አያሌው አስፋው ይባላሉ:: ትውልዳቸው ወሎ ክፍለአገር ዶቢ በሚባል አካባቢ በወራኢሉና በቦረናሳይንት አውራጃ መካከል ነው:: ሁሉንም በእኩል ደረጃ ማስተዳደር ከተቻለ በሙስሊሙ እምነት ዘንድ ከአንድ በላይ ሚስት ማግባት ይፈቀዳልና እርሳቸው በብዙ እናቶች መሀል ሆነው አድገዋል:: አምስት የሚሆኑ እንጀራ እናቶችን ባህሪም ለምደው ዓመታትን አስቆጥረዋል:: ምክንያቱም እናትና አባታቸው ተለያይተው ስለነበር አባታቸውን በመምረጣቸው ይህ ሆኖባቸዋል:: በእርግጥ በአንድ በኩልም እድለኛ ነበሩ:: ምክንያቱም የአያት ልጅ ቅምጥል እንዲሉት አይነት የመሆን አጋጣሚንም አግኝተዋል::
እርሳቸው እድለኛ ሆነው ከእናታቸው ጋር አለማደጋቸው የእንጀራ እናት ባህሪን ቢያሳያቸውም የተጎዱበት እንደነበር አይሰማቸውም:: ምክንያቱም ከሰው ጋር መኖር እንዴት እንደሚቻል አለማምዷቸዋል:: ረጅሙን የልጅነት ጊዜና የወጣትነት እድሜያቸውን ሲያሳልፉ መሰረት የሆናቸው እርሱ ስለነበር:: በዚያ ላይ ብቻቸውን ራሳቸውን ለማገዝ በሚያደርጉት ጥረት ውስጥ መግባባት ቀላል ነገር እንዲሆንላቸው ያደረገው በዚያ በተለያየ ቤተሰብ ውስጥ ማደጋቸው ነው:: በእርግጥ አንዳንዴ ይከፋቸዋል:: ምክንያቱም እንደሌሎች ሕጻናት ሲከፋቸው እናታቸው ጋር መሄድ አይችሉም:: እርሷን ያጧት ገና ትንሽ ሳሉ በደንብ ሳይጠግቧት ነው::
የአምስት እንጀራ እናት ባህሪ ጠንካራ ያደረጋቸው ባለታሪካችን፤ በብዙ ፈተና ውስጥ ቢያልፉም በቀላሉ አይወድቁም:: ይበልጡንም ጉልበታም ሆነው ይወጣሉ እንጂ:: ከሊስትሮነት እስከ software engineernet (ዳታ ዴቨሎፕ አድራጊነት) የደረሱትም በዚህ ብርታታቸውና ታታሪነታቸው እንደሆነ በሚገባ ያውቃሉ::
ሊስተሮው ተማሪ
የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን የተከታተሉት በአቅራቢያቸው ባለ ቦረና ሳይት አውራጃ መካነሰላም ላግሜራ ትምህርት ቤት ሲሆን፤ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ክፍል ተከታትለውበታል:: ከዚያ ወደ ሆጤ በር ትምህርት ቤት አመሩ:: ከአራተኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል ትምህርታቸውን መከታተል ቻሉ:: በዚህ ትምህርት ቤት በጣም ጎበዝ ተማሪ በመሆናቸው ሦስቱንም ክፍል በአንድ ዓመት ውስጥ አጠናቀውታል::
ከስድስተኛ ክፍል በኋላ ግን ግድ ወደሌላ አካባቢ መሄድና መማር ነበረባቸው :: ምክንያቱም በዚያ ሰባተኛ እና ስምንተኛ ክፍልን የሚማሩበት ትምህርት ቤት የለም:: ስለዚህም ቀን ሙሉ በእግራቸው እየተጓዙ ወደ ሚማሩበት አቃስታ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አቀኑ:: ይህንን ቦታ ቀደም ሲል በአንድ አጋጣሚ ያውቁት ነበር:: የስድስተኛ ክፍል ፈተና ለመውሰድ ፎቶግራፍ መነሳት ግድ ነውና በአቃስታ አቋርጠው ደሴ ድረስ አራት ቀን ሙሉ ከአባታቸው ጋር በመሆን ተጉዘ ፎቶግራፉን ተነስተው ትምህርታቸውን ተመዝግበው ከዛም ከሆጤ በር እስከ አቃስታ ድርስ በአንድ ቀን ተጉዘው ሰባተኛና ስምንተኛ ክፍልን ተምረዋል::
