ሰው ተወልዶ አንድ ቦታ እስኪደርስ ድረስ በርካታ መሰናክሎችና ውጣ ውረዶችን ማሳለፉ የግድ የሚሆንበት አጋጣሚ ብዙ ነው። አንዳንዱ ከውልደቱ ጀምሮ በአማረና በተደላደለ ሁኔታ ሲኖር ሌላው ደግሞ ከውልደቱ ጀምሮ ጥረህ ግረህ ብላ የሚለውን የፈጣሪ ትዕዛዝ እሱ ላይ ብቻ ይፈጸም ዘንድ የታዘዘ እስከሚመስል ድረስ ፍዳውን ያያል። በተለይም፣ ምቾት ከፊት መጥቶ ከኋላ ዘመን ላይ ሲጠፋ ጣጣና መከራው ብዙ ነው። ሰው በጉልምስና ጊዜው አግኝቶ አመሻሹ ላይ ሲያጣ፤ የሚወደው፣ የሚፈልገው ሁሉ ገሸሽ ሲልበት መመልከትን የሚያህል ሞት የለም። አባባሉም ወይም ምርቃቱም ቢሆን የሚለው “የማታ እንጀራ (ሲሳይ) ይስጥህ” አይደል? አዎ፣ ሰው ማታው ሲያምር ጥሩ ነው። ጧሪ፣ ቀባሪ ሲኖረው መልካም ነው። ያ ሳይሆን ሲቀር ግን ብዙ ነገሮች ከባድ ይሆናሉ። ከባድ መሆን ብቻም አይደለም፤ አሰቃቂም የሚሆኑበት ጊዜ የበዛ ነው።
የዛሬ የህይወት ገጽታ አምድ እንግዳችን፣ ምንም እንኳን የልጅነት ጊዜያቸው ያን ያህል ያማረ፣ የተደላደለ የሚባል ባይሆንም፣ መካከል ላይ ግን በመልካም የህይወት መስመር ላይ ነበሩ። በጉልምስና እድሜያቸውም ቢሆን ችግር አላገኛቸውም ነበር። በትልቅ የመንግስት መስሪያ ቤት ተቀጥረው ለዓመታት አገልግለዋል። ኋላም ትዳር መስርተው የልጆች አባት፤ የቤተሰብ ኃላፊም ለመሆን በቅተው ነበር። ዳሩ ግን፣ ይህ ኑሯቸው አብሯቸው ማምሸት አልቻለም። ህይወት ፊቷን ስታዞርባቸው፤ አለኝ የሚሉት ነገር ሁሉ ከእጃቸው ሲወጣ እንኳን ዘመድ አዝማድ፣ የሚያውቋቸው ይቅሩና የአብራካቸው ክፋይ የሆኑትም ልጆቻቸው ጠሏቸው። ይህ መሆኑ ለእሳቸው እጅግ በጣም ከባድ ብቻ ሳይሆን፣ ባልኖርስ የሚያሰኝ ቢሆንም፣ ነገር ግን ራሳቸውን ገዝተው ልጆቼም አንድ ቀን ሲገባቸው ”አባቴ” ይሉኝ ይሆናል ብለው በማሰብ፣ ቤታቸውን ጥለው ወጥተው፣ ደግ ልብ አነሳስቶ እንደሳቸው የከፋቸውን፣ ቀን የጨለመባቸውን፣ ይሸሸጉበት ያጡትን የሚሰበስበው መቄዶኒያ ለመግባታቸው በቂ ምክንያት ሆናቸው።
አቶ ጌታሁን መኮንን ሲታዩ እርጅና ተጭኗቸዋል፤ ይሁን እንጂ ቆፍጣና ናቸው። በአንድ ወቅት የመኪና አደጋ ደርሶባቸው ስለ ነበር እግራቸው እንደገፈለጉ አያራምዳቸውም። ነገር ግን ከዘራቸውን መርኮዝ እያሉ ያሰቡበት ይደርሳሉ፤ በመቄዶኒያ ግቢ ውስጥም እንግዶችን ተቀብሎ ቦታ ከመምራትና ከማስተናገድ ጀምሮ በአቅማቸው የሚችሉትን ሁሉ ያግዛሉ። ስለራሳቸው የሚጠይቃቸው ሰው ደግሞ ይወዳሉ። አውርተው የማይጠግቡት ታሪክ ባለቤትም ናቸው።
