰርን ፈርቶ ብቻ መሆን የለበትም፤ ከዛ ይልቅ በአንድ ሰው ስህተት ወይም ውሸት በሌላው ላይ ሊደርስ የሚችለውን ጉዳት ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም ሰዎች ፈጣሪያቸውን ቢፈሩ ፡፡ህግ ደርሶባቸው ባይታሰሩ እንኳን ህሊና ቢኖራቸው ሌላውን ሰው ጎድተው ለመኖር ባይመርጡ የሚሉት አቶ በዳዳ አንድ ሰው ምንም ያህል ሃብታም ቢሆን እንጀራን በወጥ እንጂ በወርቅ አይበላም፤ ምንም ያህል ቢሊየነር ቢሆንም በጨርቅ እንጂ በወርቅ ተጠቅልሎ አይቀበርም ይባላል ፤ በመሆኑም ወደምድር ይዘነው የመጣነው አንዳችም ነገር የለም ከዛ ይልቅ ሰዎችን ያልበደለ ንጹህ ህሊና ካለን እኛ ከማንም በላይ ሃብታም ነን ይላሉ፡፡
“……ሀብት ለእኔ ንጹህ ህሊና ነው ፤ አሁን እንደ አገር የደላልነት ሙያ መስመሩን ስቷል፤ በመሆኑም እንደ እኔ መጀመሪያ የአመከለካከት ለውጥ ላይ መስራት ይገባል፡፡ሌላው ደግሞ ጠበቅ ያለ ህግ አስፈላጊ ነው፡፡በመሆኑም ህጉ መላላት የለበትም፤ አንድ ሰው ለሰራው ጥፋት ተመጣጣኝና አስተማሪ ቅጣት ሊጣልበት ይገባል፡፡ ምክንያቱም ህሊናውን የማይፈራ ከሆነ የግድ ህግን ማክበር ስላለበት፤ “ይላሉ፡፡
አሁን ላይ ሰዎች ሌብነት ማጭበርበር የራስ ያልሆነን ንብረት የራስ አስመስሎ መጠቀምን እንደ ዘመናዊነት እያዩት ነው፡፡ ይህ ግን ዘመናዊነት ሳይሆን ዝቅጠት ነው፡፡ ሰው የማይበላውን ሳይሆን የሚላውን እንጀራ ነው መጋገር ያለበት፡፡ በመሆኑም ሰዎች በስነ ምግባር ደረጃ የማነጹ ስራ መሰራት አለበት፡፡ በነገራችን ላይ ሁሉም ደላሎች ሌባ ናቸው ማለት ይከብዳል፤ ነገር ግን ሁሉም ደላላ ደግሞ ጤናማ ስላልሆነ እንደየስራው ተጠያቂነት ሊኖር ይገባል በማለት ይናገራሉ፡፡
የቤተሰብ ህይወት
አቶ በዳዳ ትላንት ለቤተሰባቸው ትልቅ ዋጋ ከፍለዋል ፤ ዛሬ ላይ ወንድም እህቶቻቸው ክፉውን ጊዜ በሳቸው ተሻግረው ሰርተው ራሳቸውን የሚያስተዳድሩበት ቁመና ላይ ደርሰዋል። እናታቸውም በህይወት ስላሉ እስከ አሁን ያግዟቸዋል፡፡
‹‹እኔ ወታደር ሆኜ እግሬን አጥቼ እነሱን አሻግሬ እዚህ በማድረሴ ትልቅ ደስታ ይሰማኛል።በኩሌም ትዳር መስርቼ አራት ልጆች ወልጄ አምስት የልጅ ልጆችን አይቻለሁ፡፡ ልጆቼ የእኔን ሙያ አልያዙም በየራሳቸው በስሜትና ፍላጎታቸው ይሰራሉ፡፡ ነገር ግን አንዷ ልጄ አሜሪካን አገር ያለውን ቢሮ ትቆጣጠራለች›› በማለት ሃሳባቸውን ቋጭተዋል፡፡
እፀገነት አክሊሉ
አዲስ ዘመን ጥር 14 ቀን 2015 ዓ.ም