እንግዳችን የወሎ ድርቅ ሲመጣ በሁሉም አካባቢ ላይ ችግር ነበርና ትምህርታቸውን ለመቀጠል አልቻሉም:: አቃስታ ከተማ ላይ የእርዳታ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ተቋቁሞ ነበርና ከኮሚሽኑ ኃላፊ ጋር በመግባባታቸው ለእርዳታው የሚመጡ እቃዎችን የመመዝገብ ስራ አገኙ:: ስራውንም እየሰሩ ሰኔ ወር ላይ ትምህርት ስለማይገባ ወደቤታቸው ሊሄዱ ተሰናዱ:: ሆኖም ተማሪዎች ወደ ማሰልጠኛ ይግቡ የሚል ትዕዛዝ ስለመጣ እርሳቸውን ጨምሮ በአቃስታ የሚማሩ ተማሪዎች በኮምቦልቻ እርሻ ማሰልጠኛ ውስጥ ገቡ:: የሦስት ወር ስልጠናም ወሰዱ::
ከስልጠናው በኋላም ቢሆን ወደቤታቸው አልተመለሱም:: ዳግመኛ ለሌላ ስልጠና ወደ ታጠቅ ተላኩ:: እዚህም የሦስት ወር ስልጠና ወሰዱ:: ስልጠናው በአብዛኛው ውትድርናን መሰረት ያደረገ ነበርና ከዝንባቤ ነጻ አውጪ አባላት ጋር በመሆን ሰለጠኑ:: ስልጠናው ሲጠናቀቅ ሦስት ምርጫዎች ተቀመጡላቸው:: የመጀመሪያው ወደ ሰሜን ከዘመተው ጦር ጋር ተቀላቀሎ መሄድ ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ ወደ ሰፈራ መሄድ ነበር :: ሁለቱንም አልፈልግም ያለ ደግሞ ወደ መጣበት አካባቢው ይመለስ የሚሉ አማራጮች ተቀምጠው ነበር ::
እንግዳችን ትምህርቴን ብቀጥል ይሻለኛል ብለው ሦስተኛውን ምርጫ መርጠው ወደ ወሎ ተመለሱ:: ነገር ግን ያሰቡት አልሆነም:: ስለዚህም ትምህርት የሚማሩበትን መንገድ ለማግኘት የተለያዩ አማራጮችን ሞከሩ:: በስተመጨረሻ ወደ አዲስ አበባ ሄደው በቤት ሰራተኝነት ተቀጥረው ሲሰሩ ትምህርት የመማር እድሉን አገኙ:: ቀን የቤት ሰራተኛ ናቸው በማታው ክፍለጊዜ ደግሞ በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት የዘጠነኛ ክፍል ትምህርታቸውን ይከታተላሉ ::
አስረኛ ክፍል ሲደርሱ ደግሞ ሁኔረታዎች ተቀያየሩና አቶ እያሱ የሚባሉ ጓደኛቸው ጋር በመሆን ቀን ቀን ሊስትሮና ጋዜጣ መሸጥን የመሳሰሉ ስራዎችን እያከናወኑ በማታው ክፍለ ጊዜ ደግሞ ትምህርታቸውን ቀጠሉ:: 12ኛ ክፍልም እስኪደርሱ የማንንም እገዛ አልጠየቁም:: በራሳቸው ሁሉንም ነገር ማከናወንም አልተሳናቸውም :: ይሁንና ዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት ግን ማምጣት አልቻሉም:: ስለዚህም ውጤታቸው የሚያስገባቸው ኮሌጅ ነበርና ኮተቤ መምህራን ማሰልጠኛን ተቀላቀሉ:: በኮሌጁም በውጪ ቋንቋና ስነጽሁፍ ትምህርት መስክ በዲፕሎማ ተመረቁ ::
በነገሮች ተስፋ ቆርጠው የማያውቁት አቶ አያሌው፤ምንም እንኳን ድግሪያቸውን የመማር ከፍ ያለ ፍላጎት ቢኖራቸውም በተመረቁበት ዘርፍ ለሁለት ዓመት ማገልገል ነበረባቸውና ‹‹ልቤ ፋና አንደኛና መለስተኛ ትምህርት ቤት›› የመምህርነት ስራቸው ጀመሩ ፤ ቀን እየሰሩ ማታ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የዲግሪ ትምህርታቸውን ጀመሩ :: በግብርና ሚኒስቴር ከዚያም የውጪ ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር ውስጥ በመዘዋወር ሰርተዋል:: እናም ይህ ሥራቸው የፈለጉትን ማድረግ አላስቻላቸውም:: ስለዚህም የአዲስ አበባውን ዩኒቨርሲቲ ትምህርት ትተው ሌሎች አማራጮችን መፈለግ እንዳለባቸው ወሰኑ:: ይህ ውሳኔ ደግሞ የውጪ የትምህርት እድሎችን መሞከር ነበርና ፤ ተሳካላቸውⵆ