አቶ ጌታሁን የዛሬን አያድርገውና መኪናቸውን እያሽከረከሩ በአዲስ አበባ ጎዳና ላይ ሲዘዋወሩ ተመልካቻቸው ብዙ ነበር፤ እሳቸውም መዝናናት በጣም ያዘወትሩ ስለነበር የአጃቢም ችግር አልነበረባቸውም። ዛሬስ ያላችሁ እንደሆን በመጦሪያ ማዕከሉ የተሰጣቸውን የሚበሉ፤ በዚህ ሂድ፣ ይህንን አድርግ ሲባሉ ”እሺ” ብለው የሚታዘዙ ምስኪን አዛውንት ሆነዋል።
አቶ ጌታሁን ተወልደው ያደጉት ሆሳእና ከተማ ነው። አባታቸው በጅሮንድ የነበሩ ሲሆን እናታቸው ደግሞ የራስ ኃይሉ የልጅ ልጅ ናቸው። በወቅቱ ጣሊያን አገሪቱን ወርሮ ስለነበር ልኡል ራስ ኃይሉ ደግሞ ከኃይለሥላሴ ጋር ባለመስማማታቸው በግዞት ወላይታ፣ ሶዶ እንዲሄዱ ሆነ፤ የአቶ ጌታሁን እናትም አብረው ሄዱ። በወቅቱ የጣሊያን መንግስት ወላይታንም እንደሌሎቹ የአገሪቱ አካባቢዎች ሲወርር በአጋጣሚው ከእስር ተለቀቁ። ጉዟቸውንም ወደ ሻሸመኔ አደረጉ። በጅሮንድ መኮንን የአቶ ጌታሁንን እናት አገኟቸው፤ ጠልፈውም ሆሳዕና እንደወሰዷቸው ይናገራሉ።
“. . . አባቴ በወቅቱ በጅሮንድ ነበሩ። በሌላ በኩል ደግሞ በየገበያው እየተዘዋወሩ ግብር የሚያስከፍሉ (ቀራጭ) ነበሩ፤ እናም እናቴን ሻሸመኔ ላይ ጠልፈው ወደ ሆሳዕና ወሰዷት፤ ወዲያውም እኔ ተረገዝኩ፤ ቀኑ ሲደርስም ተወለድኩ። እኔ በተወለድኩ በሶስተኛ ወሬ ራስ ኃይሉ አዲስ አበባ ገቡ፤ ከዛም በወቅቱ የከምባታ ገዢ ለነበሩት ራስ አባተ ቧ ያለው ደብዳቤ ላኩ። የደብዳቤው ይዘትም የልጃቸው ልጅ እርሳቸው አገር ተጠልፋ መሄዷንና በአስቸኳይ ፈልገው እንዲልኩላቸው የሚለምን ነበር። ራስ አባተም አስፈልገው በማግኘታቸው ”እናቴ እኔን በህጻንነቴ ጥላኝ አዲስ አበባ መጣች” በማለት ሁኔታውን ያስታውሳሉ።
እናታቸው ወደ ቤታቸው ሲመለሱ አቶ ጌታሁን ከአባታቸው ጋር ሆሳዕና ለመቅረት ተገደዱ። ምክንያቱ ደግሞ እናታቸው የንጉሳውያን ቤተሰብ ስለሆኑ ሳይዳሩ፣ ሳይኳሉ ልጅ ወልዶ ይዞ መግባት ፍጹም የተከለከለ ነውር ስለነበር ነው።
አቶ ጌታሁን እስከ አስር ዓመታቸው ድረስ ከእንጀራ እናታቸው ጋር ሲኖሩ ትምህርት የሚባለውን ነገር አያውቁትም ነበር። አባታቸውም ቢሆኑ ለራሳቸው የተመቸ ኑሮን ከማሰብ ባለፈ ስለ ልጁ አያያዝ የተናገሩት ነገር አልነበረም። ነገር ግን ፈጣሪ ጥሎ አይጥልምና በሰፈር ውስጥ ፊደል የሚያስቆጥሩ፣ የኔታ በቀለ የሚባሉ አስተማሪ ሁኔታቸውን በማየት በጣም ስላዘኑ “… ይህ ልጅ እናቱ የለችም፤ የእንጀራ እናቱ ደግሞ የራሷን ሁለት ልጆች እያስተማረች ይህንን ልጅ ለማስተማር አልፈቀደችም። እኔ አስተምረዋለሁ።” በማለት ጠዋትና ማታ ትምህርት ቤት እየወሰዱ ያስተምሯቸው ጀመር።