አውስትራልያ የሚገኝና ወሎን ጎንግ ‹‹Wollongong University›› የሚባል ዩኒቨርሲቲ ምላሽ ሰጣቸውና ለመማር ወደ ስፍራው ተጓዙ:: በዩኒቨርሲቲውም የኮምፒውተር ሳይንስ ትምህርት አጠኑ:: አሁን ደግሞ ሁለተኛ ድግሪያቸውን በሳይቨር ኢንቨስቲጌሽን ኤንድ ፎረንሲክ እንዲሁም Information and Communications Technology የትምህርት መስክ ሙሉ ወጪያቸው በአውስትራልያ መንግስት ተሸፍኖላቸው እየተማሩ ይገኛሉ:: ነገር ግን ትምህርቱ በፈተና የታጠረ እንደነበር ያወሳሉ::
የመጀመሪያው ሳይቨር ኢንቨስቲጌሽን ኤንድ ፎረንሲክ የሚል ጨምረው እየተማሩ ሳለ አንድ ዓመት ተኩል እንደተማሩ ከመምህራቸው ጋር ተጋጩ:: ምክንያቱ ደግሞ ፕላጃሪዝም አድርገሃል የሚል ነበር:: ትምህርቱ የሚሰጥበት ስርዓት ፊት ለፊት ሳይሆን በበይነ መረብ በመታገዝ (በዙም) ነው:: እናም አንድ ጉዳይ ይመረጥና ጥያቄ ተሰጥቶ በቤት ውስጥ ፈተና (አሳይመንት) መልኩ ለአሰልጣኙ በጽሁፍ ይቀርባል። በሰለጠኑት መሰረትም መስራትና የተሸለ ሀሳብ ማቅረብ ደግሞ የግድ ነው:: ስለዚህም እርሳቸው ይህንን አድርገው ቢሰሩም በተደጋጋሚ ከሰሳቸው:: ስለዚህም አስተማሪውን እውቀት አለው እንጂ ማስተማር አይችልም ብለው ከጓደኞቻቸው ጋር በመሆን ከእርሱ ክፍል ራሳቸውን ለማግለል ወሰኑ። ዩኒቨርሲቲው ሁኔታውን ተረዳላቸውና ወደሌላ የትምህርት መስክ እንዲቀይሩ አገዛቸው:: በዚህም ከአንድ ዓመት ትምህርት በኋላ ቀይረው የኢንፎርሜሽን ኮሚኒኬሽን ቴክኖሎጂን መማር ጀመሩ:: አሁን ትምህርቱን ለማጠናቀቅ የስድስት ወር ጊዜ ብቻ ነው የቀራቸው::
ችግር የፈጠረው ጥንካሬ አቶ አያሌው ገና ከቤተሰብ ጋር እያሉ ነው የራሳቸው ጌታ መሆን እንዳለባቸው የተረዱት:: በዚህም በርካታ ችግሮችን ማለፍ እንዲችሉ ሆነዋል:: የመጀመሪያው የወሎ ድርቅ ሲሆን፤ ሌላው ደግሞ መሬት ላራሹ ተብሎ እንደልባቸው መንቀሳቀስ ያቃታቸው ጊዜ ነበር:: ሆኖም አንድም ቀን ለችግር እጅ ሰጥተው የማያውቱት አቶ አያሌው ሰው ካገኙ ሰው እንደሚሆኑ በሚገባ ያምናሉ:: አንድ ቀን ይህ እንደሚሆንም ያስባሉ:: እምነታቸው ግን በአሰቡት ቀን ባይሆንም እውን ሆኖላቸዋል::
ሁለቱ የአክስታቸው ልጆች ከጅማ ሲመጡ እንዲወስዷቸውና በዚያ እየሰሩ እንዲኖሩ ጠይቀዋቸው ነበር:: ነገር ግን እነርሱ የራሳቸውን እህትና የእህት ልጆችን ስለወሰዱ ለእርሳቸው ቦታ አልነበራቸውም:: እሳቸውም አልተናደዱባቸውም፤ ተስፋም አልቆረጡም:: ይህ አቋማቸው በወራት ውስጥ ሌላ አቅጣጫ ጠቆማቸው:: በአካባቢያቸው የሚያውቁትና የሚቀርቡት ሰው ወደ ጅማ እንደሚሄድ ነገራቸው:: ስለዚህም ቤተሰብ በዚያ አላቸውና ለማንም ምንም ሳይናገሩ ተከትለዋቸው ሄዱ:: ጅማ ሲደርሱም ዘመዶቻቸውን ተቀላቀሉ:: ዓላማቸው ሰርቶ መለወጥ ነውና ብዙም በዘመድ ቤት አልቆዩም::
ድንገት ተነስተው አንዱን የአክስታቸውን ልጅ ይዘው እግራቸው ወደመራቸው ቦታ ለመድረስ ጉዞ ጀመሩ:: ጫካውን እያቋረጡም “የቡ” የምትባል ከተማ ደረሱ:: ከተማዋ በስፋት ቡና የሚመረትባት ነበረች:: ወቅቱ ደግሞ ቡና የሚለቀምበት ጊዜ ነው:: እናም እነርሱም በለቀማ ሥራው ላይ ተሰማርተው ለስድስት ወራት ሰሩ:: ወደ ስምንት ኩንታል ቡና ለየግላቸው አግኝተውም ተመለሱ:: ከዚያ ልጁን ለቤተሰቡ መልሰው የደረሳቸውን ቡና በመሸጥ ገንዘቡን ይዘው ወደትውልድ ቀያቸው ወሎ ገቡ::
ወሎ ከደረሱ በኋላ ግን ሀሳባቸውን አባታቸው ሊቀበሉት አልፈለጉም:: ‹‹አግብተህ ውለድ፣ ከዚህ መሄድ የለብህም›› አሏቸው:: ገና ሰርቼ አልጠገብኩም የሚሉት ባለታሪካችን በሀሳባቸው ሊስማሙ አልቻሉም:: ስለዚህም በሁለቱ መካከል አለመግባባት ተፈጠረና ቀያቸውን ትተው ወደ አዳማ (ናዝሪት) አክስታቸው ጋር ተጓዙ::
አክስታቸው ለእርሳቸው ቀርቶ ለራሳቸውም በብዙ ድካምና ልፋት የሚኖሩ ናቸው:: ስለዚህም ክረምትን ብቻ በዚያ ቤት አሳልፈው ሥራ ቅጥር ወደ ደላሎች ጋር አመሩ:: ከአዲስ አበባ የመጡ ሰዎች አገኙ ፤ ሰዎቹ የተማሩና ሌሎችን ማገዝ የሚወዱ ስለነበሩም እንደሚያስተምሯቸው ቃል ገቡላቸው:: ስለዚህም ማቄን ጨርቄን ሳይሉ ተከተሏቸው:: አዲስ አበባን መማሬያዬም፤ መስሪያዬም ያሉት ከዚህ በኋላ ነበር :: አሁን ያሰቡትን ነገር ያገኙም መስሏቸዋል:: ምክንያቱም በማታ የሚማሩበት እድል ተሰጥቷቸዋል:: ቀን ደግሞ በቤት ሰራተኝነት ገንዘቡ ቢያስም ተከፍሏቸው ይሰራሉ:: ብዙ ነገሮች ተደላድለውላቸዋልⵆ
ከጥበቃ እስከ ጽዳት ድረስ የመስራት ግዴታው የእርሳቸው ነበር:: ሥራው የወንድ የሴት አይባልም:: በዚህ ደግሞ ቀጣሪያቸው ሳይቀሩ ይሳተፋሉ:: እማወራዋ ታማሚ ስለሆኑ አባወራው ናቸው ምግብ የሚያበስሉት:: ከቤት ወጥተው ከጓደኞቻቸው ጋር በመሆን መስራት ሲጀምሩ ደግሞ የበለጠ መሰረት እንደጣሉላቸው ተረዱ::
ቤቱ ትምህርት ቤታቸው እንደነበርም አመኑ:: የሥራን ክቡርነት ፤ የቤት ጽዳት ጉዳይ አሳሳቢ እንዳይሆንባቸው አድርጓቸዋል፤ ሥራን ሳይመርጡ መስራትን አለማምዷቸዋል:: ከሁሉም በላይ ለዛሬ መሰረት የሆናቸውን የኤሌክትሮኒክስ ሥራን እንዲያውቁት አስችሏቸዋል:: ማለትም ቀጣሪያቸው የሌላ ሙያ ባለቤት ቢሆኑም በቤት ውስጥ የአካባቢው ሰው በሙሉ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች ሲበላሽባቸው ይሰሩላቸዋል:: ጎን ለጎንም እርሳቸውን ያሰሯቸዋል:: ይህ ደግሞ አቶ አያሌውን ከቴክኖሎጂው ጋር እንዲተዋወቅ አድርገዋቸዋል::
አቶ አያሌው አዲስ ነገር መሞከር የሚወዱ በመሆናቸው ከጭንቀት ልገላገል በሚል ከተመቻቸው ቤት መውጣት ፈለጉ:: ግን መንስኤ የሆናቸው አንድ ነገር ነው:: ይህም የአሰሪያቸው ጉብዝናቸውን አላደንቅም ማለት ነው:: በተደጋጋሚ የደረጃ ተማሪ ቢሆኑም አድናቆታቸውን አልቸሯቸውም:: ይልቁንም ‹‹በክፍል ውስጥ ሁለት ተማሪ ነበር አንደኛው በለጠህ አንተ ምርጫ ስለሌለ ሁለተኛ ወጣህ›› ይሏቸዋል:: ይህ ደግሞ እጅጉን ያማቸው ነበርና አክስቴ ታማለች በሚል ሰበብ ደብዳቤ በመጻፍ በእርሳቸው ፖስታ ሳጥን ቁጥር አስገብተው ከቤት እንዲወጡ ሆኑ::