አቶ ጌታሁን የመማር ፍላጎቱ ስለነበራቸውም በጣም ጎበዝ ተማሪ ሆኑ። አባታቸውንና እንጀራ እናታቸውን እየተደበቁ በማጥናት ትምህርቱን ገፉበት። ሶስተኛ ክፍልም ደረሱ።
“. . . ራስ ኃይሉ 13 ልጆች፤ 17 የልጅ ልጆችን አይተዋል። ልክ እኔ ሶስተኛ ክፍል ስደርስ እሳቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ። ሁሉም የሚገባውን ሲወርስ የእኔም እናት ሲኒማ ራስ አካባቢ ያለን ቤት በአንድ ሺህ ብር፤ ሲዳሞ ተራና አቡነ ዼጥሮስ ሀውልት አካባቢም ያሉ ቤቶችን ተከራይተው ኪራዩ እንዲሰጣት ተናዘዙላት። የወር ገቢዋም ወደ 1ሺ 46 ብር ገደማ ደረሰ። ይህ ደግሞ በወቅቱ በጣም ትልቅ ገንዘብ ነበር። እናቴ ትዳር መስርታ የነበረ ቢሆንም ልጅ ማግኘት ግን አልቻለችም።” በማለት ስለ እናታቸው የሚናገሩት አቶ ጌታሁን፣ ቀጥሎ የነበረውን የእናታቸውን ውሳኔም እንደዚህ ያስታውሱታል።
“. . . እናቴ ልጅ እምቢ ስላላት ይሁን እኔን ፈልጋኝ ባላውቅም እኔ ወዳለሁበት አገር ለአባቴ እንዲደርሰው ደብዳቤ ጽፋ ላከች ’… ከአንተ ጋር ሆኜ የወለድኩትን ልጄን ምንም ይሁን ምን ላክልኝ። ሞቷል ግን እንዳትለኝ፤ ቢሞት እንኳን እሱን የሚተካ ልጅ ብቻ ላክልኝ፤ እባክህ’። ደብዳቤው ደግሞ ከትምህርት በጌት ስመጣ እጄ ላይ ደረሰ።”
አባታቸው ስለ ልጃቸው ትምህርት ቤት መሄድ (መማር) ምንም መረጃ አልነበራቸው። አቶ ጌታሁንም የደረሳቻቸውን ደብዳቤ ያልታሸገ በመሆኑ ከፍተው ያነባሉ። ሲያነቡት ግን በጣም ያልጠበቁት ነገር ሆነባቸው። ደብዳቤው በቀጥታ የመጣው ከእናታቸው መሆኑን ተገነዘቡ። በከፍተኛ ደስታ ውስጥ ሆነውም አባታቸው እስከሚመጡ መጠባበቅ ጀመሩ። አባታቸው ሲመጡም ”መልዕክተኛ ያመጣው ደብዳቤ ነው” በማለት ሰጧቸው። አባታቸውም ”ምንድን ነው?” ብለው ሲጠይቋቸው ማንበብ እንደማይችሉ፤ ከፍተውም እንዳላዩት በመናገር አባታቸው እስኪያነቡላቸው ድረስ በጉጉት ይጠብቃሉ። አባታቸውም ደብዳቤውን ከፍተው ካዩ በኋላ ከእናታቸው መላኩንና ሰሞኑን ገበያ ወጥተው ልብስ ገዝተውላቸው እናታቸው ጋር እንደሚወስዷቸው ቃል ይገቡላቸዋል።