ኑሯቸውን በትምህርት ቤት ያወቋቸው ጓደኛቸው አቶ እያሱ ቤት አደረጉም:: አቶ ኢያሱ ደግሞ ከሰዎች ጋር መግባባት የሚችሉና ብዙ የሚያቋቸው ሰዎች ያሏቸው በመሆናቸው መርካቶ ብርሃን ቁርስ ቤት አስቀጠረዋቸው በአስተናጋጅነት ሥራ ጀመሩ:: ከካሳንቺስ ተነስተው መርካቶ ድረስም ሌሊት በመነሳት በእግራቸው እየሄዱ ቢሰሩም ይህ ሁኔታ ከባድ ፈተና እንዲያጋጥማቸው አድርጓቸዋል:: በዚህም የሥራ ቦታ ለመቀየር ተገደዱ:: አንድ ዓመት ከፈተናው ጋር እየታገሉ ቆይተውም ሥራውን አቆሙትና በቀላሉ ሰርተው የሚገቡበትን አማራጭ ፈለጉ:: ይህም የሊስትሮ ሥራ ሲሆን፤ ከጃንሜዳ እስከ ቅድስት ማሪያም ቤተክርስቲያን ድረስ እየተዘዋወሩ ከትምህርታቸው ጎን ለጎን መሥራታቸውን ቀጠሉ::
ይህንን ሁኔታ የተመለከቱ በአዲስ አበባ ከተማ ታዋቂ የነበሩት የአየለ ፎቶ ቤት ባለቤት አቶ አየለ በራቸውን ክፍት አደረጉላቸውና ጃንሜዳ አካባቢ በሚገኘው ቡና ቤታቸው በአስተናጋጅነት ቀጠሯቸው:: ይህ እድል ደግሞ ለስድስት ወር ያህል ሲሰሩበት የቆዩትን ሊስትሮ ካማስቆሙም ባሻገር ሌላ መልካም አማራጭ ይዞላቸው ብቅ አለ:: በግብርና ሚኒስቴር ውስጥ የሚቀጠሩበትን ሁኔታ አመቻቸላቸው:: በ30 ብር ደሞዝ በተላላኪነት ተቀጥረውም የመንግስት ሰራተኝነቱን እንዲለማመዱት ሆኑ::
በመስሪያ ቤቱ በመዝገብ ቤት ሰራተኝነት ያገለገሉ ሲሆን፤ ከ10 ዓመት በላይ በቦታው ቆይተዋል:: ሆኖም በተቋሙ የቁጥጥር ኮሚቴ የሚባል ሲቋቋም እርሳቸው የቁጥጥር ኮሚቴው ጸሐፊ በመሆናቸው የተነሳ ነገሮች የተለየ ችግር ፈጠሩባቸው:: በዚህም ወደሌላ ቦታ እንዲመደቡ ውሳኔ ተላለፈ:: ሆኖም ግን እርሳቸው አጋጣሚዎችን መጠቀም ይችላሉና ነገሩን ውሳኔውን አስቀየሩት:: ደርግ ሊወድቅ ትንሽ ዓመታት ሲቀረው የውጪ ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር የሚባል ተቋም በመመስረቱ እዚያ የሚገቡበትን ሁኔታ አመቻቹ:: መጀመሪያ የመዝገብ ቤት ሰራተኛ በመሆን ከዚያም ኃላፊ በመሆንና በመቀጠል የጠቅላላ አገልግሎቱን ጨምረው በመስራት ለስድስት ዓመት ያህል አገለገሉ:: ከዚህ ጎን ለጎንም ትምህርታቸው እንዳለ ሆኖ የሙያና መደበኛ ትምህርት የሚባል በወጣቶች የተጀመረ እንቅስቃሴ ነበርና ለስድስት፣ ስምንትና 12ኛ ክፍል የወደቁ ተማሪዎች የመደገፍና የማስተማር ሥራን በማስተባበር ያከናውኑ ነበር::
አቶ አያሌው ለትምህርት በሄዱበት ከአገራቸው ውጪ ብዙ ሰርተዋል:: ሆኖም የአገራቸው ጉዳይ ያንገበግባቸዋልና እዚያ ያለውን ሥራ ጭምር ትተው በመምጣት ካንፓኒ ጭምር ከፍተው ሲንቀሳቀሱ ቢቆዩም ስራቸው ያልተመቻቸው ሰዎች ዳግመኛ ከአገራቸው እንዲወጡ አደረጓቸው:: ስለዚህም የአውስትራልያና የኒውዝላንድ ዜግነት ስላላቸው ከአገራቸው ሌላ ሚስት አግብተው ወደ አሜሪካ ተመለሱ:: በዚያም ልዩ ትኩረታቸውን መጽሐፍ መጻፍ ላይ በማድረግ ሁለት መጽሐፍትን ለንባብ አበቁ::