“. . . አንደኛ እናቴ በህይወት ኖራ እኔን ፈልጋ ደብዳቤ መላኳ፤ ከዛ ቀጥሎ ደግሞ አባቴ ደብዳቤውን ካየ በኋላ የሰጠኝ ተስፋ ተደማምሮ በጣም አስደሰተኝ። መቼ ይሆን ቀኑ ብዬ እንድጓጓ አደረገኝ። ነገር ግን አባቴ በቃሉ መሰረት ልብሱንም ሊገዛልኝ፣ እናቴ ጋርም ሊወስደኝ ሳይችል ቀረ። በዚህ በጣም ተናደድኩ” በማለት ሁኔታውን ያስታውሳሉ።
ነገር ግን እናታቸው አንዴ ልጃቸውን የማግኘት ልባቸው ተነስቷልና አቶ መኮንን በተባለው መሰረት ልጃቸውን ልከው ባያሳዩዋቸውም እራሳቸው ጓዛቸውን ጠቅልለው ልጃቸው ወዳሉበት አገር አቀኑ።
“. . . ምንም እንኳን በእሷ መልዕክት መሰረት አባቴ እኔን ወደ እናቴ ለመውሰድ ባይችልም እናቴ እራሷ እኔ ያለሁበት ድረስ መጣች። በቅሎ ላይ ቁጭ ብላ ሳያት በጣም ታምራለች። በዛ ላይ ደግሞ ትልቅ ሻንጣ ይዛለች። በወቅቱ አባቴ ቤት አልነበረም። እንጀራ እናቴ ግን ነበረች። እሷም ጥሩ አቀባበል አደረገችላት። የነበረው ደስታ ደስታ እንዳይመስልሽ። አባቴም ቢሆን በጣም ደስተኛ ነበሩ። በወቅቱ እናቴ እኔን በማግኘቷ በጣም ደስ አላት። ነገር ግን ያለሁበትን ሁኔታ፣ ጉስቁልናዬን ስታይ ተከፋች። እናም ”ይዤህ ብሄድ ፈቃደኛ ነህ?” ብላ በሚስጢር ጠየቀችኝ። በነገራችን ላይ፣ እሷ ብቻ ሳትሆን የክርስትና አባቴም ጠይቀውኝ ነበር፤ እኔም ተስማማሁ። ይህንን ስስማማ ግን አባቴ አያውቅም” በማለት ሁኔታውን ያስታውሳሉ።
ከእናታቸው ጋር በዚህ ሁኔታ የተስማሙት አቶ ጌታሁን ልብስ ተገዝቶላቸው፣ በቀጣዩ እሁድ ቀን መጥተው እንደሚወስዷቸው ቃል ገብተውላቸው ተለያዩ። ቀኗን በጉጉት ሲጠብቋት መድረሱ አልቀረም ደረሰ። እናትም እሁድ እለት ልጃቸውን ለመውሰድ ተገኙ። በወቅቱ ሆሳእና አውሮፕላን ይገባ ስለነበር አውሮፕላን ማረፊያው ላይ መጠበቅ ጀመሩ። አባታቸውም የልጃቸው እናት መምጣታቸውን አውቀው ስለነበር ስጦታ ሊሆናቸው የሚችለውን፣ አገሩና ቤቱ ያፈራውን ነገር ሁሉ ይዘው እዛው ተገናኙ። እናትም ”ቸኩያለሁ” በሚል ልጃቸውን ”ና ተሰናበተኝ” ብለው ከሳሙት በኋላ ”እስኪ ግባና አውሮፕላኑን እየው” በማለት ወደ ውስጥ እንዳስገቧቸው ይናገራሉ።
“. . . በወቅቱ አባቴ ከእናቴ ጋር እንደምሄድ አላወቀም ነበር፤ አውሮፕላኑ ውስጥ ግባ ስትለኝም አይቼ እንድወጣ መስሎት ነበር። ነገር ግን እናቴ እኔን ግባ ካለችኝ በኋላ ወደ አባቴ ዞር ብላ ”ልጄን ስለሰጠኸኝ እግዚአብሔር ይስጥህ” ብላ ተሰናብታው፣ እኔን ይዛኝ አዲስ አበባ ገባን” በማለት ከእናታቸው ጋር አዲስ አበባ የመጡበትን አጋጣሚ ይናገራሉ።