ባህር ማዶ የተሸገረው ሥራ ቀጣዩ ሥራቸው ባህር ማዶ የተሸገሩበት ሲሆን፤ ለትምህርት በሄዱበት ቀርተው ከአውስትራልያ ወደ ኒውዝላንድ በማቅናት የሰሩበት ነው:: ድርጅቱ ኮንቴክ ግሩፕ ኢንተርናሽናል ሲባል በኮምፒውተር ሳይንስ ፕሮግራሚንግ ሰራተኝነት ያገለገሉበት ነበር:: ከኒውዝላንድ ወደ አውስትራልያ ተመልሰው ደግሞ ሎካትሪክስ ኢንተርናሽናል ፒቲ ሊተድ በሚባል ድርጅት ውስጥ ሶፍትዌር ዶቨሎፐር በመሆን አገልግለዋል:: በዩኒውካስል ዩኒቨርሲቲ የፕሮግራም ሲስተም የተማሪዎች ረዳት ሆነውም ሰርተዋል::
ከዓመታት ቆይታ በኋላ ደግሞ የኒውዝላንድ ዜግነት ያላት ሚስት አግብተው የዚያን ዜግነት አግኝተው እንደልባቸው እየተዘዋወሩ እንዲሰሩ ሆኑ:: ስለዚህም የእርሳቸው የሥራ ቦታ ኒውዝላንድና አውስትራልያ ላይ ያረፈ ሆነ :: አውስትራልያ ላይ ራሳቸውን ወደማስተዳደሩ እንዲገቡ ያገዛቸውም እንደልብ መዘዋወር መቻላቸው ነው:: ከሰሯቸው ሥራዎች አንዱ ቴሌኮም ላይ የሚሰራ ካንፓኒ ውስጥ ተቀጥረው ለዓመታት የሰሩበት ሲሆን በሶፍትዌር ቴስት ኢንጅነርነት አገልግለውበታል:: ከዚያ ከአምስት ዓመት የሥራ ላይ ቆይታ በኋላ በአንድ ጉዳይ ባለመስማማታቸው የተነሳ ‹‹አርጅቷል›› በሚል ከሥራ ተሰናበቱ::
ሥራውን እንዲያቆሙ ያደረጋቸው የማርጀት ጉዳይ ሳይሆን ሀቀኝነታቸው ነበር :: እርሳቸው እንደሚሉት፤ መነሻው ድርጅቱ አንድ የስራ ፈቃድ (ላይሰንስ) ለአንድ ኮምፒውተር የሚል ስምምነት አድርጓል:: ይህንን ግን ለ100 ኮምፒውተር ካልተጠቀምኩ አለ:: ፊርማውን የሚያረጋግጡት ደግሞ የሶፍትዌር ቴስት ኢንጅነሩ እርሳቸው ናቸው:: እናም አይሆንም ብለው ከለከሉ:: በዚህም ሌላ መስሪያ ቤት ለመቀጠር እንኳን አልቻሉም ነበር:: ምክንያቱ ደግሞ የስራ ልምዳቸው ታይቶ የሰሩበት መስሪያ ቤት ሲደወል ‹‹ከሰርክል ውጪ ማሰብ አይችልም›› ይሉባቸዋል::
በምንም ጉዳይ ተስፋ ቆርጠው የማያውቁት ባለታሪካችን፤ ሁኔታውን መከላከል በሚችሉት መልኩ ሁሉ አከናውነው መግቢያ መስሪያ ቤታቸውን አመቻቹ:: ሥራው አየር መንገድ ውስጥ የተቀጠሩበት ሲሆን፤ ደንታ ( Dubai national Airline Transite Association) ይባላል:: የዱባይ ካንፓኒ ነው:: ዋና ሥራቸው ኬተሪንግ ሰርቪሱ ላይ ከቀረጥ ነጻ (ዲዩቲ ፍሪ) የሚገቡ እቃዎችን ቁጥጥር ማድረግና በኮምፒውተር መመዝገብ ነበር:: ኮቪድ እስኪገባ ድረስም በቦታው ላይ አገልግለዋል:: ዛሬ ደግሞ በአውስትራልያ ሆነው ከትምህርታቸው ጎን ለጎን የራሳቸውን ሥራ ይሰራሉ:: አንዱ የኢትዮጵያ ቡናን ማቅረብ ሲሆን፤ ሌላው እንደ ፋስት ፉድ አድርገው የጀርመን ባህላዊ ሶሴጅን በዳቦ አድርገው ይሸጣሉ::
የአገር አበርክቶ
ለአቶ አያሌው ሁልጊዜ አገር ትቀድማለች:: በየጊዜውም በሥራቸው ሁሉ እርሷን ሳያስታውሱ ተኝተው አያድሩም:: በኒውዝላንድም ሆነ በአውስትራልያ እያሉ በሚሰሯቸው ትልልቅ ሥራዎች ውስጥ ለአገሬ ምን ይጠቅማል የሚል ነገርን ያስባሉ:: በዚህም ብዙ ነገሮችን ሰርተው አገር ውስጥ የሚተገበርበትን ሁኔታ ይፈጥራሉ:: ለምሳሌ የኤሌክትሮኒክስ ላይብረሪ ማኔጅመንት ሲስተምን በአገር ውስጥ እንዲተገበር ያስቻሉት በኒውዝላንድ አገር ተቀጥረው በሚሰሩበት ተቋም ውስጥ ሶፍትዌሩን dere አማርኛ ተርጉመው በመስራታቸው ነው::