ኑሮ በአዲስ አበባ
አዲስ አበባ ከተማ እንደገባን ያረፍነው ጉለሌ አካባቢ በሚገኘው የእናቴ መኖሪያ ቤት ነው። ደማቅ አቀባበል ተደረገልኝ። ከዛም እናቴ ያሉብኝን የጤና ችግሮች በሙሉ ማስመርመር ጀመረች። አንዱና ትልቁ ችግሬ ቋንጃዬ አካባቢ ስራመድ የሚይዘኝ ነገር ነበርና እሱን በህክምና አስተካከሉልኝ። ትምህርቴንም መቀጠል ስነበረብኝ መድሃኒአለም ትምህርት ቤት አስገባችኝ።
ትምህርቱን እንደወደዱት የሚናገሩት አቶ ጌታሁን እሳቸው ከተማሩት ትምህርት ጋር ሲያነጻጽሩትም ያን ያህል ልዩነት እንዳላዩበት ያስረዳሉ። ልዩነቱንም ለማጥበብ በትምህርታችው ጎብዘው እየሰሩ ስለነበር ዓመቱ መጨረሻ ላይ ፈተና ተፈትነው ውጤት ሲመጣም ሶስተኛ ደረጃን አገኙ (3ኛ ወጡ ማለት ነው)። ይህ ደግሞ እጅግ በጣም አበረታታቸው።
አቶ ጌታሁን ሰኔ ላይ ትምህርታቸውን እንዳጠናናቀቁ ወደ ትውልድ መንደራቸው ነው መሄድ የፈለጉት። እዛ ሲሄዱም ከአለባበስ ጀምሮ በሁሉም ነገር ከሌሎቹ ተለይተዋል። ብዙዎቹ በስኬታቸው ተደስተዋል። አባታቸውም ልጃቸው በዚህን ያህል ደረጃ ስለተለወጡ በመደሰት መርቀው ዳግም ወደ አዲስ አበባ ላኳቸው።
አቶ ጌታሁንም መስከረም ጠብቶ ወደ ትምህርታቸው ተመለሱ። አራተኛ፣ አምስተኛ . . . እያሉ ስድስተኛ ክፍል ደረሱ። ብሄራዊ ፈተና የሆነውን ሚኒስትሪም ተፈተኑ። በወቅቱ የሚኒስትሪ ፈተናን የወደቀ ሰባተኛ ክፍል ሲገባ፤ ያለፈ ደግሞ ሰባተኛ ክፍልን ዘሎ ስምንተኛ ክፍል ይገባ ነበርና አቶ ጌታሁን የስድስተኛ ክፍል ሚኒስትሪ ፈተናቸውን በሚገባ ስላለፉ ስምንተኛ ክፍል ገቡ።
ስምንተኛ ክፍልንም ካጠናቀቁ በኋላ የገቡት ወደ ተግባረ እድ ቴክኒክና ሙያ ትምህርት ኮሌጅ ነበር። እዛም “የሜካኒካል ድሮዊንግ” ትምህርታቸውን ለሁለት ዓመት ተከታትለው ከንጉሠ ነገሥት አጼ ኃይለሥላሴ እጅ ሰርተፍኬታቸውን፤ እንዲሁም የሰዓት ሽልማት አግኝተው ለመመረቅ በቁ።
ስራ በብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት
በወቅቱ ማተሚያ ቤቱ አዲስ የነበረ ሲሆን በ140 ብር የወር ደመወዝ ቀጠራቸው። እሳቸውም ወደ ማተሚያ ቤቱ የሚመጡ የህትመት ጥያቄዎችን ሁሉ ዲዛይን እያደረጉ ለህትመት የማዘጋጀት ስራቸውን ተያያዙት።
“. . . ስራ ማግኘቴ እጅግ ነበር ደስ ያለኝ። የመንግስት ስራ ደግሞ ደስ ይላል። እናቴም እኔው ብቻ ስለነበርኩ ልጇ ደስ ብሎኝ እንድደሰትላት ብዙ ጥረት ታደርግ ነበር። በወቅቱ ስራ ስይዝ መኪናሁሉ ገዝታ ሰጠችኝ። በዛም ከተማዋን መዞር፣ በእረፍት ቀን ደግሞ ከጓደኞቼ ጋር ተሰብስበን ናዝሬት እየደረስን መመለስ . . . ብቻ ወቅቱ በጣም የተዝናናሁበት፤ ብዙ ጥሩ ጊዜያትንም ያሳለፍኩበት . . . ለእኔ በጣም አስደሳች ጊዜ ነበር” ይላሉ።
አቶ ጌታሁን በዚህ መልኩ እየሰሩ ባሉበት ሁኔታ በአገሪቱ ላይ የመንግስት ለውጥ መጣ። ንጉሳዊው አስተዳደር ወርዶ ወታደራዊው ደርግ ስልጣኑን ተቆጣጠረ። እሳቸውም በስራቸው ቀጠሉ። ከኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት፣ እንዲሁም ከሌሎች ደንበኞች የሚመጡ የህትመት ጥያቄዎችንም በብቸኝነት በሚያሳትመው ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት ዲዛይነር (እንዲሁም የህትመት ክትትል) ሆነው ገጾችን እያስዋቡ፣ ከደረጃቸው ዝቅ እንዳይሉ፣ እየተቆጣጠሩ ለህትመት ሲልኩም ቆዩ። በሂደትም ደመወዛቸው 7 መቶ ብር ደረሰ። እሳቸው ግን ባንክ ማስገባትን (ቁጠባን) አይወዱም ነበር። ይዝናናሉ፣ በተረፋቸው የተቸገረን ይረዱበታል። ”እንደውም . . .” ይላሉ “እንደውም . . . እናቴ ቤት ያለደመወዝ ይሰሩ ከነበሩ ልጆች መካከል አንዱን አስተምሬ አሁን በኢትዮጵያ አየር መንገድ ግራውንድ ቴክኒሻን ሆኖ በመስራት ላይ ይገኛል።” በማለት የገንዘብ አጠቃቀማቸውን ከሰብአዊ ባህርያቸውና ኃላፊነትን ከመወጣት አቅማቸው ጋር አዋዝተው ይናገራሉ።
ለ28 ዓመታትም ደከመኝ፣ ሰለቸኝ . . . ሳይሉ፣ ለህትመት ስራዎች ጥራትና ውበት የበኩላቸውን ሙያዊ ኃላፊነት ሲወጡ የቆዩት አቶ ጌታሁን ምንም ባላሰቡትና ባልጠበቁት ወቅት የህይወታቸውን መስመር የሚቀይር መጥፎ አጋጣሚ ተፈጠረ።
የእስር ጊዜያት
በ1984 ዓ.ም አንዳንድ የማውቃቸው ሰዎች በእስር ላይ ነበሩ፤ እኔ ደግሞ ”ለእነሱ ትመሰክራለህ በሚል ስድስት ኪሎ አካባቢ ወደሚገኘው ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተጠራሁ። እዛም ከደረስኩ በኋላ ይፈልጉኝ የነበሩትን አካላት አገኘኋቸው” በማለት በወቅቱ የገጠማቸውን የሚናገሩት አቶ ጌታሁን ቀጥለውም ወደ ማረፊያ ቤት እንዲሄዱ ተደረጉ። ሰንበትበት ሲልም ”የቀይ ሽበር ወንጀለኛ ነህ” በሚል ፍርድ ቤት ተከሰሱ።