ነገሩ እንዲህ ነው ኒውዝላንድ ሆነው በሚሰሩበት ወቅት ጃፓኖች የላይብረሪ አጠቃቀማቸውን ለማዘመን ሲሉ ሶፍትዌር አሰሯቸው:: እርሳቸው በእንግሊዝኛ የሰሩትን በጃፓንኛ ተርጉመው ተግባራዊ አደረጉት:: እናም የአገራቸውን ችግር በቅርበት ያውቁታልና ወደ አማርኛ ተረጎሙት:: ይህ የተተረጎመ ሶፍትዌርም በመጀመሪያ በአንድ በካናዲያን ዜጋ አማካኝነት ተገዝቶ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ገባ:: ይህቺው ሴት በቀጣይ ወደ ጅማ ዩኒቨርሲቲ አምርታ ነበርና በዚያም የሚገባበትን ስርዓት ፈጠረች:: በመጨረሻ በብሪቲሽ ካውንስል አማካኝነት በ 300 ሺህ ብር ተገዝቶ ፒያሳ አካባቢ በነበረው ቤተመጽሀፍት (ላይብረሪ) ውስጥ ሲተገበር ቆየ:: በኋላም ትምህርት ቤቱ ወደ ኢንባሲው ሲገባ ለወመዘክር (Ethiopian national Archive) ተሰጠ:: አሁን ወመዘክር እየተጠቀመበት እንደሚገኝ አጫውተውናል::
ሌላው አቶ አያሌው ለአገራቸው ያበረከቱት ነገር የእጅ ስልክ(ሞባይል ) ገንዘብ መሞያ ካርድ የሚፋቀውን ወደ ወረቀት የሚቀየርበትን መንገድ የፈጠሩበት ነው:: ምክንያታቸው ደግሞ ሁለት ነገር ሲሆን የመጀመሪያው ካርዱ ሲፍቁት የተለያዩ በሽታዎችን ማምጣት መቻሉን በማረጋገጣቸው ፤ ሌላው ደግሞ ከህትመት ጋር ተያይዞ አገሪቱ እያወጣች ያለውን የውጪ ምንዛሪ ወጪ ለመቀነስ አስበው ነው:: ስለዚህም ጨረታ ወጥቶ ተወዳድረው አሸነፉ:: ሆኖም ጥቅማቸው በተለያየ መልኩ የቀረባቸው ሰዎች ሊያስቀምጧቸው አልቻሉም:: በሕይወታቸው ላይ አደጋ ለማድረስ ሁሉ ፈለጉ:: በዚህም የከፈቱትን ተቋም ይዘጋልኝ ብለው አመልክተው ሳይዘጋላቸው ትተው ከአገር ወጡ::
እንደ እርሳቸው እምነት ሀሳቡ እያሸነፈ ሲመጣ የሚበላው ገንዘብ ይቀራል:: ትርፉ አገር እንጂ ሌቦች አይሆኑም:: እናም ብልጫውን ላለማመን የጨረታውን ሰነድና የመጡ መሳሪያዎችን ደበቁት:: ይባስ ብሎም በየስድስት ወሩ የሚወጣው 500 ሺህ ካርድ ለሶስት ዓመት እንዲሆን ተደርጎ ጨረታው ተሰረዘ። አምስት መቶ ሺህ ብራቸውን ይዘው ጠብቁ ይከፈታል እያሉ ያጓጓቸው ገቡ:: በዚህም ሳይበቃቸው ያሳድዷቸው ጀመር:: ስለዚህም ‹‹ከመሞት መሰንበት›› ብለው የሚወዷትን አገራቸውን ትተው ዳግመኛ ወደውጪ ሄዱ:: ቴክኖሎጂውን ስላዩትና መረጃዎቻቸውን በእነርሱ እጅ ስለሆነ እርሳቸው ከወጡ በኋላ ወደ ተግባር ገቡበት:: ይህንን ሲመለከቱም ‹‹ከብሩ በላይ አገሬ ተጠቅማለችና ደስ ብሎኛል›› ይላሉ::