አቶ ጌታሁን በወቅቱ ከስ ይመስረትባቸው እንጂ ከአንድ ቀን በላይ ፍርድ ቤት አልሄዱም፤ ዝም ብለው እስር ቤት ቁጭ ብለው ዓመታት ተቆጠሩ እንጂ። ኋላም በእሳቸውና በቤተሰባቸው ጥረት ከ12 ዓመታት የእስር ቤት ቆይታ በኋላ ተፈቱ።
አቶ ጌታሁን ”ከምንም በላይ የሚገርመው” ይላሉ ”ፍርድ ቤት መቅረብ የቻልኩት በታሰርኩ በአስረኛ ዓመቴ ላይ ነበር። እስከዛ ድረስ ለማቆየታቸው ደግሞ ዋናው ምክንያት እሱ ላይ ምስክሮችን ለማሰባሰብ ጊዜ ስለሚያስፈልገን ረጅም ቀጠሮ ይሰጠን እያሉ ስለሚያጓትቱት መሆኑንም ይናገራሉ።
“. . . ከእስር እንደወጣሁ በቀጥታ ያመራሁት 26 ዓመት ወደ ሰራሁበት ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት ነበር። ጡረታዬ እንዲከበርልኝ ጠየኩ። ነገር ግን ’የታሰርክበት ጊዜ ከሶስት ዓመት በላይ በመሆኑ የጡረታ መብትህን አያስከብርልህም። ከሶስት ዓመት በላይ ለሆነ እስረኛም ጡረታ አይገባውም’።” መባላቸውን ያስታውሳሉ።
አቶ ጌታሁን ጡረታዬ ሊከበርልኝ ይገባል በማለት ወደ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን፤ እንዲሁም፣ ሌሎች ቦታዎችም ለመሄድ ቢሞክሩም ውጤቱ ግን አመርቂ አልነበረም። ከዚህ በኋላ ህይወታቸውን ለማቆየት የተለያዩ ማተሚያ ቤቶች በመሄድ ለመስራት ሞከሩ። ነገር ግን እሳቸው በሚፈልጉት መንገድ ሊሆንላቸው አልቻለም። የለመዱት አይነት የስራ ሁኔታም አላገኙም። ያም ቢሆን ግን መስራትን መረጡ። በዚህ መካከል የቀን ጎዶሎ ገጥሟቸው። አንድ ቀን ጠዋት ወደ ስራ ሲሄዱ የመኪና አደጋ አጋጠማቸው። ይህ ደግሞ ከስራም ብቻ ሳይሆን ከህይወት ሩጫቸው ሁሉ ገታቸው።
አቶ ጌታሁን በ1980 ዓ.ም ከልጆቻቸው እናት ጋር ትዳርን መስርተው አንዲት ሴትና ሶስት ወንዶች ልጆችን ያፈሩ በሚችሉት አቅም አስተምረው ለወግ ማዕረግ ያበቁ ቢሆንም፤ እንደ ሌሎች አባቶች በቤታቸው ቁጭ ብለው ልጆቻቸው ጠዋሪ ቀባሪ ሊሆኗቸው አልቻሉም። ልጆቻቸው እስከ ዲግሪ ድረስ የመማር እድልን ቢያገኙም (አሁንም እየተማረ ያለ አለ) በተለያየ ምክንያት ስራ ስላላገኙ አባታቸውን መሰብሰብ ሳይሆንላቸው ቀረ። አባት አቶ ጌታሁንም ቤት ቁጭ ብለው የልጆቻቸውን ችግር ማየት አልፈለጉም። እናም ”የመጨረሻዬ . . .” ብለው የወሰዱት አማራጭ ወደ መቄዶንያ፣ የአረጋውያንና አእምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል መግባትን ነው።
“. . . አባት አባት ሁኖ የሚከበረው ከእጁ ላይ የሆነ ነገር ሲኖረው ነው። እኔ ምንም የለኝም፤ ቤት አልሰራሁም። ከእናቴ የወረስኩትን ቤት ደርግ ቀምቶኛል። ከዛ በኋላ ህይወቴን የገፋሁት በኪራይ ቤት ነው። ያስቀመጥኩት፣ አሁን የእድሜያ ማምሻ ላይ ልጠቀምበት የምችለው ጥሪት የለኝም። ይህ መሆኑ ደግሞ ልጆቼ የምፈልገውን አይነት ፊት ሊያሳዩኝ አቃታቸው፤ እኔም የእነሱን ችግር ቁጭ ብዬ ከማይ በማለት የደከመ አቅሜን እየጎተትኩ መቄዶንያ መጥቼ መስራቹን፣ ቢኒያም በለጠን ለመንኩት እሱም “. . . እኛ ጠዋሪ ቀባሪ እንሆኖታለን” ሲል ወደ ተቋሙ አስገባኝ” በማለት ወደ ማእከሉ የገቡበትን ሁኔታ ይናገራሉ።
አባት በመቄዶንያ
ዛሬ አቶ ጌታሁን የከፋውን ቀን ገለል ሊያደርጉ፤ ማምሻቸውን ጎዳና እንዳይወጡ መቄዶንያ ታድጓቸዋል። በማዕከሉ መጠለያን ጨምሮ የምግብና የህክምና አገልግሎትን ያገኛሉ። እሳቸውም ይህንን ላደረገላቸው ማዕከል ያቅማቸውን ለማገዝ እንግዳ ከመቀበል፣ ቦታ ከመምራት . . . ጀምሮ የሚችሉትን ሁሉ ይሰራሉ።
“. . . ልጅ ማጣት ምንም ላይሆን ይችላል። በስነልቦና መጎዳት ግን ከጉዳቶች ሁሉ የከፋ ጉዳት ነው። መጠለያ አጥቼ መንገድ ላይ ብወድቅ እዛው ሞቼ እቀራለሁ እንጂ ማን ያነሳኛል? አሁን ለሆዴ አላስብ። ለመኝታዬ . . . ምን ልልበስ ብዬ አልጨነቅ፤ ኧረ ቢኒያም፣ ረጅም እድሜ ከጤና ጋር ይስጠው። ተከብሬ፣ አምሮብኝ እየኖርኩ ነው” በማለት ያሉበትን ወቅታዊ ሁኔታ ይናገራሉ።
አቶ ጌታሁን መቄዶንያ ከገቡ አሁን ሶስት ዓመት ሆኗቸዋል። በእነዚህ ጊዜያት ደስተኛም መሆን ችለዋል። “. . . መቄዶንያ እኮ የደሃ መሰብሰቢያ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ ጭንቅላት ያለበት ቤት ነው። ምሁሩ፣ ዶክተሩ፣ አውሮፕላን አብራሪው፣ ወታደሩ፣ የጦር ጀነራሉ . . . ኧረ ስንቱ፤ ብቻ ኢትዮጵያ አንጡራ ሃብቷን አፍሳ ያስተማረቻቸው፤ ነገር ግን፣ ጊዜ ያዘነበለባቸው፣ እንደ እኔ ያሉ በርካታ ሰዎች አሉ። ”እሱ ባይኖር ኖሮ ምን እንሆን ነበር?” ብዬ ሳስብ ግራ ይገባኛል። በርካታ ደጋግ ኢትዮጵያውያንም ስላሉ እስከ አሁን ችግር አልገጠመንም” በማለት ስላሉበት ሁኔታ ማዕከል ይናገራሉ።
እኛም እንላለን፣ እጆች ሁሉ ወደ ሜቄዶኒያ ይዘርጉ!!!
እፀገነት አክሊሉ
አዲስ ዘመን እሁድ ታህሣሥ 9 ቀን 2015 ዓ.ም