አገራቸውን ትተው ቢሄዱም ያልተዋቸው ነገሮች ነሩር:: ይህም የከፈቱትን ካምፓኒ ስላልዘጉት የስራ ግብር ተብሎ ከነቅጣቱ 700 ሺህ ብር እዲክፈሉ ተወሰነ:: ይህንን ያህል ገንዘብ ክፈል መባል ትክክል አይደለም ቢሉም ማንም ሊሰማቸው አልቻለም:: ሳይሰሩና ጁፒተር ከተባለ ድርጅት ያመጡትን ሪጅስተር ማሺኑን በደብዳቤ መልሰው ባሉበትም ነበር ክፈል የተባሉት:: ስለዚህ አገራቸውንን ትተው ወጡ:: በድጋሚ ሰባት ዓመት ቆይተው መስራት ፈልገው ጠቅላይ ሚኒስቴር ዶክተር ዐብይ አህመድ አገራችሁን በእውቀትና በጉልበት እንዲሁም በገንዘባችሁ አገልግሉ ሲሉ እሺ ብለው ቢመጡም ይህ ጉዳይ አላፈናፍን ስላላቸው ተመለሱ:: ዳግመኛ ወደአገራቸው የሚመልሳቸው ጉዳይ አገኙ:: ከመሄዳቸው በፊት በወቅቱ አመልክተው ስለነበር 700 ሺህ ብር እዳ በኮቪድ ምክንያት ከፍተኛ የግብር እዳ ያለባቸው ሰዎች ተለይተው ሲሰረዝላቸው እርሳቸው አንዱ ሆኑ:: በደረሳቸው ደብዳቤ መሰረት ነጻ መሆናቸውን አረጋጋገጡ:: ይህ ደግሞ ለአገራቸው ለመስራት እንዲንደረደሩ አደረጋቸው::
ለአገራቸው አዲስ መሰረት ለመጣልም ይፈልጋሉ:: አንደኛው ከሽንኩርት ኬሚካል መስራት ሲሆን፤ ይህንን በውጪ አገር በሚኖሩበት ወቅት አድርገውታል:: ሌላው ደግሞ ከቡና ወደ አራት አይነት ምርት መስራት ችለዋልና አገራቸው ላይ መከወን ይሻሉ:: በተጨማሪም መንግስት አቅዶት ያለውን የውጪ ባንኮችን ወደ አገር ውስጥ ማስገባት ጉዳይ ላይ መሳተፍ ይፈልጋሉ:: ለዚህ ደግሞ የተመቻቸ ሁኔታ እንዳላቸው ይናገራሉ::
ለሁለተኛ ድግሪያቸው የያዙት ፕሮጀክት በphysical fiat currency (PFC) and Digital fiat Currency ( DFC) እንዲሁም ከዲጅታል ባንኪንግ ጋር የሚያያዝ መሆኑ አንዱ በቴክኖሎጂ የታገዘ ሥራ ለማቅረብ የሚያስችላቸው ነው:: እናም ይህንን ፕሮጀክታቸውን ለመስራት አንድ ሚሊዬን ዶላር ጠይቀዋልና ሲጨርሱት ባንክ ስርዓቱ ላይ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ያምናሉ አገራቸውንም እንደሚጠቅሙበት አጫውተውናል::
መልዕክት
ከሙስና ጋር በተያዘ የመጀመሪያ መልዕክታቸውን ያስተላልፋሉ:: ሙስና ሲስተም እንጂ ሌላ አይደለም:: ማንም ባለስልጣንም ሆነ አመራር ያለ ህግ ክፍተት አይሰራም:: ሕጉን ተጠቅሞ ክፍተቱን አይቶ በአሰራር ውስጥ አልፎ አገርን ሊሰርቅ ይችላል:: እናም ይህንን ማጥፋት የሚቻለው ሰዎችን በመያዝና በማሰር ብቻ ሳይሆን መንገዱን (ሲስተሙን) በማስተካከል ነው:: ለሙስና መፍትሄው ሲስተሙ እንዳያሰርቅ ማድረግ ሲቻል ብቻ ነው:: ከዚያም በሻገር የተዘረፈውን ገንዘብ ለሕዝብ ጥቅም መዋል ሲቻል በራሱ ጊዜ ሌባው ሥራውን ያቆማል::
መንግስት ለአገር ጥቅም ሲባል የማያደርገው ነገር የለም:: ጥቅሙ ግን በጥልቀት መመርመርና ሕዝብን የያዘ መሆን አለበት:: ምክንያቱም አንዳንድ ጊዜ በምሁራን ብቻ ነገሮች ሲመረመሩ ህዝብ የማይረዳበት አጋጣሚ ይፈጠራል:: እናም ሕዝብ አውቆት ጸሐይ ሞቆት ፤ ጠቃሚነቱ ተረጋግጦ ነገሮች መከወን ይኖርባቸዋል:: ሕጎች መከበርም አለባቸው:: በተለይም ከውጪ የሚገቡ ነገሮች ላይ መለሳለስ ማሳየት አይገባም:: ለአገር ጥቅም ሲባል ጥብቅና ጥልቅ ምርመራ ማድረግ ያስፈልጋል ሌላው ምክረሀሳባቸው ነው:: እኛም ምክሩ መልካም ነውና እንመልከተው በማለት ለዛሬ የያዝነውን ሀሳብ ቋጨን::
ጽጌረዳ ጫንያለው
አዲስ ዘመን ታህሳስ 16/2015